1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሶሪያ ጦርነትና የኃያሉ ዓለም ዝግጅት

ሰኞ፣ ነሐሴ 27 2005

ፕሬዝዳት ኦባማ የሚተማመኑበትን እቅዳቸዉ ለማስፈፀም-የሚተማመኑበትን ዘመናይ ጦር ከምርጥ መሳሪያዎቹ ጋር አዝምተዋል።የሶሪያ የቅርብ ወዳጆች ሩሲያ፥ ቻይና እና ኢራን የድብደባዉን ዕቅድና ዘመቻ አጥብቀዉ ይቃወማሉ።የሩሲያዉ ፕሬዝዳት ቭላድሚር ፑቲን ከዚሕም አልፈዉ አሜሪካና የተባባሪዎችዋን አቅድ አጣጥለዉ ነቅፈዉታል።

https://p.dw.com/p/19aOK
US President Barack Obama(L) and US Secretary of Defense Chuck Hagel stand for the American National Anthem during a ceremony to commemorate the 60th anniversary of the signing of the Armistice that ended the Korean War, at the Korean War Veterans Memorial in Washington, DC, July 27, 2013. AFP PHOTO / Saul LOEB (Photo credit should read SAUL LOEB/AFP/Getty Images)
ኦባማና መከላከያ ሚንስትራቸዉ ሔግልምስል Saul Loeb/AFP/Getty Images

ሶሪያዎች ሠወስት ዓመት እንደለመዱት ይተለላለቃሉ።ለንደኖች፥ የደማስቆ መንግሥትን በኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ሕዝብን በመጨረስ ወነጀሉ፥ ሶሪያን ለመብደብ ዛቱ፥ ፎከሩና በስተመጨረሻዉ ገሸሽ-ገለል አሉ።ፓሪሶች እንደ ለንደን፥ ዋሽግተኖች ዛቱ ፎከሩና የድብደባ-ነጋሪቱ ዋሽንግተን ላይ እስኪጎሰም አድፈጠዉ ቀሩ።ዋሽግተኖች እንደፎከሩ ነዉ።ሞስኮዎች፥ ቤጂንጎች፥ ቴሕራኖች የድብደባ ፉከራ፥ ዘመቻ፥ ዝግጅቱን እንደተቃወሙ ነዉ።እነሱንም፥ ድፍን ዓለምንም የሚያስተናብረዉን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን የጋራ ማዕከልነት የተቀበለዉ የለም።የሶሪያን ጦርነት፥ የሐያሉ ዓለም የዉጊያ-ዝግጅት፥ ተቃዉሞ ያፍታ ዝግጅታችን ትኩረት ነዉ-አብራችሁኝ ቆዩ።


የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ መጀመሪያ ሶሪያን በጣሙን የሶሪያ መንግሥትን አስጠንቅቀዉ ነበር።

«በዚሕ ሠዓት እዚያ ባለዉ ሁኔታ ወታደራዊ እርምጃ እንዲወሰድ አላዘዝኩም።ግን እንደተጠቀሰዉ የኬሚካዊ እና የባዮሎጂያዊ መሳሪያ (የመጠቀም) ጉዳይ በጣም አሳሳቢ ነዉ።ይሕ ጉዳይ ሶሪያን ብቻ የሚመለከት ዓይደለም።እስራኤልን ጨምሮ ባካባቢዉ ያሉ የቅርብ ተባባሪዎቻችንን የሚያሰጋ፥ እኛንም የሚያሳስብ ነዉ።ኬሚካዊና ባዮሎጂያዊ ጦር መሳሪ ከመጥፎ ሰዎች እጅ እንዲገባ (ልንፈቅድ) አንችልም።»

ነሐሴ ሃያ-ሁለት ሺሕ አስራ ሁለት( ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎሮጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ።ቀጠሉ፥-ለአፀፋ-እንደማያመነቱ ዛቱ ቃል ገቡም።

«ለአሰድ ሥርዓትም ሆነ፥ እዚያ ላሉት ወገኖች ግልፅ ማድረግ የምንፈልገዉ ኬሚካዊ ጦር መሳሪያን (ለዉጊያ) ማንቀሳቀስ ወይም ጥቅም ላይ ማዋል ለኛ ቀይ መስመር ነዉ።ይሕ ስሌቴን ይቀይረዋል። ይሕ ጥያቄዬን ይለዉጠዋል።ይሕ ለኛ ቀይ መስመር መሆኑን ባካባቢዉ ላሉ ወገኖች በሙሉ አሳዉቀናል።ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ማንቀሳቀስና መጠቀም ከባድ አፀፋ እንደሚገጥመዉ ተናግረናል።»

ነሐሴ-ሃያ-አንድ ሁለት ሺሕ አስራ-ሰወስት።ማስጠንቀቂያ፥ ዛቻ ቃሉ ዓመት ደፈነ።ርዕሠ-ከተማ ደማስቆ አጠገብ ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ወይም መርዛማ ጋዝ መተኮሱ ተነገረ።በሌላ አባባል የፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ ቀይ መስመር መጣሱ ተወራ።

የተነገረ፥ የተወራዉ መጣራት፥ መረጋገጥ አለበት።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አጣሪዎች ቡድን እዚያዉ ደማስቆ ነበረ።ቡድኑ መርዛማዉ ጋዝ ተተኩሷል የተባለበትን አካባቢ ለመመርመር፥ የተኳሾቹን ማንነት ለማጣራት ከሶሪያ መንግሥት ተፈቅዶለት በአራተኛዉ ቀን ወደ አካባቢዉ ተንቀሳቅሷል።«ተልዕኮዉ ዛሬ ነሐሴ ሃያ-ስድስት በሰዓታት ዉስጥ በአካባቢዉ ምርመራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል።እያንዳዱ ሰዓት ትርጉም አለዉ።ተጨማሪ ጊዜ እንዲጠፋ አንፈልግም።»

ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን። ዋና ፀሐፊዉ እንዳሉት የዓለም አቀፉ ድርጅት የመርማሪዎች ቡድን በኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ተመትቷል የተባለዉን አካባቢ ለመርመር ወደ አካባቢዉ የተንቀሳቀሱት ነሐሴ-ሃያ ስድስት ነዉ።ቡድኑ ከአካባቢዉ የሰበሰበዉ መረጃ ቢያንስ በይፋ እስከ ዛሬ ተመርምሮ፥ ተጣርቶ አላበቃም።የለንደን ፖለቲከኞች ግን ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ መተኮሱን ለማወጅ፥ የፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ ቀይ መስመር መጣሱን በግልፅ ለመናገር የዓለም ማሕበር የምርመራ ዉጤት መጠበቅ አላስፈለጋቸዉም።

ለንደኖች ዓለም አቀፉን ድርጅት አይደለም የቅርብ ወዳጆቻዉን የዩናይትድ ስቴትስ አቻዎቻቸዉን ለመጠበቅ እንኳን አልታገሱም።በሁለት ሺሕ አስራ-አንድ የሊቢያዉ የርስ በርስ ጦርነት እንደተጀመረ የብሪታንያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዊሊያም ሔግ የያኔዉ የሊቢያ መሪ ኮሎኔል ሙዓመር ቃዛፊ ወደ ቬኒዙዌላ ኮብልለዋል የሚል መረጃ እንደደረሳቸዉ ተናግረዉ ነበር።ኋላ ዉሸትነቱ ሲረጋገጥ የጠየቃቸዉ የልነበረም።

በቀደምም የተባበሩት መንግሥታት የመርማሪዎች ቡድን ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ተተኩሷል ተብሎ ወደ ሚጠረጠርበት ቦታ ገና ጉዞ ሳይጀምር የታላቅዋ ብሪታንያ ታላቅ ዲፕሎማት ኮሚካዊ ጦር መሳሪያ መተኮሱን አይደለም የተኳሹን ማንነት እንደሚያዉቅም በግልፅ ተናገሩ።ነሐሴ ሃያ-ስድስት ሁለት ሺሕ አስራ-ስድስት።

«ባለፈዉ ሮብ በጣም ከፍተኛ የኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ድብደባዉን የፈፀመዉ የአሳድ ሥርዓት ለመሆኑ ለኛ በብሪታንያ መንግሥት ዉስጥ ላለነዉ ግልፅ ነዉ።መረጃዎቹ በሙሉ ወደዚያ አቅጣጫ ነዉ የሚያመለክቱት፥ የዓይን ምሥክሮቹ፥ ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ የተተኮሰዉ፥ የሥርዓቱ ሐይላት ያን አካባቢ ሲደበድቡ መሆኑ (ያንኑ) አመልካች ነዉ።»

የዘመኑ ዓለም ፖለቲካዊ ሥርዓት ቀያይሽ፥ የዓለም ሐያል፥ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መስራች፥ የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ቋሚ አባል ትልቅ ዲፕሎማት ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ መተኮሱን አይደለም፥ የተኳሹን ማንነት ጭምር አዉቀዉ፥ ማወቃቸዉን ለዓለም እያሳወቁ የዓለም አቀፉ ድርጅት ሌላ-ምርመራ ለማድረግ ሌላ ገንዘብና ጊዜ ማጥፋቱ በርግጥ አነጋገሪ፥ ግራ አጋቢም ይመመስላል።ነዉም።


ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዊሊያም ሔግ ያሉ-የሚናገሩት አነጋገሪ፥ ግራ አጋቢነቱን ማስተንተን በርግጥ አያስፈልጋቸዉም።የምክር ቤት እንደራሴዎቻቸዉን አቋም ለመገምገም እንኳን አልታገሱም፥ ወይም የማስተንተን አቅም ብስለቱ ያጥራቸዉ ነበር።እና ደማስቆ መዳራሻ በመኬሚካዊ ጦር መሳሪያ መደብደቡን፥ ደብዳቢዉ የደማስቆ መንግሥት መሆኑን በይፋ ተናግረዉ አላበቁም።የኦባማን ቃል ለማስከበር መንግሥታቸዉ ቀዳሚ መሆኑን ከራሳቸዉ ከኦባማ ቀድመዉ አረጋገጡም እንጂ።

«በሃያ-አንደኛዉ መቶ ክፍለ ዘመን፥ ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ጥፋት እንዲያደርስ፥ በዚሕ መንገድ ሰዎች እንዲገደሉ ልንፈቅ አንችልም።ያለ-አፀፋ እርምጃ አናልፈዉምም።»

ሔግ ለሚያዘምቱ፥ ለሚያስጠነቅቁት ወታደራዊ አፀፋ ከሩቅ የሚወቅስ፥ የሚጠይቃቸዉ ቢኖር እንኳ በርግጥ ደንታም አይሰጣቸዉ።ከዚያዉ ከምክር ቤት እንደራሴዎቻቸዉ ለተንቆረቆሩት ጥያቄዎች መልስ መስጠት ግን እሳቸዉም አለቃቸዉ ጠቅላይ ሚንስትር ዴቪድ ካሜሩንም ግድ ነበረባቸዉ።

«(ካሜሩን) ፕሬዝዳት አሳድ ይሕን አድርገዋል ያሉበትን ምክንያት ለቤቱ ሊያስረዱ ይችላሉ?አሰድ ኬሚካዊ ጦር መሳሪያ ይተኩሳሉ ለማለት ተጠያቃዊ ምክንያት አለመኖሩ አንዳዶችን ያሳስባል።»

አሉ-አንዱ የምክር ቤት እንደራሴ።አርብ።ሌለኛዉ ቀጠሉ፥-

«ሶሪያን መደብደብ፥በሐገሪቱ እና ባካባቢዉ ያለዉን ሁኔታ ይበልጥ ላለማባባሱ (ካሜሩን) የሚሰጡት ማረጋገጪያ አለ?»

ሌሎቹም-እንዲሁ።ጠቅላይ ሚንስትር ዴቪድ ካሜሩን እና ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዊልያም ሔግ ሶሪያን ለመደብደብ የፈለጉበትን ምክንያት ለማስረዳት፥ ለሚዥጎደጎደዉ ጥያቄ መልስ ለመስጠት ብዙ ሞከሩ።እንደራሴዎቹን ማሳመን ግን አልቻሉም።እንደ ዲሞክራሲዉ ወግ በድምፅ ብልጫ ተሸነፉ።

«በቀኝ በኩል የድጋፍ ድምፅ ሁለት መቶ ሰባ-ሁለት፥ በግራ በኩል የተቃዉሞዉ ድምፅ ሁለት መቶ ሰማንያ-አምስት።»

የብሪታንያ መንግሥት የዛተ፥ የፎከረበት የጦርነት ዘመቻ-በሐገሪቱ ምክር ቤት ድምፅ ሲሸከሽፍበት፥ እንደለንደኖች ሁሉ የደማስቆን ገዢዎችን ለመቅጣት ሲጋበዙ የነበሩት የፓሪስ መሪዎችም ከወትሮ አቋማቸዉ ሸብረክ ማለት መጀመሩ።እርግጥ ነዉ ፕሬዝዳት ፍራንሷ ኦላንድ ሌላ ሐገር ለመዉረር ከብሪታንያዉ ጠቅላይ ሚንስትር ከዴቪድ ካሜሩን የሚሻሉበት ሁለት፥ ከዩናይትድ ስቴትሱ ደግሞ አንድ ዕድል አላቸዉ።

ኦላንድ እንደ ካሜሩን-የቶኒ ብሌር፥ እንደ ኦባማ የጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ እኩይ ምግባር መጥፎ ዉርስ የለባቸዉም።ጠቅላይ ሚንስትር ካሜሩን ራሳቸዉ ባለፈዉ አርብ እንዳሉት የምክር ቤት እንደራሴዎቻቸዉ የሶሪያዉን የዘመቻ ዕቅድ ዉድቅ ያደረጉት የቀድሞዉ የሐገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር ቶኒ ብሌር እና የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳ ጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ ኢራቅን በሐሰን መረጃ ወርረዉ በየሐገራቸዉም፥ በኢራቅም በድፍን ዓለምም ያደረሱት ጥፋት በመኖሩ ነዉ።

ኦላንድ ከሳርኮዚ ሊቢያን መደብደብን ቢወርሱም፥ ከዣክ ሺራክ ግን የኢራቅን መወረር ተቃዉሞ እንጂ የወረራ ጥፋት ዉድቀትን አልወረሱም።ይሕ-ከካሜሩንም ከኦባም ይለያቸዋል።ሶሪያን ለመደብደብ ከካሜሩን በሌላም ጉዳይ ይለያሉ፥ምክር ቤታቸዉን ሳያማክሩ ሌላ ሐገር የሚወር ጦር ቢያንስ ለአራት ወራት ማዝመት ይችላሉ።

ያም ሆኖ የብሪታንያ ምክር ቤት የዘመቻዉን ዕቅድ ዉድቅ ካደረገ በሕዋላ ፓሪሶች ያንድ ሳምንት ፉከራ-ዛቻቸዉን ማቀዝቀዝ ግድ ሆኖባቸዋል።የፈረንሳይ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ማኑኤል ቫል ትናንት እንዳሉት ደግሞ ፓሪሶች ከእንግዲሕ የዋሽግተኖችን ኮቴ ማዳመጥ ግድ አለባቸዉ።

«አዲስ ምዕራፍ ዉስጥ እንገኛለን።ብሪታንያ ጣልቃ እንዳትገባ የሐገሪቱ ምክር ቤት ከወሰነ በሕዋላ፥ ማክበር የሚገባን አማራጭ አለ።ፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ ምክር ቤታቸዉን ለማማካር መወሰናቸዉን ማክበር አለብን።ላሁኑ ጊዜ አለን።ይሕን ያለንን ጊዜ ጉዳዩ እንዲንቀሳቀስ ልንጠቀምበት ይገባል።»

ፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ-የፕሬዝዳትነትነቱን ሥልጣን ከያዙ ወዲሕ ቀዳሚያቸዉ ፕሬዝዳት ጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ ያወደሙትን የሐገራቸዉን ምጣኔ ሐብት ለማሻሻል፥ ያጠፉትን የአሜሪካን ሥም፥ ዝና ክብር ለመመለስ በብዙ ጉዳይ ቃል ገብተዋል።ጥቂቱን እንጠቅስ፥-የእስራኤልና የፍልስጤሞችን ግጭት ዉዝግብ ለማስወገድ ዋሽግተን አይደለም ካይሮ-ድረስ ወርደዉ ቃል ገብተዉ ነበር።ከየሐገሩ ታፍሰዉ ያለፍርድ በርካታ ሰዎች የታሰሩበትን የኹዋንታናሞ ማጎሪያ ጣቢያን በአንድ ዓመት ጊዜ ለመዝጋት ቃል ገብተዉ ነበር።

አምባገነኖች በየሕዝባቸዉ ላይ የሚፈፅሙትን ግፍ እና በደል ማስቆም ባይችሉ እንኳን መስተዳድራቸዉ ከአምባገነኖች ጋር እንደማይተባበር ቃል ገብተዉ ነበር።የዓለም ብቸኛ ልዕለ-ሐያል ሐገራቸዉ አቅም ጉልበት ሐብቷን በዓለም ሠላም ለማስፈን እንድታዉለዉ ለማድረግ እንደሚጥሩ ቃል ገብተዉ ነበር።ኦባማ ለገቡት በጎ ቃል፥ ተስፋ የዓለምን ታላቅ የሠላም ሽልማት ኖቤልን ተሸልበዉበታል።

ከጠቀስናቸዉ መሐል ግን አንዱንም ቃል በከፊል እንኳን ገቢር አላደረጉም።ሶሪያ ላይ በሐሳብ ያሰመሩትን ቀይ-መስመር ለማስከበር የገቡትን ቃል እንደማያጥፉ ግን በቀደም በድጋሚ አረጋግጠዋል።

«ጥንቃቄ ከተሞላበት እሳቤ በሕዋላ ዩናይትድ ስቴትስ በሶሪያ ሥርዓት የተመረጡ ኢላማዎች ላይ ወታደራዊ እርምጃ እንድትወስድ ወስኛለሁ።ይሕ ማብቂያዉ የማይታወቅ ጣልቃ ገብነት አይሆንም።እግራችንን ሶሪያ ምድር አናሳርፍም።ከዚሕ ይልቅ እርምጃችን በጊዜና በመጠን የተወሰነ ነዉ።ይሁንና የአሰድ ሥርዓት ኬሚካዊ ጦር መሳሪያያ በመጠቀሙ ተጠያቂ ማድረግ፥ እንዲሕ አይነት ባሕሪዉን መግታት፥አቅሙን ማዳካም እንደምንችልም እተማመናለሁ።»

ፕሬዝዳት ኦባማ የሚተማመኑበትን እቅዳቸዉ ለማስፈፀም-የሚተማመኑበትን ዘመናይ ጦር ከምርጥ መሳሪያዎቹ ጋር አዝምተዋል።የሶሪያ የቅርብ ወዳጆች ሩሲያ፥ ቻይና እና ኢራን የድብደባዉን ዕቅድና ዘመቻ አጥብቀዉ ይቃወማሉ።የሩሲያዉ ፕሬዝዳት ቭላድሚር ፑቲን ከዚሕም አልፈዉ አሜሪካና የተባባሪዎችዋን አቅድ አጣጥለዉ ነቅፈዉታል።

«እንዲያዉ ተራ ግምት እንኳን ይመስከራል።የሶሪያ መንግሥት ጦር ድል እየተቀዳጀ ነዉ።ባንዳድ አካባቢዎች አማፂያኑን ከቧል።በዚሕ ሁኔታ ለረጅም ጊዜ «የምዕራቡ) ጦር ጣልቃ እንዲገባ ለሚጠይቁት ሐይላት ያሸናፊነት ካርድ መሸለም ፍፁም ትርጉመ-ቢስነት ነዉ።በተለይ የዓለም አቀፉ መርማሪ ቡድን በመተለሰበት ባሁኑ ወቅት እርምጃ ይወሰድ መባሉ ከምንም አይነት ተጠይቅ ጋር አይጣጣምም።ሥለዚሕ በሶሪያዉ ጦርነት ሌሎች ጣልቃ እንዲገቡ ለሚፈልጉ ሐይላት፥ ከዓለም አቀፉ ጠንካራ ሐይል-በተለይ ከአሜሪካ ድጋፍ የሚሹ ወገኖች ጠብ አጫሪነት ብዬ ነዉ የማምነዉ።»

የሰማቸዉ እንጂ-የተቀበላቸዉ ምዕራባዉ ሐይል የለም።የዩናይትድ ስቴትስ ቦምብ ሚሳዬል ሶሪያን የሚያነደዉን ዉጊያ የሚያጋጋምበት ዕለት እየተቆጠረ ነዉ።ሶሪያም ኢራቅን፥ አፍቃኒስታንን፥ ፍልስጤም እስራኤልን፥ ሊቢያን ለመቀየጥ-ትጣደፋለች።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Russia's President Vladimir Putin looks on during a meeting with journalists in the far eastern city of Vladivostok, August 31, 2013. Putin said on Saturday that it would be "utter nonsense" for the Syrian government to use chemical weapons when it was winning the war, and urged U.S. President Barack Obama not to attack Syrian forces. REUTERS/Alexei Nikolskyi/RIA Novosti/Kremlin (RUSSIA - Tags: POLITICS HEADSHOT) ATTENTION EDITORS - THIS IMAGE HAS BEEN SUPPLIED BY A THIRD PARTY. IT IS DISTRIBUTED, EXACTLY AS RECEIVED BY REUTERS, AS A SERVICE TO CLIENTS
ፑቲንምስል Reuters
A UN convoy of vehicles, carrying inspectors investigating allegations of the Syrian regime's use of chemical weapons, drives through the Lebanese village of Taanayel after crossing into Lebanon from Syria on August 31, 2013. The team of UN inspectors left Damascus after completing their probe into a suspected chemical weapons attack near Damascus, an AFP reporter said. AFP PHOTO/ANWAR AMRO (Photo credit should read ANWAR AMRO/AFP/Getty Images)
የተመድ መርማሪዎችምስል AFP/Getty Images
Britain's Prime Minister David Cameron is seen addressing the House of Commons in this still image taken from video in London August 29, 2013. Cameron said on Thursday it was "unthinkable" that Britain would launch military action against Syria to punish and deter it from chemical weapons use if there was strong opposition at the United Nations Security Council. REUTERS/UK Parliament via Reuters TV (Foto: Reuters) / Eingestellt von wa
ካሜሩንምስል Reuters
Blick auf die Innenstadt von Damaskus, aufgenommen am 07.10.2005. Foto: Oliver Berg +++(c) dpa - Report+++
ደማስቆምስል picture-alliance/dpa/dpaweb

ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ












ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ