1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሽብር ስጋት ያጠላበት የ2016 ዓ.ም. አቀባበል

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 22 2008

ዘመኑን በጎርጎሮሳዊው ቀመር የሚያሰላው አለም አዲሱን 2016 ዓም በሪችት በፊሽታ በፈንጠዝያ ሻምፓኝ በመራጨትና በሙዚቃ ድግሶች ተቀብሎታል ። ሆኖም በአብዛኛው የዓለም ክፍል በተለይም በአውሮፓ በዓሉ የተከበረው በሽብር ጥቃት ስጋት ድባብ ውስጥ ነው ።

https://p.dw.com/p/1HWvV
Berlin, Neujahrsfeiern
ምስል Reuters

[No title]

በአውሮፓ ህብረት መቀመጫ ብራሰልስ የአዲሱ ዓመት አቀባበል እንደተለመደው በርካታ ህዝብ በሚሰበሰብበት የአደባባይ የርችት ተኩስና የሙዚቃ ትርኢት አልተከበረም። በ2015 የሽብር ጥቃቶች በደረሱባት በፓሪስም እንዲሁ በዓሉ የቀዘቀዘ ነበር። በሌሎች የአውሮፓ ትላልቅ ከተሞችም በዓሉ የተከበረው እከዛሬ ባልታየ ከፍተኛ የፀጥታ አጠባበቅ ነበር። በፈረንሳይ ትናንት 100 ሺህ ፖሊሶች ለጥበቃ የተሰማሩ ሲሆን የቤልጂግ ፓሊስ ደግሞ ሰሞንኑ ሲያደርግ እንደከረመው ተጠርጣሪ አሸባሪዎችን ሲያሳድድ ነበር።

በጀርመን ደግሞ አዲሱ ዓመት ከመግባቱ ከአንድ ሰዓት አስቀድሞ በደቡባዊ ጀርመንዋ በሙኒክ ከተማ ፖሊስ የአጥፍቶ ጠፊ የሽብር ጥቃት ሊደርስ ይችላል ብሎ የሰጋባቸው ሁለት የባቡር ጣቢያዎች ከሰው ነጻ እንዲሆኑ አደርጎ ነበር ። ፖሊስ ጥቃቱን አሲረዋል ብሎ የጠረጠራቸውን 7 ሰዎች እያደነ ነው። ፖሊስ በዚህ መንስኤ በሙኒክ ጥብቅ የጸጥታ ማስጠንቀቂያ አውጥቶ የነበረ ቢሆንም ዛሬ አንስቶታል። በአውሮፓ ትላልቅ ከተሞችና በዩናይትድ ስቴትስ የአዲስ ዓመት አቀባበል ምን እንደሚመስል የሚያስቃኙ ቅንብሮቻችንን ነው የምናስከትለው ። በብራሰልስ በዓሉ እንዴት እንዳለፈ ዘጋቢያችንን ገበያው ንጉሴን ስቱድዮ ከመግባቴ በፊት ጠይቄው ነበር።

ብሪታንያም አዲሱን ዓመት የተቀበለችው ከእስከዛሬው በተለየ ጥብቅ የፀጥታ ጥበቃ መሆኑን የለንደንዋ ወኪላችን ሃና ደምሴ ዘግባለች።

እዚህ ጀርመን በአዲስ አመት ዋዜማ በባየር ሙኒክ ከተማ የሽብር ጥቃት ሊሰነዘር ይችላል በሚል ስጋት የተጣለው ማስጠንቀቂያ ተነስቷል። ፖሊስ የሽብር ጥቃት ሊደርስባቸው ይችላል ብሎ በመስጋቱ ሥራ ያቆሙት የባቡር ጣቢያዎችም አገልግሎቶች መስጠት ጀምረዋል። የሙኒክ ፖሊስ ከአጋር የደህንነት ተቋሞች የሽብር ጥቃት ሊሰነዘር እንደሚችል ጥቆማ ቢደርሰዉም እስካሁን የተያዘ ተጠርጣሪ የለም። እሸቴ በቀለ ዝርዝሩ ዘገባ አዘጋጅቷል።

ከአውሮፓ የኣትላንቲክ ውቅያኖስን አቋርጠን ወደ ዩናይትድ ስቴትስ ስንሻገር እዚያም በሃገሪቱ ትላልቅ ከተሞች በዓሉ በተመሳሳይ የፀጥታ ጥበቃ መካሄዱን ወኪላችን ናትናኤል ወልዴ ዘግቧል። በሃገሪቱ ትልቅ የንግድ ከተማ ኒውዮርክ በታይምስ ስክዌር አደባባይ ከ1 ሚሊዮን በላይ የተገመተ ህዝብ በ ፌሽታና ሪችት በመተኮስ ባከበረው በዓል ላይ በሺህ የሚቆጠሩ ፀጥታ አስከባሪዎች ተሰማርተው ነበር ።

ዘገባዎቹን ለማድመጥ ከታች የሚገኙትን የድምጽ ማዕቀፎች ይጫኑ

ገበያው ንጉሴ

ሃና ደምሴ

እሸቴ በቀለ

ናትናኤል ወልዴ

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ