1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ኤኮኖሚ

 የናጄሪያ አዲስ ሕግ እና ስደተኞች

ነጋሽ መሐመድ
ሐሙስ፣ መጋቢት 14 2009

ባለፈዉ የጎርጎሪያኑ 2016 ዓመት ብቻ ከሰላ ሺሕ በላይ ናይጄሪያዉያን የሜድትራኒያንን ባሕር ተሻግረዉ አዉሮጳ ገብተዋል።«የሰዎች ንግድ» ተብሎ በሚጠራዉ ዝዉዉርም ናጄሪያ ስማቸዉ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱ ሐገራት መሐል ናት።አዉሮጳ ዉስጥ ከ10 ሺሕ የሚበልጡ ናጄሪያዉያን ሴቶች ለሴተኛ አዳሪነት ተዳርገዋል።

https://p.dw.com/p/2ZoGe
Mittelmeer Migranten und Flüchtlinge in Schlauchboot
ምስል picture-alliance/AP Photo/S. Diab

Nigeria will seine Migranten stoppen - MP3-Stereo

የናጄሪያ መንግሥት ከሐገሪቱ የሚወጡ ሥደተኞችን ለመቆጣጠር ይረዳል ያለዉን አዲስ ሕግ አፅድቋል።ባለፈዉ ሰኞ በይፋ የታወጀዉ «የሰዎች ዝዉዉር ደንብ 2017» የተሰኘዉ ሕግ ከናጄሪያ የሚወጡትን ብቻ ሳይሆን ወደ ናጄሪያ የሚገቡ ሰዎችንም ዝዉዉር ለመቆጣጠር ያለመ ነዉ።ናይጄሪያ እንደ አብዛኞቹ የአፍሪቃ ሐገራት ሁሉ ወደ አዉሮጳ የሚሰደዱ ዜጎችዋን እንድትቆጣጠር ከአዉሮጳ ሕብረት አባል መንግስታት ከፍተኛ ግፊት ይደረግባታል።አዲሱ ሕግም ከናጄሪያዉያን ይልቅ አዉሮጶችን ለማስደሰት ያለመ መስሏል።ያን ፊሊፕ ሾልስ የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

«ለንግድ ከዉጪ የሚገቡ ሰዎች የሚደረግባቸዉ ቁጥጥር ይላላል።«አሸባሪ እና ታጣቂ» የሚባሉ ኃይላት እንዳይገቡ ግን  የሐገሪቱ ድንበር ጥብቅ ቁጥጥር ይደረግበታል።በዚሕ ሒደት ከ እና ወደ ናጄሪያ የሚጓዙ ሰዎች ይመዘገባሉ።»ይላል አዲሱ ሕግ።ስም ምዝገባዉ ግን በርግጥ አስቸጋሪ፤አታካችን እና የተወሳሰበም ነዉ።
የናጄሪያዉ የስደተኞች ጉዳይ መስሪያ ቤት የበላይ ኃላፊ መሐመድ ባባንዴዴ ግን ከአፈፃፀሙ አስቸጋሪነት ይልቅ የሕጉን አስፈላጊነት ነዉ የሚናገሩት።
                      
«ናይጄሪያ ዛሬ ስደተኛ  አሸጋጋሪዎችን ለመዋጋት በፅናት መቆሟን አረጋግጣለች።በርካታ ዜጎቻችን በረሐና ባሕር ዉስጥ እንደሚሞቱ እናዉቃለን።ለዚሕም ነዉ ናጄሪያ ስደተኛ ትልካለች እየተባለ የምትወቀሰዉ።ሰዉን ካንዱ ድንበር ወደ ሌላዉ ማሸጋገር ወንጀል ነዉ።» 
እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ1963 የፀደቀዉን የስደተኞች ጉዳይ ሕግ የሚተካዉ አዲሱ ሕግ በሕገ-ወጥ መንገድ ከናጄሪያ በሚወጣ ወይም በሚገባ ሰዉ ላይ የሚያስጥለዉ ቅጣት በጅግ ከፍ ብሏል።ድሮ ዝቅተኛዉ ቅጣት አንድ ዩሮ ነበር።አሁን፤- ሰወስት ሺሕ ዩሮ።ሰዎች አሸጋጋሪዎች ላይ የሚጣለዉ ቅጣትም በብዙ እጥፍ ንሯል።
ናጄሪያ በርካታ ዜጎቻቸዉ ወደ አዉሮጳ ከሚሰደዱባቸዉ ሐገራት አንዷ ናት።ባለፈዉ የጎርጎሪያኑ 2016 ዓመት ብቻ ከሰላ ሺሕ በላይ ናይጄሪያዉያን የሜድትራኒያንን ባሕር ተሻግረዉ አዉሮጳ ገብተዋል።«የሰዎች ንግድ» ተብሎ በሚጠራዉ ዝዉዉርም ናጄሪያ ስማቸዉ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱ ሐገራት መሐል ናት።አዉሮጳ ዉስጥ ከ10 ሺሕ የሚበልጡ ናጄሪያዉያን ሴቶች ለሴተኛ አዳሪነት ተዳርገዋል።
አብዛኞቹ ስደተኞች ወይም አዉሮጳ የሚደርሱት ከናጄሪያ፤ኒዠር፤ከኒዠር ሊቢያ እያሉ ሜድትራኒያንን ባሕር አቋርጠዉ ነዉ።አዲሱ የናጄሪያ ሕግ የሐገሪቱ መንግሥት ከኒዠር መንግሥት ጋር በመተባበር ስደተኞች ኒዠር ዉስጥ ጭምር እንዲያዙ ይደነግጋል።
                  
«ኒዠር የገባ ስደተኛ ከኒዠር አልፎ ለመጓዝ ማቀዱን የሚያረጋግጥ መረጃ ከተገኘ ልናቆመዉ እንችላለን።ምክንያቱም ከዚያ ግዛት የሚያስወጣዉ ፍቃድ (ቪዛ) የለዉምና።»
ይላሉ የስደተኛ ጉዳይ ኃላፊ መሐመድ ባባንዴዴ።ናጄሪያዊዉን ከናጄሪያ አልፎ ኒዠር ላይ መያዝ።በናጄሪያ የተባበሩት መንግሥታት የፍልሰት ድርጅት (IOM) ግን ይሕን የሕግ አንቀፅ «ሕገ ወጥ» ይለዋል።የድርጅቱ ኃላፊ ወይዘሮ ኢኒራ ክርድዚሊች እንደሚሉት የሰዎችን የመዘዋወር ነፃነት መገደብ ነዉ።
                                   
«ማንኛዉም ግለሠብ በነፃ የመንቀሳቀስ እና የመፍለስ መብት አለዉ ። ናጄሪያዉያንም በኤኮዋስ ደንብ እንደተጠቀሰዉ እንደማንኛዉም  ሐገር ዜጋ ሁሉ በነፃ የመንቀሳቀስ መብታቸዉ ሊከበር ይገባል።»በምዕራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሐብት ማሕበረሰብ (ECOWAS) ደንብ መሠረት የአባል ሐገራት ዜጎች ከንዱ ሐገር ወደ ሌላዉ ያለ ቪዛ መንቀሳቀስ ይችላሉ።የIOM ኃላፊ አዲሱ የናጄሪያ ሕግ ይሕን ይቃረናል ባይ ናቸዉ።የሰዎች የመንቀሳቀስ እና የመፍለስ መብት ከነበረ የተገደበዉ ከአቡጃ በፊት ብራስልስ ነዉ።የአዉሮጳ ሕብረት ርዕሰ-መንበር።
የጀርመንን ጨምሮ የአዉሮጳ መንግሥታት አፍሪቃዉያን ስደተኞች ወደ አዉሮጳ እንዳይገቡ አፍሪቃዉያን መንግሥታት ያግዱላቸዉ ዘንድ ከተለያዩ የአፍሪቃ መንግሥታት ጋር ተስማምተዋል።ዜጎቻቸዉን ወይም የሌሎች ሐገራት ስደተኞችን ለሚያግዱ የአፍሪቃ መንግሥታት አዉሮጶች ጠቀም ያለ ገንዘብ ለመክፈል ቃል ገብተዋል።አንዷ ናጄሪያ መሆኗ ነዉ።ባንፃሩ አዉሮጶች  የሚፈልጉትን የማያደርጉ የአፍሪቃ መንግስታትን በማዕቀብ ለመቅጣት እየዛቱ ነዉ። 

Niger Flüchtlinge aus Nigeria
ምስል DW/A. Cascais
Niger Flüchtlinge aus Nigeria
ምስል DW/A. Cascais

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ