1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአቶ በቀለ ገርባ የአመክሮ መብት መከልከል

ሐሙስ፣ ጥር 29 2006

በእስር ላይ የሚገኙት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የእስር ጊዜያቸውን ቢጨርሱም ኣመክሮ መከልከላቸው ተሰማ። ህክምናም እያገኙ ኣይደለም ተብሏል። የኮንግረሱ ዋ/ጸኃፊ ለዶቸቬሌ እንደ ነገሩት ከሆነ አቶ በቀለ ገርባ የ 3 ዓመት ከ 7 ወር የእስር ጊዜያቸውን ኣጠናቀው መለቀቅ የነበረባቸው ባለፈው ጥር 11 ቀን ነበር

https://p.dw.com/p/1B3u3
Symbolbild Justitia Justizia
ምስል picture-alliance/dpa

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሺን በበኩሉ የዚህ ኣይነት ቅሬታ እስከኣሁን እንዳልደረሰው ኣስታውቋል።

ቀድሞ በዶ/ር መረራ ጉዲና ይመራ የነበረው የኦሮሞ ህዝብ ኮንግረስ (ኦህኮ) እና ያኔ በአቶ ቡልቻ ደመቅሳ ይመራ የነበረው የኦሮሞ ፌደራሊስት ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፈዲን) ተዋህደው የፈጠሩት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ተቀዳሚ ም/ሊቀመንበር ነበሩ፤ አቶ በቀለ ገርባ። በያዙት ኃላፊነትም ያለ ኣግባብ የታሰሩ ኦሮሞዎችን ጉዳይ እየተከታተሉ ለዓለም ዓቀፍ የመብት ተሟጋቾች እና ለሚመለከታቸው ሁሉ ያሳውቁም ነበር። ይኸው ተግባራቸው ያላስደሰተው የኢትዮጵያ መንግስት ታዲያ የኮንግረሱ ዋ/ጸኃፊ አቶ በቀለ ነጋ እንደሚሉት ኣሸባሪ በሚለው ድርጅት ስም ወንጅሎ ኣስፈረደባቸው። የተፈረደባቸው ስምንት ዓመት ሲሆን በይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት ወደ 3 ዓመት ከ 7 ወር ተሻሽሎላቸው ነበር ዝዋይ እስር ቤት የከረሙት።

Wahl in Oromia Äthiopien 23.Mai 2010
ምስል DW

አቶ በቀለ ገርባ ከዝዋይ እስር ቤት ጀምሮ ኣሁን በሚገኙበት የቃሊቲ ወ/ቤትም ታመው ህክምና እንዳላገኙም ነው እየተነገረ ያለው። የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሺን ሊቀመንበር የሆኑት አምባሳደር ጥሩነህ ዜና ግን የዚህ ኣይነት አቤቶታ እስከ ኣሁን ኣልደረሰንም ባይ ናቸው።

ከኢትዮጵያ መንግስት ወከባና እስራት ሸሽተን በጎረቤት ኣገር እንገኛለን ከሚሉት የኦሮሞ ተወላጆች መካከል ኣንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ ስደተኛ በበኩላቸው ከአቶ በቀለ ገርባ በባሰ ሁኔታ ህክምና ተነፍገው የሞቱ የኦሮሞ እስረኞችም ኣሉ ሲሉ ኣንዳንዶቹን ጠቃቅሷል። ከዚሁ በመነሳ የኢትዮጵያ እስር ቤቶች የስራ ቐንቐ ኦሮምኛ ሆኗል እስከማለትም ተደርሷል። የሰብዓዊ መብት ኮሚሺን ሊቀመንበሩ አምባሳደር ጥሩነህ ዜና ግን ሊደንቀን ኣይገባም ይላሉ።

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ም/ሊቀመንበሩ፤ አቶ በቀለ ገርባ፤ በተፈረደባቸው ዕለት የፍርድ ማቅለያ ኣስተያየት ይሰጡ ዘንድ እድል ቢሰጣቸውም «ሳላጠፋ የፈረደብኝን ፍ/ቤት ይቅርታ ኣልጠይቅም። ይቅርታ መጠየቅ ካለብኝ የሚጠበቅብኝን ያህል ካልሰራሁለት የኦሮሞን ህዝብ ነው ይቅርታ እምጠይቀው» ሲሉ ችሎቱ ፊት ቆመው መናገራቸው አይዘነጋም።

ጃፈር ዓሊ

ተክሌ የኋላ