የተገን ጠያቂዎች መብትና ረቂቁ ደንብ
ማክሰኞ፣ መስከረም 15 2005የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ የሲቪል ነፃነት ኮሚቴ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ባካሄደው ድምፅ አሰጣጥ አሁን በሚሰራበት የአውሮፓ ህብረት የስደተኞች አቀባበልና አያያዝ ላይ ማሻሻያዎችን ያደረገ ረቂቅ ደንብ አጽድቋል ። ረቂቁ ተገን ጠያቂዎች የሚያዙበትን ምክንያት የሚገድብ ፣ የሚያዙባቸው ሁኔታዎች እንዲሻሻሉ የሚጠይቅና ከለላ እንዲሰጣቸው ባመለከቱበት አገር ሥራ የሚጀምሩበትን የጊዜ ገደብ ከቀድሞው የሚያሳጥር ነው ። ከዚሁ ጋርም ስለ ሚያስፈልጓቸው የጤና ምርመራዎች አስቀድሞ ጥናትና ክትትል ማድረግንም ያካትታል ። ከረቂቅ ደንቡ የተወሰነው ክፍል ሲወደስ አንዳንዱ ክፍል ደግሞ ተተችቷል ። ። እጎአ የ 2003 ቱ የአውሮፓ ህብረት የተገን አሰጣጥ ደንብ ላይ ማሻሻያ ያደረገው አዲሱ ረቂቅ የአውሮፓ ህብረት ምክር ቤትን ስምምነት አግኝቷል ። የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ እንዳስታወቀው ከህብረቱ ምክር ቤት ጋር በረቂቅ ደንቡ ላይ ስምምነት ላይ የተደረሰው ከ4 አመታት ድርድር በኋላ ነው ። በረቂቁ ውስጥ ከተካተቱት ማሻሻያዎች አንዱ ተገን ጠያቂዎች የሚያዙበትን አግባብ የሚመለከተው ክፍል ይገኝበታል ። ረቂቁ የተገን ጠያቂዎችን አቀባበል ና አያያዝ ደረጃዎች ምን መሆን እንደሚገባቸውም በዘረዘረበት ደንብ ተገን ጠያቂዎች በሚከተሉት 6 ምክንያቶች ብቻ መያዝ እንዳለባቸው አስቀምጧል ። በዚሁ መሰረት አንድ ተገን ጠያቂ የሚያዘው
አንደኛ የተገን ጠያቂውን ማንነት ለማጣራት ፣ ሁለተኛ ዓለም አቀፍ ከለላ እንዲሰጠው ወይም እንዲሰጣት ያስገባው ያስገባችው ማመልከቻ የያዛቸውን ጉዳዮች ለማጣራት ፣ ሶስተኛ
ወደ አንድ አባል ሃገር ግዛት የመግባት መብት ላይ ውሳኔ ለመስጠት
አራተኛ ብሄራዊ ፀጥታንና ስርዓትን ለማስጠበቅ ፣ አምስተኛ ተገን ጠያቂው ዓለም አቀፍ ጥበቃ እንዲደረግለት ያመለከተው ወደ ሃገሩ እንዳይመለስ ለማዘግየት አሰቦ ነው ተብሎ ከታመነበት ወደ ሃገሩ እንዲመለስ ዝግጅት ለማድረግ
6 ተኛ በደብሊኑ ስምምነት መሠረት ተገን ጠያቂውን ወደ ሌላ የህብረቱ አባል አገር ማስተላለፍ ሲያስፈልግ ነው ። ይሁንና ለተገን ጠያቂዎች መብት የቆሙ አንዳንድ ድርጅቶች ማሻሻያው አሁንም ግልፅ ባለመሆኑ አሳስቧቸዋል ። ማራይ ፔልሰር መንግስታዊ ባልሆነው ለተገን ጠያቂዎች መብት በሚታገለው ፕሮአዙል በተባለው ድርጅት የህግ ባለሞያ ናቸው ። በርሳቸው አስተያየት በረቂቁ ደንብ የተቀመጡት ተገን ጠያቂዎች የሚታሰሩባቸው ምክንያቶች ግልፅ አይደሉም ። ፔልሰር እንደሚሉት በማሻሻያው የተዘረዘሩት ምክንያቶች በአንዳንድ ሃገራት ተገን ጠያቂዎች በዘፈቀደ መታሰራቸውን ህጋዊ የሚያደርግ ነው ።
እንዳለባቸው አስቀምጧል ። በዚሁ መሰረት አንድ ተገን ጠያቂ የሚያዘው
« ሰዎች እንዲታሰሩ በምክንያትነት የተጠቀሱት 6 ጉዳዮች ለሚያዙት ሰዎች ሁሉ ምክንያት አድርጎ ለማቅረብ በጣም አስቸጋሪ መሆኑን አይተናል ። ምክንያቱም ይህ የሚታሰሩበት ምክንያት በብዙ ሃገሮች ለምሳሌ እንደ ሃንጋሪና ግሪክ በመሳሰሉት ሃገራት ህጋዊ አፈፃፀሙ አይከበርም ወይም በነዚህ ሃገሮች ሰዎችን በዘፈቀደ ለማሰር መሣሪያ ነው የሆነው ። »
በአሁኑ ሰአት እጅግ ብዙ ስደተኞችን በማስተናገድ ግንባር ቀደሙን ስፍራ ከሚይዙት የአውሮፓ ህብረት አባል አገሮች አንዷ ግሪክ ናት ። በግሪክ የስደተኞች አያያዝ እጅግ አስከፊ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባላት በአካል ተገኝተው ያረጋገጡት ጉዳይ ነው ። በማልታም እንዲሁ ችግሩ የከፋ ነው ። ረቂቅ ደንቡ በነዚህ ሃገራት ለውጥ ማምጣቱ ቀርቶ ተገን ጠያቂዎች እንዲገላቱ ያደርጋል ባይ ነው ፕሮአዙል ። እ.ጎ.አ የ 2003 አመተ ምህረቱ የአውሮፓ ህብረቱ ደንብ ተገን ጠያቂዎች የሚታሰሩባቸውን ምክንያቶች በግልፅ አላስቀመጠም ። በዚህ የተነሳም ተገን ጠያቂዎች የሚያዙበት ሁኔታ አተረጓጎም ለአባል ሃገራት ክፍት የተተወ ነበር ። በረቂቅ የተገን ጠያቂዎችን አያያዝ በተመለከተም በአጠቃላይ እንደ መመሪያ የተቀመጠው በተለዩ የማቆያ ስፍራዎች መያዝ እንዳለባቸው ነው ። ሆኖም አንድ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገር አመልካቹን በዚህን መሰል ማዕከል ማቆየት ካልቻለ ና ግለሰቡን ወህኒ ቤት ለማስገባት ከተገደደ አመልካችዋ ወይም አመልካቹ ከሌሎች እስረኞች በተለየ ስፍራ መያዝ እንዳለባቸው ቦታውም አየር ማግኝት የሚችሉበት ሊሆን እንደሚገባ በአዲሱ ረቂቅ ተመልክቷል ። ከዚሁ ጋርም አመልካቾች መብቶቻቸውንና ግዴታዎቻቸውን በሚረዱበትና ይረዳሉ ተብሎ በሚታሰብበት ቋንቋ ሊብራራላቸው እንደሚገባም በማሻሻያው ተጠቅሷል ።
ስምምምነት ላይ በተደረሰበት በአዲሱ ደንብ መሰረት ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆች የሚታሰሩት እማራጭ ሲጠፋ መሆን እንደሚገባው ሃሳብ ይሰጣል ። በማሻሻያው እንደተጠቀሰው ሊታሰሩ የሚችሉት እጅግ በተለየ ምክንያት መሆን ነው ያለበት ።የሚያዙት ለአጭር ጊዜ መሆን ሲገባው በተቻለ ፍጥነት ተለቀው አመቺ ወደ ሆነ ስፍራም መወሰድ ይኖርባቸዋል ። እነዚህ ልጆች እስር ቤት ውስጥ መያዝ እንደሌለባቸው ከአዊቂዎች ተለይተው የሚያስፈልጓቸው ነገሮች ባሉበት ስፍራ መያዝ እንደሚገባቸው ነው በረቂቁ የሰፈረው ። ሆኖም እንደ ፕሮአዝዩልዋ ፔርሰል የተሻሻለው ደንብ አስገዳጅ ባለመሆኑ ያን በጥሩ ጎኑ የሚነሳ አይደለም
« የልጆችን አያያዝ በተመለከተ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት የኮሚሽኑን ስምምነት እንዲቀበሉ ሃሳብ ከመስጠት ውጭ ጠንካራ ወይም አስገዳጅ ደንብ ስለሌለው ለአካለ መጠን ያልደረሱ ተገን ጠያቂዎችን ለመንከባከብ ምንም አይነት የተወሰደ ጥሩ እርምጃ አላየሁም ። »
እንዳለባቸው አስቀምጧል ። በዚሁ መሰረት አንድ ተገን ጠያቂ የሚያዘው
ፌስቱስ ታናዊ ካካሜሩን ወደ ጀርመን የተሰደደ ተገን ጠያቂ ነው ። ከጀርመን መዲና በርሊን ወጣ ብሎ በሚገኝ የተገን ጠያቂዎች መጠለያ ውስጥ ነው የሚኖረው ። ለጥገኝነት ላስገባው ማመልከቻ የጀርመን ባለሥልጣናት የሚሰጡትን ውሳኔ በመጠባበቅ ላይ ይገኛል ። የጀርመን መንግሥት ከለላ እንዲሰጠው ካመለከተ አንድ አመት ሆኖታል ። እስካሁን ግን የሥራ ፈቃድ የለውም ። ባለፈው ሳምንት የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ባወጣው አዲስ ረቂቅ ደንብ መሠረት ወደፊት ተገን ጠያቂዎች በአንድ የህብረቱ አባል ሃገር አለም አቀፍ ከለላ እንዲሰጣቸው ካመለከቱ ከ 9 ወር በኋላ ሥራ እንዲጀምሩ ይፈቅዳላቸዋል ። አሁን በሚሰራበት ደንብ ግን ተገን ጠያቂዎች መሥራት የሚችሉት ከለላ እንዲሰጣቸው ካመለከቱ ከአንድ አመት በኋላ ነው ። በዚህ መሰረት ካሜሩናዊው ፌስቱስ ሥራ መያዝ ይፈቀድለታል ። ሆኖም እርሱ ለሚያመለክትበት ሥራ የአውሮፓ ህብረት ዜጋ ካልተገኘ ነው ሥራው ሊሰጠው የሚችለው ። ይህ በደንቡ ላይ የሰፈረው አሰራር ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው ግን በየሃገሩ ህግና ደንብ መሰረት በሚገኘው የሥራ ፈቃድ መሠረት መሆኑ የተቀመጠውን ደንብ በአባል ሃገራት በሙሉ ተግባራዊ መሆኑን አጠያያቂ ማድረጉ አልቀረም ። ያም ሆኖ ፕሮአዝዩል ይህ ትልቅ እርምጃ ነው ሲል አወድሶታል ። የጀርመን መንግሥትም ሌሎች ሃገራት ማሻሻያውን እንዲደግፉ ግፊቱን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል
« ጀርመን መንግሥታቱ ለስደተኞች ድጋፍ የመስጠቱን ኃላፊነት እንዲወስዱ ግፊት የማድረጉን መርህ ማጠናከር በሚለው አቋሟ መፅናት አለባት ። »
አዲሱ ረቂቅ ማሻሻያ የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ የነፃነት ኮሚቴ 45 አባላትን ድጋፍ ሲያገኝ 9 ተቃውመውታል ። በ 4 ደግሞ በድምፀ ተአቅቦ አልፈውታል ። ረቂቁ ህግ ሆኖ ከመውጣቱ በፊት አባል ሃገራት ስምምነት ላይ የተደረሰበትን ማሻሻያ ማፅደቅ ይኖርባቸዋል ። ከዚያም ስምምነቱ ወደ ፓርላማው ተመልሶ የጎርጎሮሳውያኑ 2012 አመተ ምህረት ከማብቃቱ በፊት ድምፅ ይሰጥበታል ተብሎ ይጠበቃል ። ማሻሻያው ከፀደቀ በኋላ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ህጉን በብሄራዊ ህጋቸው ውስጥ ለማካተት የ 2 አመት ጊዜ ይሰጣቸዋል ።
ሂሩት መለሰ
ሸዋዮ ለገሰ