1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የናይጀርያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተፎካካሪዎች

ሐሙስ፣ የካቲት 7 2011

የፊታችን ቅዳሜ የካቲት 10  በናይጀርያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ይካሄዳል። 72 እጩዎች በቀረቡበት በዚህ ምርጫ የሐገሪቱ ሁለት አንጋፋ ፖለቲከኞች በግንባር ቀደምትነት ይወዳደዳሉ ተብሎ ይጠበቃል። ወጣት ፖለቲከኖች ግን ለሃገሪቱ ከፍተኛ ሥልጣን በሚደረገዉ ዉድድር ከጨዋታ ዉጭ ተደርገዋል ተብሎአል።   

https://p.dw.com/p/3DP9X
Muhammadu Buhari und Atiku Abubakar
ምስል Atiku Media Office

በምርጫዉ ዘንድሮም ወጣት ፖለቲከኞች ገሸሽ ተደርገዋል

በሕዝብ ብዛት ከአፍሪቃ አንደኛ በሆነችዉ ናይጀርያ ዘንድሮ በሚካሄደዉ ምርጫ ወጣት እና አዲስ የተባሉት ፖለቲከኞች ለሃገሪቱ ከፍተኛ ሥልጣን በሚደረገዉ ዉድድር ከጨዋታ ዉጭ ተደርገዋል ተብሎአል።   

200 ሚሊዮን ግድም  ነዋሪዎች ያላትና በአፍሪቃ በሕዝብ ብዛት ቀዳሚዉን ሥፍራ ይዛ የምትገኘዉ ናይጀርያ የፊታችን ቅዳሜ በምታካሂደዉ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ 84 ሚሊዮን ሕዝብ ድምፅ ለመስጠት ተመዝግቧል።  ይህ ቁጥር ከዓለፈዉ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ጋር ሲወዳደር 18 በመቶ እንደሚበልጥ ነዉ የተነገረዉ። ምርጫዉ እየተቃረበ ሲመጣ «APC» All Progressives Congress በመባል የሚጠራዉ የናይጀርያ ገዢ ፓርቲ እና ሕዝባዊ ዲሞክራቲክ ፓርቲ « PDP » በመባል የሚታወቀዉ ተቃዋሚ ፓርቲ መካከል የሚታየዉ ዉጥረት እየጋለ መጥቶአል።  ባለፉት ቀናት ደቡብ ምስራቅ ናይጀርያ በሁለቱ ተቀናቃኝ ወገኖች መካከል በተፈጠረ ግጭት አምስ ት ሰዎች ሞተዋል። የናይጀርያ ተቃዋሚ ፓርቲ ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ መዲና አቡጃ ላይ ላደርግ የተዘጀሁት የምርጫ  ቅስቀሳ  መንግሥት አስተጓጉሎብኛል፤ «ፓሌትዊ» በተባለ ግዛት በሽዎች የሚቆጠሩ የድምፅ መስጫ ካርዶች ከጥቅም ዉጭ ተደርገዋል ሲል መንግሥትን ይከሳል።  72 እጩዎች በቀረቡበት በቅዳሜዉ የናይጀርያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፤ ስድስት ሴት እጩዎች ይሳተፋሉ።  ከሴት እጩዎች መካከል ኦቢ ኤዚክቬስሊ የተባሉ የኤኮኖሚ  ባለሞያዋና  ከቺቦክ በቦኮሃራም በመቶዎች የሚቆጠሩ ታዳጊ ሴቶች ተገቱ መባላቸዉን ተከትሎ «BringBackOurGirls»  « ሴት ልጆቻችን መልሱ» በሚል በዓለም ደረጃ ብዙዎች የተሳተፉበት ንቅናቄ መስራች ይገኙበታል።       

Präsidentschaftswahl Nigeria Wahlplakate
ምስል DW/K. Gänsler

በዘንድሮዉ የናይጀርያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዋንኞቹ ተፎካካሪዎች በስልጣን ላይ የሚገኙት ፕሬዚዳንት መሃመዱ ቡሃሪና የዋነኛዉ ተቃዋሚዉፓርቲ መሪ አቲኩ አቡበከር ናቸዉ። ቡሃሪ ተቃዋሚ ፓርቲን ወክለዉ በሃገሪቱ በጎርጎረሳዉያኑ 2015  የተካሄደዉን ምርጫ አሸንፈዉ ነዉ መንበሩን የተቆጣጠሩት። የ76 ዓመቱ ፕሬዚዳንት በምርጫ ወቅት ከገቡት ቃል  ብዙዉ አልተገበሩም በመባል ይወቀሳሉ።የቡሃሪ ጤናም አስተማማኝ አይደለም።ባለፉት ዓመታት ለብዙ ወራቶች በዉጭ ሃገር ህክምና ሲከታተሉ መቆየታቸዉ ይታወቃል። በኒዮርክ ዩንቨርስቲ የፖለቲካ ጉዳይ ምሁር ናይጀርያዊዉ ኦልያኒካ አጀላ እንደሚሉት ፤ ፕሬዚዳንቱ ጤንነት ስለሌላቸዉ መሪነት ቦታ ላይ መስራት አይችሉም።    

Präsidentschaftswahl Nigeria Aliyu Rabe Daura
ምስል DW/K. Gänsler

«ብዙ ሰዎች የመምራት አቅም  የለዉም ብለዉ ያምናሉ። በሃገሪቱ ዉስጥ ስልጣን ላይ የሚገኘዉ ሳይሆን በመንግሥት ዉስጥ የሚገኙ ጥቂት ሰዎች ናቸዉ መንግሥቱን እያስተዳደሩ ያሉት።»

የፕሬዚዳንት መሃመዱ ቡሃሪ ዋና ተፎካካሪ አቲኩ አቡበከር ናቸዉ።አቡበከር በናይጀርያ እስከዛሬ በተካሄደ አምስት ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በእጩነት ቀርበዉ ስኬት አላገኙም።  በጎርጎረሳዉያኑ 2015 በተካሄደዉ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በመለያ ምርጫ አሁን በስልጣን ላይ በሚገኙት በቡሃሪ ተሸንፈዋል። አቡበከር ቱጃርም ናቸዉ። የፖለቲካ ጉዳይ ምሁሩ ናይጀርያዊዉ  ኦልያኒካ አጃላ እንደሚሉት በኤኮኖሚዉ ዘርፍ አቲኩ አቡበበከር የዳበረ ልምድ አላቸዉ። በዚህም ናይጀርያዉያን በቂ የሥራ ቦታን ይፈጥራሉ ፤ ሥራን ለመፍጠርም ገንዘባቸዉን ሥራ ላይ ያዉላሉ። የሚል እምነት አላቸዉ።     

Nigeria Wahlen Präsidentschaftswahlen Plakat
ምስል AP

«በንግዱ ዘርፍ አቡባካር ግዙፍ የሆነ ትስስር ያለቸዉ ሰዉ ናቸዉ። ስለዚህም ምንም አይነት ሥራ ባይሰሩ እንኳ የስራ ቦታን መፍጠር ይችላሉ ገንዘባቸዉንም በንግዱ መስፈር ማፍሰሳቸዉን ይቀጥላሉ ብለዉ የሚያምኑ ሰዎች ጥቂት አይደሉም።  ብዙ ሰዎች አቡበካር በንግድና በኤኮኖሚጉዳዮች ይበልጥ እዉቀት አላቸዉም ብለዉ ያምናሉ። »

የናይጀርያዉ ምርጫ በሃገሪቱ ፀጥታ፣ ኤኮኖሚ እንዲሁም በሙስና ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መሆኑን የፖለቲካ ጉዳይ ምሁሩ ኦልያኒካ አጀላ ይናገራሉ። በሃገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል እስካሁን  መፍትሄ ያላገኘዉ የቦኮሃራም ተደጋጋሚ ጥቃት ፤ በሰሜናዊ ምዕራብ እና በደቡባዊ ምስራቅ ናይጀርያ መቋጫ ያጣዉ በገበሪዎች እና አርብቶ አደሮች መካከል የሚደረጉ  ግጭቶች ተጠቃሽ ናቸዉ። እንደ ዓለማቀፉ ሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባለፉት ሦስት ዓመታት ብቻ በእነዚህ ግጭቶች 3600 ሰዎች ሕይወታቸዉን አጥተዋል። 

በናይጀርያ የሚታየዉ ሙስናም  ሌላዉ የሃገሪቱ  የኤኮኖሚ ከፍተኛ ተግዳሮት ነዉ።  የቡሃሪ መንግሥት  ሥር የሰደደዉን ሙስና ለማስወገድ ጥረት ቢያደረግም  ችግሩን መቅረፍ አልተቻለም። የናይጀርያ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ እና እጩ ተወዳዳሪ አቲኩ አቡባካርም ገንዘብ ነክ ከሆነ ወንጀል ጋር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተከሰዉ ነበር። በዚሁ በያዝነዉ ሳምንት ፕሬዚዳንት ቡሃሪ ተቀናቃኛቸዉ የተቃዋሚዉ ፓርቲ መሪ አቲኩ አቡበከር የምርጫ ድምፅን ሳይገዛ አይቀርም ሲሉም ከሰዋቸዋል። ስለዚህም ይላሉ የፖለቲካ ምሑሩ አጃላ ነጻና ፍትሃዊ ምርጫ ይኖራል ማለት ዘበት ነዉ።  

«በደህንነት እና በሌሎች ጉዳዮች  ምክንያት በምርጫዉ ወቅት የደኅንነት ሠራተኞች በእያንዳንዱ የምርጫ ጣብያ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እንዲካሄድ ያስችላሉ ማለት አይቻልም።»

Karikatur: Nigeria Politik
ምስል A. Baba Aminu

 60 % የሚሆነዉ የናይጀርያ ዜጋ ወጣት ቢሆንም የፊታችን ቅዳሜ በሚደረገዉ ምርጫ ለመምረጥ የሚወጣዉ ግን የድሜ ባለጠጋ እጩዎችን ነዉ። ታዋቂዋ ናይጀርያዊት አምደኛ ሚሪያም ላዉሺ ምርጫዉ ዛሬም ወጣትን ያላካተበት ምክንያት የማኅበረሰቡን ባህልና ልማድን ተከትሎ ነዉ የሚል እምነት አለት።

« እንደባህላችን ከሆነ ወጣቱ ታላላቆቹን ማክበርና ዝም ብሎ መስማት አለበት። ይህ ጥሩ ባህል ቢሆንም ወጣቱ ፖለቲካን በተመለከተ ምንም አይነት እድል የለዉም።»  

ታዛቢዎች እንደሚሉት ቡሃሪም ሆኑ አቡባካር ለሚመርጣቸዉ ወጣት ናይጀሪያዉ ይዘዉ የቀረቡት ጥሩ የሚባል አማራጭ ሃሳብም የላቸዉም።

 

አዜብ ታደሰ / ዳንኤል ፔልዝ

ነጋሽ መሐመድ