የሶሪያ ግጭትና የተባበሩት መንግሥታት
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 18 2004
26 04 12
የሶሪያ መንግሥትና አማፂያን እርስ በርስ እየተወቃቀሱ ነዉ።ሁለቱ ወገኖች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መዕልክተኛ ኮፊ አናን ያረቀቁትን የሠላም ዕቅድ ቢቀበሉም ግጭት ዉጊያቸዉን ሙሉ በሙሉ አላቆሙ።የሶሪያ ብሔራዊ ምክር ቤት የተሰኘዉ የተቃዋሚዎች ስብስስብ የደማስቆ መንግሥት ይፈፅመዋል ያለዉን ጥቃትና ግድያ ለማስቆም የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ተሰብስቦ እንወያይ ዛሬ ጠይቋል።የሶሪያ መንግሥት ዛሬ እንዳስታወቀዉ ደግሞ ተቃዋሚዎቹ የሐማ ከተማን ለማሸበር ያዘጋጁት ቦምብ ድንገት ፈንድቶባቸዉ አስራ-ስድስት ሰላማዊ ሰዉ ገደለዋል።ግጭቱና መወነጀጀሉ የሠላም ዕቅዱንና ሶሪያ የሚሰፍረዉን የታዘቢ ሠራዊት ተልዕኮ ያጉለዋል የሚሥጋት አሳድሯል።
የሶሪያ ተፋላሚ ሐይላት የደረሱበትን ሥምምነት ገቢር ማድረጋቸዉን የሚታዘበዉ የተባበሩት መንግሥታት ሠራዊት ሶሪያ መግባት ከጀመረ ዋል-አደር አለ።የታዛቢዉ አላማ በቃል ሲናገሩት ቀላል፥ ሲሰሙት የሚጥም ጥሩ ነዉ።በሶሪያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መልዕክተኛ የኮፊ አናን ቃል አቀባይ አሕመድ ፈዉዚም እንዲሕ ቀመሩት።
«የሶሪያ መንግሥት እነዚሕ ተቆጣጣሪዎችን ከመፍቀድ ሌላ-ምርጫ የለዉም።ባለሥድስት ነጥቡን ዕቅድ ተስማምተዉበታል።ታዛቢዎቹ እንዲሠፍሩ ተስማምተዋል።ታዛቢዎችን ለማስፈርም ከነሱ (ከመነግሥት) ጋር እየሠራን ነዉ።ለታዛቢዎቹ ደሕንነት፥ለተለዋዋጭ ሥራቸዉና በነፃነት እንዲንቀሳቀሱ ዋስትና መስጠት አለባቸዉ።»
ሶሪያ ያለዉ እዉነት ግን ከተባለዉ ጋር የሚጣረስ ነዉ-የሚመስለዉ።ልዩ መልዕክተኛ ኮፊ አናን በሸመገሉት ሥምምነት መሠረት የተቀናቃኝ ሐይላት ግጭት መቆም፥ የሶሪያ መንግሥት ጦርና ከባድ ጦር መሳሪያዎች ከየከተሞቹ መዉጣት ነበረባቸዉ።እስከ ዛሬ ግን ይሕ አልተፈፀመም።ተቃዋሚ ሐይላት ዛሬ እንዳስታወቁት ደግሞ ስምምነቱ ገቢር ከሆነበት ጊዜ ጀምሮ የመንግሥት ጦር በከፈተዉ ተኩስ አንድ መቶ ሰዎች ተገድለዋል።
መንግሥት በበኩሉ ተቃዋሚዎቹ ሕዝብን እያሸበሩ፥ ተቋሟትን እያጠፉ ነዉ በማለት ይወነጅላል።የደማስቆ መንግሥት ዛሬ እንዳስታወቀዉ ተቃዋሚዎቹ ለሽብር ያዘጋጁት ቦምብ ሐማ ዉስጥ ፈንድቶባቸዉ አስራ-ስድስት ሰላማዊ ሰዎችን ገድለዋል።የሶሪያ የቅርብ ወዳጅ የምትባለዉ ሩሲያ ደማስቆ ጦሯንና ከባድ የጦር መሳሪያዋን ከከተማ አለማስወጣትዋን አረጋግጣለች።የዚያኑ ያክል ተቃዋሚዎቹ ለሽብር ማሴራቸዉን አዉግዛለች።
ግጭት ዉዝግብ ያልተለየዉን የሠላም ስምምነት ገቢራዊነት ለመታዘብ እስካሁን የዘመቱት ወታደሮች አንዳድ ሥፍራ እንቅፋት እንደቀጠማቸዉ ቃል አቀባይ አሕመድ ፈዉዚ አስታዉቀዋል።ያም ሆኖ ፈዉዚ እንደሚሉት ለሶሪያ ሰላም ወታደሮቹን ፈጥኖ ከማስፈር የተሻለ አማራጭ የለም።
«እዚያ ካሉ የኛ ሰዎች ያልተከለሰና ያልተበረዘ ዘገባ ደርሶኛል።ታዛቢዎቹ ሲንቀሳቀሱ በፀጥታ አስከባሪዎችና የሶሪያን መንግሥት በሚደግፉ ወገኖች ተንጓጠዋል።ይሕ ፍፁም ተቀባይነት የለዉም። ባስቸኳይ መቆም አለበት።ለዚሕም ነዉ የተኩስ አቁሙ ስምምነት ለንቋሳ በመሆኑ ተጨማሪ ታዛቢዎችን በተቻለ መጠን ባስቸኳይ እንድናሠፍር የምንገደደዉ።»
ሶሪያ ዉስጥ ሠወስት መቶ ሰማያዊ መለዮ ለባሾችን በሰወስት ወር ለማስፈር ነዉ የታቀደዉ። እራሳቸዉን የሶሪያ ወዳጆች ብለዉ ከሚጠሩት ሐገራት መካካል የዩናይትድ ስቴትስ፥ የብሪታንያ፥ የፈረንሳይ፥ የሳዑዲ አረቢያ፥ የቀጣርና የቱርክ ወታደሮች በሰላም ስምምነቱ ታዛቢ ሠራዊት ዉስጥ እንዳይካተቱ የሶሪያ መንግሥት ከልክሏል።
በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዩናይትድ ስቴትስዋ አምባሳደር ሱዛን ራይስ የሶሪያ መንግሥትን ተቃዉሞ ክፉኛ ተችተዉታል።የሶሪያ መንግሥት ግን የእነዚያ ሐገራት መንግሥታት አማፂያንን ይረዳሉ ወይም ያስታጥቃሉ በማለት ይወነጅላቸዋል።
ታዛቢዉ ሠራዊት ከየትም ይዝመት ከየት ሰወስት መቶ ወታደር ነዉ።ሶሪያ ጎረቤት ሊባኖስ ከዚሕ ቀደም የተደረገዉን ስምምነት ለማስከበር የሠፈረዉ ሠራዊት አንድ ሺሕ አምስት መቶ ነበር።በሕዝብ ብዛት ሊባኖስን ስድስቴ በምታጥፈዉ ሶሪያ ሰወስት መቶ ሠራዊት አስፍሮ ሠላም ይከበራል ማለት ሲበዛ አጠራጣሪ ነዉ።
በሊባኖስ የሠላም ተልዕኮ የሃያ አመት ልምድ ያላቸዉ ቲሙር ጎክሴል እንደሚሉት ግን ሠራዊቱ ግጭትን ይቀንስ እንደሁ እንጂ መፍትሔ ሰጪ አይደለም።
«ወታደሮቹ የሚጫወቱት በጣም ጠቃሚ ሚና አለ።ይሑንና መጨረሻ ላይ ሁኔታዉ ከተበለሻሻ ሁሉም እነዚያን ታዛቢዎች ይወቅሳል ብዬ እፈራለሁ።ልክ በአረብ ሊግ ታዛቢዎች እንደደረሰዉ አይነት ማለት ነዉ።ብዙ መጠበቅ የለብንም።እንደሚመስለኝ ከነዚሕ ሰዎች ከሚገባዉ በላይ እየጠበቅን ነዉ።የነሱ መገኘት በርግጥ ይጠቅማል።የግጭቱን መጠን ይቀንሰዋል።ለችግሩ ግን መፍትሔ ሰጪ አይደሉም።»
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሰ