1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአማራና ትግራይ ህዝቦች የዉይይት መድረክ  በመቐለ

ሰኞ፣ የካቲት 18 2011

የትግራይና አማራ ህዝብና ልሂቃን አንድነትና ሰላማዊ ግንኙነት ላይ ያተኮረ የመጀመሪያው ህዝባዊ ውይይት መድረክ በመቐለ ተካሄደ፡፡ በመድረኩ ጥናታዊ ፅሑፍ ያቀረቡ ምሁራን የአማራና ትግራይ ህዝቦች በሀገር ምስረታና ግንባታ ሂደት ቀዳሚና ትልቅ ተሳትፎ እንደነበራቸው አትተዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3E4OJ
Äthiopien Friedensgespräche in Mekele
ምስል DW/M. Hailesilassie


የትግራይና አማራ ህዝብና ልሂቃን አንድነትና ሰላማዊ ግንኙነት ላይ ያተኮረ የመጀመሪያው ህዝባዊ ውይይት መድረክ በመቐለ ተካሄደ፡፡ በመድረኩ ጥናታዊ ፅሑፍ ያቀረቡ ምሁራን የአማራና ትግራይ ህዝቦች በሀገር ምስረታና ግንባታ ሂደት ቀዳሚና ትልቅ ተሳትፎ እንደነበራቸው አትተዋል፡፡ በመቐለ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን የሰላም ፎረም አስተባባሪነት የተካሄደው ውይይት ከአማራ ክልልና ሌሎች የኢትዮጵያ ክፍሎች የታደሙ ልሂቃን እንዲሁም የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የሚወክሉ ተሳታፊዎች ተገኝተውበታል፡፡በሃይማኖት፣ ባህል፣ አኖኖር፣ ሥነ- ልቦናና ታሪክ የትግራይና አማራ ህዝቦች የተቆራኙ መሆናቸው የገለፁት በውይይት መነሻ ፅሑፍ ያቀረቡ ምሁራን በዚህ ወቅት እየታዩ ያሉ ችግሮችም ነባሩን ግንኙነት ታሳቢ ባደረገ መልኩ ሊፈቱ ይገባል ብለዋል፡፡ በህዝባዊ የውይይት መድረኩ ፅሑፍ ያቀረቡ የዲላ ዩኒቨርሲቲው የታሪክ መምህር ዶክተር ቴድሮስ ሃይለማርያም በአማራና ትግራይ ህዝቦችና ልሂቃን የሚፈጠር አንዳች ችግር አንድምታ ሀገራዊ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም ጉዳዩ ለፖለቲካ ልሂቃን ብቻ የሚተው ሳይሆን የሁሉም ተሳትፎ የሚሻ ነው ብለውታል፡፡ ከጎንደር፣ ወሎ፣ ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲዎች የወጡ ምሁራንም በሰላም ፎረሙ ተሳትፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሃይማኖት ምሁራንም በመድረኩ የሰላም መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን መቐለ የሚገኘው የቅዱስ ፍሬሚናጦስ አባ ሰላማ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሥነ መለኮት መምህር የሆኑት ሊቀ ሊቃውንት አባ መላኩ ታከለ የሰው ልጆች በተፈጥሯቸው ተከብረው ሊኖሩ የሚገባ ፍጡራን ናቸው በማለት የዘርና ብሔር ክፍፍል በመንፈሳዊ አስተምህሮ ተቀባይነት እንደሌለው ገልፀዋል፡፡በትግራይና አማራ ህዝብና ልሂቃን አንድነትና ሰላማዊ ግንኙነት ላይ ባተኮረው የውይይት መድረክ ከምሁራን በተጨማሪ በሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የተውጣጡ የማሕበረሰብ ክፍሎችም ተገኝተውበታል።


ሚሊዮን ኃይለሥላሴ


አዜብ ታደሰ 
ማንተጋፍቶት ስለሺ