1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአለም ሰብአዊ መብት ምክር ቤትና ሱዳን

ዓርብ፣ መስከረም 26 1999

የአዉሮጳ ሕብረት ረቂቅ ለዳርፉሩ ሰብአዊ ቀዉስ የካርቱም መንግሥት ነዉ-ተጠያቂ የሚያደርገዉ።ይሁንና የሙስሊምና የአፍሪቃ ሐገራት የአዉሮጳ ሕብረትን ረቂቅ ሐሳብ የሚቀበሉት አይመስልም።

https://p.dw.com/p/E0hx
የጄኔቩ ጉባኤ
የጄኔቩ ጉባኤምስል AP

ትናንት የተጀመረዉ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብት ተማጋች ምክር ቤት ስብሰባ በሐገራት የሰብአዊ መብት ይዞታ ላይ እየተናገረ ነዉ።የቀድሞዉ የአለም የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ፈርሶ «የሰብአዊ መብት ምክር ቤት» በሚል ስም ባዲስ መልክ ከተዋቀረ ወዲሕ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰየመዉ ስብሰባ ዛሬ የምዕራባዊ ሱዳን ግዛት የዳርፉርን ግጭትንና በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚፈፀመዉ በድል አብይ የመነጋገሪያ ርዕሱ አድርጎታል።

አርባ-ሰባት አባል ሐገራትን የሚያስተናብረዉ የተባበሩት መንግሥት የሰብአዊመብት ምክር ቤት በዚሕ-ቅርፁ ከተዋቀረ፣ በዚሕ ስሙ-ከተሰየመ ወዲሕ በአለም የሰብአዊ መብት ይዞታ ላይ ለመነጋገር ሲሰየም ትናንት የጀመረዉ የመጀመሪያዉ ነዉ።የመጀመሪያዉ ስብሰባ ሁለተኛ ርዕሥ ሱዳን ነች-ዳርፉር።ላለፉት ሰወስት አመታት በግጭት ሁከት በምትታበጠዉ በምዕራባዊ ሱዳን ግዛት ዳርፉር በሰላማዊ ሰዎች ላይ ሥለሚፈፀመዉ ግፍ ያልዘገበ ድርጅት፣ ግፉን ያላወገዘ የሰብአዊ መብት ተቋም በርግጥ የለም።

የአፍሪቃ ሕብረትም እንደብዙዎቹ ድርጅቶች ሁሉ በቅርቡ የዳርፉርን የሰብአዊ መብት ሁኔታ በተመለከተ አንድ ዉሳኔ አሳልፎ ነበር።አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ምክር ቤት ዛሬ ዉለዉን ከመረበት አንዱና ዋነኛዉም የአፍሪቃ ሕብረት ዉሳኔ ነዉ።የሰብአዊ መብት ተሟጋች ምክር ቤት የተባለዉ ተቋም ባልደረባ ቴዎዶር ራትጌበር እንደሚሉት ግን የአፍሪቃ ሕብረት ዉሳኔ የተድበሰበሰ ነዉ።ሕብረቱ ራትጌበር እንደሚሉት ዳርፉር ዉስጥ በዋነኛነት ሰብአዊ መብት የሚጥሰዉን ወገን በግልፅ አለመጥቀሱ አስደናቂ ነዉ።የካርቱም መንግሥትን።


«የአፍሪቃ ሕብረት ሁኔታዉን በተገቢዉ መንገድ አለማያቱ አሳዛኝ ነዉ።የራሱ አባል አሁን በምትፈፅመዉ ሁኔታ ወደፊት መቀጠል እንደማይገባት አለማስጠንቀቁ ያሳዝናል።የአፍሪቃ ሕብረት ልክ እንደ ሱዳኑ ሁሉ በዉስጣዊ ጉዳዩ የሚታይ ሕፀፅን ለመተች አለመፈቅዱን መገንዘብ አይገድም።»

የዳርፉር ጉዳይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባበሰ መምጣቱ ይታመናል።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት የግዛቲቱን ሠላም የሚያስከብረዉ የአፍሪቃ ሕብረት ሠራዊት በአለም አቀፍ ሠራዊት እንዲተካ ቢወስንም የሱዳን መንግሥት ዉሳኔዉን እስካሁን ዉድቅ እንዳደረገዉ ነዉ።

የሱዳን መንግሥትና ዋናኛዉ የዳርፉር አማፂ ቡድን የሰላም ዉል ቢፈራረሙም ከሁለት መቶ ሐምሳ ሺሕ በላይ ሕዝብ ያለቀበት፤ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የተሰደደበት ግጭት ጦርነት ግን እንደቀጠለ ነዉ።የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ምክር ቤት የበላይ ወይዘሮ ሉዊስ አርቦር የሰላም ዉሉ የፈየደዉ የለም ባይ ናቸዉ።

ምክር ቤቱ በዛሬዉ ዉሎዉ ከአፍሪቃ ሕብረት ዉሳኔ ላሌ የአዉሮጳ ሕብረት ሥለ ዳርፉር ጉዳይ ባቀረበዉ ረቂቅ ሐሳብ ላይም ይነጋገራል።የአዉሮጳ ሕብረት ረቂቅ ለዳርፉሩ ሰብአዊ ቀዉስ የካርቱም መንግሥት ነዉ-ተጠያቂ የሚያደርገዉ።ይሁንና የሙስሊምና የአፍሪቃ ሐገራት የአዉሮጳ ሕብረትን ረቂቅ ሐሳብ የሚቀበሉት አይመስልም።