1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የንፁህ የመጠጥ ዉኃ አቅርቦት ችግር በኢትዮጵያ

ሐሙስ፣ መጋቢት 13 2010

በኢትዮጵያ 60 በመቶ የሚሆነዉ ሕዝብ የንፁህ መጠጥ ዉኃ በአቅራቢያዉ አያገኝም ሲል ወተር ኤድ የተባለ ድርጅት ገለፀ።ድርጅቱ በዛሬዉ እለት የሚከበረዉን የዓለም የዉኃ ቀን አስመልክቶ ባወጣዉ ሪፖርት ሀገሪቱ የዉኃ አቅርቦትን እያሻሻሉ ካሉ 10 ሃገራት ዉስጥ 7ተኛ ደረጃ ላይ ብትሆንም

https://p.dw.com/p/2unej
Äthiopien Wokro In the drought area in Wokro ( avalibility of Water by UNESCO support )
ምስል DW/G. Tedla

Access to water in Ethiopia - MP3-Stereo

 

አብዛኛዉ ሰዉ በመኖሪያ አቅራቢያዉ ንፁህ የመጠጥ ዉኃ አያገኝም ። ከንፁህ መጠጥ ዉኃ እጥረት ጋር በተያያዘም በዓለም ላይ በየሁለት ሴኮንዱ አንድ ህፃን ይሞታል ሲል ድርጅቱ ገልጿል። በየዓመቱ መጋቢት 14 ቀን የሚከበረዉን የዓለም የዉኃ ቀን አስመልክቶ   ድርጅቱ  ባወጣዉ ሪፖርት በዓለም ላይ 900 ሚሊዮን የሚጠጉ  ሰወች ንፁህ የመጠጥ ዉኃ አያገኙም። ቁጥሩ በዓለም ላይ በርካታ ሰዎች ህይወትን በአስቸጋሪ ሁኔታ እየገፉ መሁኑን ያሳያል ሲሉ የድርጅቱ ቃል አቀባይ ሚስ ካሮሊን ዊለር ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል።
«በዛሬዉ እለት ያወጣነዉ  የዉኃ አጠቃቀም ክፍተት ሪፖርት እንደሚያሰየዉ በዓለም ዙሪያ 844 ሚሊዮን ሰወች በመኖሪያ አቅራቢያ ንፁህ የመጠጥ ዉሃ የማግኜት እድል የላቸዉም።ያ ማለት ዉሃ ለማግኜት ረዥም መንገድ በመጓዝ አስቸጋሪ የለት ተለት ህይወት ይገፋሉ ማለት ነዉ።»
በዓለም ላይ የንፁህ መጠጥ ዉሃ እጥረት ካለፈዉ ዓመት ጋር ሲነፃፀርም  ከፍተኛ መሆኑን ዘገባዉ ገልፆ፤  ፍልሰት፣ የህዝብ ቁጥር መጨመር፣ደካማ የገንዘብ አቅርቦት፣ የዓየር ጠባይ ለዉጥና  ለንፁህ መጠጥ ዉሃ አቅርቦት ቅድሚያ አለመስጠት ለቁጥሩ ማሻቀብ በምክንያትነት ተጠቅሰዋል።   የንፁህ መጠጥ ዉሃ ተጠቃሚነትና ተደራሽነት በሀብታምና በድሆች መካከል ልዩነቱ ከፍተኛ መሆኑም በሪፖርቱ ተመልክቷል። ያለ ንፁህ መጠጥ ዉሃ አቅርቦት ድህነትን መቀነስ፣ የጤና ሁኔታን ማሻሻልና  ሌሎች ዓለም ዓቀፍ  የልማት ግቦች ማሳካት ስለማይቻል መንግስታት ለንፁህ መጠጥ ዉሃ ተደራሽነት  ትኩረትና አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጡ  ቃል አቀባይዋ  ጠይቀዋዋል።
«ወተር ኤድ ፤በዓለም ዓቀፉ የዉሃ ቀን የሚጠይቀዉ ችግሩን ለመፍታት መንግስታት ትኩረት እሰጥተዉ እንዲሰሩና አፋጣኝ ርምጃ እንዲወስዱ ነዉ።የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በ2030 ንፁህ የመጠጥ ዉሃና ንፅህና ለእያንዳንዱ ሰዉ ለማዳረስ የያዘዉን ግብ ለማሳካት በሚፈለገዉ ፍጥነትና መሻሻል እየሄደ አይደለም።እናዉቃለን ማሻሻል ይቻላል ግን የፖለቲካ ትኩረትና በየደረጃዉ የገንዘብ ድጋፍ ያስፈልጋል።» 
ኢትዮጵያ የዉሃ አቅርቦትን እያሻሻሉ ካሉ 10 ሀገራት ዉስጥ 7ተኛ ደረጃ ላይ ብትሆንም ንፁህ የመጠጥ ዉሃ አቅርቦት በመኖሪያ አቅራቢያ ከማያገኙ 10 ሀገራት መካከል 2ተኛ ፣ በጣም ዝቅተኛ የዉሃ አቅርቦት ካላቸዉ ሀገራት ደግሞ በ 4ተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።በሀገሪቱ  39 በመቶ የሚሆነዉ ህዝብ ብቻ  በመኖሪያ አቅራቢያዉ ንፁህ የመጠጥ ዉሃ ያገኛል ያሉት ሀላፊዋ አቅርቦቱን ለማሻሻል መንግስት በርትቶ ሊሰራ ይገባል ነዉ ያሉት።
1,«ከዩኑሴፍና ከዓለም ዓቀፉ የጤና ድርጅት ያገኜነዉ መረጃ እንደሚያሳየዉ  በኢትዮጵያ 3 ህዝብ  በመኖሪያ አቅራቢያዉ ንፁህ የመጠጥ ዉሃ አያገኝም። ምንም እንኳ በጥናቱ ኢትዮጵያ  መሻሻል እያሳዩ ካሉ  10 ቀዳሚ ሀገራት ዉስጥ ብትሆንም። ያ ማለት አሁንም ድረስ  ንፁህ የመጠጥ ዉሃን የበለጠ ተደራሽ ለማድረግ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ያስፈልጋል ማለት ነዉ።»
አቶ አበራ ተስፋዬ በንፁህ መጠጥ ዉሃ ተደራሽነት ከመንግስትና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር  በጥናትና  በማማከር ስራ በርካታ ዓመታት የሰሩ የዉሃ ሃብት ባለሙያዉ ናቸዉ። ሪፖርቱን በተመለከተ ያላቸዉን ሙያዊ አስተያየት ጠይቀናቸዉ ነበር።በመንግስት በኩል ከሚቀርቡ ሪፖርቶች የቁጥር ልዩነት ቢኖርም ችግሩ መኖሩን ግን ያሳያል ብለዋል።

Äthiopien Gurage Zone
ምስል 3BL Enterprises
Äthiopien Dürre Wassertransport
ምስል picture-alliance-akg-images/Y. Travert

ኤርትራ ፤ፓፓዋ ኒጊዋና  ዩጋንዳ  በጣም ዝቅተኛ የንፁህ መጠጥ ዉሃ አቅርቦት ያላቸዉ ሀገራት ተብለዉ በቅደም ተከተል ከአንድ እስከ ሶስት ባለዉ ደረጃ በሪፖርቱ ተቀምጠዋል። 

ሞዛንቢክ የዉሃ አቅርቦትን በከፍተኛ ደረጃ እያሻሻሉ ካሉ ሀገሮች ዝርዝር ዉስጥ በአራተኛ ደረጃ ላይ ስትሆን ነገር ግን በዝቅተኛ የዉሃ አቅርቦት አስረኛ ደረጃ መሆኗ ነዉ የተመለከተዉ።

ሌላዋ በሪፖርቱ የተካተተችዉ ታንዛኒያ በጣም ዝቅተኛ የዉሃ ተደራሽነት ካላቸዉ አስር ሀገሮች ዉስጥ ስትሆን በሀገሪቱ  13 በመቶ የሚሆነዉ ህዝብ ንፁህ  የመጠጥ ዉሃ ለማግኜት ሰላሳ ደቂቃ መጓዝ ይኖርበታል።በሪፖርቱ  ኒጀርና ማሊ ንፁህ የመጠጥ ዉሃ በማግኜት ረገድ በድሆችና  በሃብታሞች መካከል ሰፊ  ልዩነት ያለባቸዉ ሀገሮች ሲሆኑ ኤዥያዊቷ ሀገር ህንድ ደግሞ አብዛኛዉ ህዝቧ የሚጠጣ ዉሃ ለማግኜት ከግማሽ ስዓት በላይ መጓዝ ይኖርበታል ነዉ የተባለዉ።
እንደድ ርጅቱ ዘገባ  ከንጹህ መጠጥ ዉሃ እጦት  በሚመጡ በሽታዎች ሳቢያ በዓለም ላይ ከዓምስት ዓመት በታች ያሉ 289 ሚሊዮን ህፃናት በየ ዓመቱ ፣800 በየቀኑና  አንድ ህፃን ደግሞ በየ ሁለት ሴኮንዱ ይሞታል።

ፀሀይ ጫኔ

ሂሩት መለሰ