የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ምርጫ እንዲዘገይ መጠየቁ
ዓርብ፣ ነሐሴ 11 2004
ለፊታችን ሰኞ የታሰበው የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ምርጫ ና የሽግግሩ መንግሥት የጊዜ ገደብ ማብቂያ ሳይገፋ አንደማይቀር እየተነገረ ነው ። ዶቼቬለ ያነጋገራቸው በሶማሊያ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር የሚያካሂድ ተቋም ሃላፊ ጅብሪል አብዱል እንዳሉት የሶማሊያን ረቂቅ ህገ መንግሥት በቅርቡ ያጸደቁት የሶማሊያ የጎሳ ተወካዮች ፕሬዝዳንቱን የሚመርጡትን የምክር ቤት አባላት ስም ዝርዝር እንዲያቀርቡ የተሰጣቸው የጊዜ ገደብ ከ 10 ቀናት በፊት ቢያበቃም እስካሁን የሚፈለገው የምክር ቤት አባላት ቁጥር አልተሟላም ። የሃገር ሽማግሌዎቹም ቀኑ እንዲገፋ በመጠየቅ ላይ ናቸው ።
የሶማሊያ የህገ መንግሥት አፅዳቂ ምክር ቤት ፣ የሶማሊያን ረቂቅ ህገ መንግሥት እንዳፀደቀ የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ምርጫና የሶማሊያ መንግሥት ምስረታ ነሐሴ 14 ,2004 ዓ.ም እንደሚካሄድ በእርግጠኝነት ነበር የተነገረው ። ይሁንና ይህ በተያዘው እቅድ መሠረት መከናወኑ እንደሚያጠራጥር ይሰማል ። መቀመጫውን ሶማሊያ መዲና መቋዲሾ ያደረገው በሶማሊያ ጉዳይ ላይ ጥናትና ምርምር እንዲሁም ውይይት የሚያካሂደው በእንግሊዘኛው ምህፃር CRI የተባለው የጥናት ማዕከል ዋና ሃላፊ ጅብሪል አብዱል ለዶቼቬለ እንደተናገሩት የሶማሊያ ሸንጎ አባላት ተጨማሪ ጊዜ ጠይቀዋል ።
« በአሁኑ ሰአት የሶማሊያን ቋሚ መንግሥት ለመመሥረት እጎአ ነሐሴ 20 2012 አመተ ምህረት በተያዘው ቀነ ገደብ አደራጆቹም ሆነ የሃገር ሽማግሌዎች የተያዘላቸውን እቅድ ተግባራዊ ሊያደርጉ የሚችሉ አይመስልም ። ይህ ሊሆን ስለማይችልም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የተለያዩ አካላት ቀነ ገደቡ ወደ ነሐሴ መጨረሻ ወይም ደግሞ ወደ መስከረም መጀመሪያ መገፋት አለበት ሲሉ ጥሬ እያቀረቡ ነው ። »
የዚህም ምክንያቱ ይላሉ አቶ ጅብሪል የሶማሊያ የምክር ቤት አባላት ምርጫ መጓተት ነው
« ምክንያቱ የሶማሊያ ጉዳይ በሚመለከታቸው ዋነኛ ተዋናዮች መካከል የሚካሄደው የፖለቲካ ድርድር ነው ። የሃገር ሽማግሌዎቹ ራሳቸው በምርጫ ሂደት ውስጥ ፈተና ገጥሟቸዋል ። አንዳንድ የጎሳ ተወካዮች በምክር ቤት አባላት ምርጫና ያጭዋቸውን የምክር ቤት አባላት ዝርዝር አጠናቆ በማቅረቢያ ጊዜ መስማማት አልቻሉም ።ስለዚህ በተለይ የሃገር ሽማግሌዎች ተስማምተው 275 የምክር ቤት አባላትን ማቅረብ ባለመቻላቸው ቀነ ገደቡ መገፋቱ የማይቀር ሆኗል ። »
የፊታችን ሰኞ እንደሚካሄድ ይጠበቅ የነበረው የሶማሊያ ቋሚ መንግሥት ምሥረታ እንዲገፋ የተጠየቀበት ሌላው ምክንያት የምክር ቤት አባላት ምርጫው የተቀመጡትን መስፈርቶች ያሟላ ባለ መሆኑ ነው ። እንደገና ጅብሪል ።
« ከመስፈርቶቹ አንዱ ከምክር ቤቱ መቀመጫ 50 በመቶው በሴቶች እንዲያዝ ይደነግጋል ።
የሚያሳዝነው በሃገር ሽማግሌዎቹ ከቀረበው የአባላት ዝርዝር ውስጥ 9 በመቶው ብቻ ሴቶች
ናቸው የሚገኙበት ። ይህም በመካከላቸው ፈተና የፈጠረ ጉዳይ ሆኗል ። ይህን የመሳሰሉ ሌሎችም ወሳኝ ጉዳዮች አሉ ። ማን በወንጀል ተሳትፏል ? የሚለውም እንዲሁ ይታያል ። ማን የጦር አበጋዝ ነበር ? የሚለውና ያለፈ ታሪካቸውን ማጣራትም እንዲሁ ለምክር ቤት አባላት ምርጫ አሰቸጋሪ በመሆኑ ሂደቱ አዝጋሚ የሆነ ይመስላል ። »
ጅብሪል እንዳሉት በመሰረቱ ከትናንት ጀምሮ በሶማሊያ መቀመጫ የያዘ የተሟላ ምክር ቤትና የምክር ቤት አፈ ጉባኤ ሊኖር ይገባ ነበር ። ምክር ቤቱም የሶማሊያን ፕሬዝዳንት ለመምረጥ መዘጋጀት ነበረበት ።ከ 2 ወራት በፊት የተሰየመውየምርጫ ኮሚቴ እስከ ትናንት ድረስ ከሃገር ሽማግሌዎች ያገኘው የ 135 የምክር ቤት አባላትን ስም ዝርዝር ነው ። ወደ 140 የሚሆኑ የሌሎች ተወካዮች ስም ግን እስከ ትናንት አልደረሰውም ። ከዚህ ሌላ በአባላት ምርጫ ሙስና እንዳለ ይሰማል ።
« ክሶችና የአፀፋ ክሶች ይሰማሉ ። የፓርላማ አባል ሆኖ ለመመረጥ የሚሰጠው ገንዘብ 50 ሺህ ዶላር ደርሷል የሚሉ ክሶች ይሰማሉ ። እንዚህ እስካሁን ያልተረጋገጡ ክሶች ናቸው ። ሙስናው እስከ ሲቪል ማህበራት ዘልቋል ። ሶማሊያን በጥቅሉ ስንመለከት ይህ ፈታኝ ሁኔታ ነው »
በነዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ምርጫ እንደታሰበው ሰኞ መካሄዱ አጠራጣሪ ነው ቢባልም የተመድ የሶማሊያ የፖለቲካ ጉዳዮች ቢሮ ግን ሁሉም ነገር በተያዘው እቅድ እንደሚከናወን ነው ለዶቼቬለ የተናገረው ።
ሂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ