1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«የታፈነዉ» የተቃዉሞና እንቅስቃሴዋ የተቋረጠዉ ጎንደር

Merga Yonas Bulaሰኞ፣ ነሐሴ 9 2008

ባሳለፍነዉ ሳምንት መጨረሻ ላይ በአማራ ክልል በተለያዩ ቦታዎች ተቃዉሞ ሰልፍ መጠራቱን ማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ይጠቁማሉ።

https://p.dw.com/p/1JifN
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Deutsch

[No title]

በክልሉ በስተ ምዕራብ የምትገኘዉ የሃዊ ብሄረሰብ አስተዳደር እስከ ደጀን ድረስ፣ ምሥራቅ ደግሞ ሰሜንና ደቡብ ወሎን ጨምሮ የኦሮሞ ብሄር አስተዳደር እንዲሁም ሰሜን ሸዋን ይዞ እስከ ደብረ ብርሃን ድረስ «ያልተፈቀዱ፣ እዉቅናና ባለቤት የሌላቸዉ» ሰልፎች ተጠርተዉ እንደ ነበር ነገር ግን ሳይካሄዱ መቅረታቸዉን የክልሉ መንግሥት የኮሙኒኬሼን ኃላፊ አቶ ንጉሡ ጥላሁን ለዶቼ ቬሌ አረጋግጠዋል።


በሌላ በኩል ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ የወልድያ ነዋሪ የሆኑት ግን ተቃዉሞዉ ሳይካሄድ ቀረ ይባል እንጅ የመንግስት ታጣቂ ኃይል በወሰደዉ የእስራት እና የአፈና ርምጃዎች የማኅበረሰቡ ጥያቄ ሳይሰማ ቀርቷል ይላሉ።

ይህን ጉዳይ አስመልክቶ አቶ ንጉሡ አስረዋል፣ አፍነዋል የሚሉት ሰላምን የማይፈልጉ፣ የሰዉ ሕይወት እንዲጠፋ፣ ንብረትም እንዲወድም የሚፈልጉ ናቸዉ ካሉ በዋላ፤ የተወሰደዉ ርምጃም የኅብረተሰቡን ሰላምና ደህንነት ለመጠበቅ እንጅ ኅብረተሰቡ ላይ ጭንቀትና ሽብር ለመልቀቅ አይደለም ይላሉ።


በሰሜን ወሎ የመቄት ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ሌላዉ ስማቸዉ እንዳይጠቅስ የፈለጉ እማኝ፤ በትናንትናዉ ዕለት ከሦስት ሰዓት ጀምሮ እስከ 7:30 ድረስ ሰላማዊ ሰልፍ ሲካሄድ እንደነበር ነዉ የገለጹልን።


ይህ በእንዲህ እንዳለ በጎንደር ከተማ ከትናንት ጀምሮ እንቅስቃሴዉ እንደቀዘቀዘ፤ ኅብረተሰቡ ከቤቱ እንደማይወጣ፤ መጓጓዣም እንደሌለ እየተነገረ ነዉ። አቶ ንጉሡ በከተማዋ የትራንስፖርት የመቆም አስማምያ ታይቶበታል ይላሉ።

የዶቼ ቬለን የፌስ ቡክ ገጽ ተከታታዮችን በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን ጠይቀን ነበር፣ አንዳንዶቹ ማኅበረሰቡ «ሰላም ፈላጊና አስተዋይ ስለሆነ ነው ለተቃዉሞ ያልወጣው» ሲሉ ሌሎች ደግሞ «ይሄ ነገር ህዝቡ መንግሥት ስለተዘጋጀበት ለማዘናጋት የተደረገ ይመስላል፤ እና ይሄ የህዝብ ብልጠት ተመችቶናል» እንዲሁም «የተሠለፈው የመንግሥት ኃይል ስለነበረ ህዝቡ መውጣት አልቻለም» የሚሉ አስተያየቶችን አጋርተዉናል።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሰ