1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮጳ «የስደተኞች ጉዳይ ዉል» እና አፍሪቃ

ዓርብ፣ ሰኔ 3 2008

የአዉሮጳ ኅብረት እንደሚለዉ ስደተኞችን በተመለከተ ከአፍሪቃ ጋር ሊዋዋል ያቀደዉ «የስደተኞች ጉዳይ ዉል» አዲስ ነዉ። የዶቼ ቬለዉ ሉድገር ሻዶምስኪ ባቀረበዉ ሐተታ የዉሉ ዓላማ የፍልሰትን መንገድ ማስተካከል ሳይሆን ሠዎች ወደ አዉሮጳ እንዳይመጡ ለመግታት ነዉ።

https://p.dw.com/p/1J3u2
Italien Bootsflüchtlinge
ምስል picture alliance/epa/Italian Navy

በአዉሮጳ ኅብረት የቀረበዉ «የስደተኞች ጉዳይ ዉል» ከአሁን ጀምሮ በዉዴታም ሆነ በግዴታም በሥራ ላይ መዋል አለበት። ወይም ባለፈዉ ማክሰኞ የአዉሮጳ ኅብረት እንደገለፀዉ እቅዱን በትክክል ለሚተገብሩት ይሸልማል ካልሆነ ግን ይቀጣል። ሽትራስቡርግ በሚገኘዉ የአዉሮጳ ፓርላማ ለመጀመርያ ጊዜ ይፋ የሆነዉ «የስደተኞች ጉዳይ ዉል» ለአውሮጳ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ተጠሪ ፌዴሪካ ሞገሪኒ ልክ እንደ «የኮፐርኒከስን ሥር ነቀል አዲስ ሃሳብ» እንደማለት ነዉ። እንደሚታወቀዉ የኮፐርኒከስን ሥር ነቀል አዲስ ሃሳብ ሌሎች የተረዱለት ከሞተ ከ 200 ዓመት በኋላ ነበር። እዉነታዉ ግን የአዉሮጳ ኅብረት የስደተኞች ፖለቲካ መርሃ-ግብር እስካሁንም ድረስ አለመስራቱን ነዉ። ፍልሰትን ለመግታት እስካሁን የነበሩት የተለያዩ እቅዶችና መርሃ ግብሮች አንሰዉ አይደለም። ለምሳሌ የስደተኞችን ፍልሰት ለመግታት ስመጥር የሆኑት «የካርቱም ዉል» ወይም «ቫሌታ ስምምነት» ተጠቃሽ ናቸዉ።


እንዳለመታደል ሆኖ ግን እቅዱ ዉጤታማ አልሆነም። ከሊቢያ ጋር የሚደረገዉ የትብብር ሥራ እንዴት ነዉ የሚጠናከረዉ? የሊቢያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚንስትር በቅርቡ ስደተኞችን መልሰን አንወስድም ሲሉ አልተናገሩም? ከጋዳፊ አገዛዝ በኋላ ሊቢያ መፈረካከስዋ የታወቀ ነዉ፤ ከየትኛዉ ሊቢያ ጋር ነዉ የትብብር ሥራ መተግበር የፈለግነዉ? ይህ የአዉሮጳ የስደተኞች ዉል አዉሮጳዉያን ሳይሆኑ ተግባራዊ ማድረግ የሚችሉት አፍሪቃዉያኑ በፈለጋቸዉ አቅጣጫ የስደተኞችን ቁጥር በመጨመር እነሱ በሚሹት ዉል ላይ ለመድረስ ይጠቀሙበታል።

እንደቀድሞዉ ሁሉ ብረስልስ የሚገኘዉ የአዉሮጳ ፓርላማ ከእነዚህ አጋር ተብዬ የአፍሪቃ ሃገራት በአመዛኙ የሚጎርፉትን ወጣት ወንድ ፍልሰተኞች ጉዞ ለማስቆም አሁንም ምን ፍላጎት እንደሌላቸዉ አልገባዉም። ከታማኝ ምንጮች በተገኘዉ መረጃ መሠረት ከፍተኛ ስልጣን ያላቸዉ ወታደራዊ አባላት በተቃራኒዉ በሕገ-ወጥ ሰዎችን ወደዉጭ እየላኩ ገንዘብ ያገኛሉ።

በርካታ ሶማልያዉያን እንዲሁም በሙስና የተጨማለቁ የሶማልያ ፖለቲከኞች የየለት ኑሮአቸዉን የሚገፉትም ከዲያስፖራዉ በሚላክላቸዉ ገንዘብ ነዉ። ሌሎች እንደሚሉትም የአፍሪቃ ባለስልጣናት ወጣት ሥራ አጦችንና አመፅ ቀስቃሾችን በደስታ ነዉ ከሃገር የሚያሰናብቱዋቸዉ።

ይህ ባለፈዉ ማክሰኞ ይፋ የሆነዉ የአዉሮጳ ኅብረት «የስደተኞች ዉል» ፍልሰተኞችን ወደ ትዉልድ ሃገራቸዉና ወደ ስደት መሸጋገርያ ሃገራት በመመለስ ከዝያም ኤኮኖምያቸዉን በማጠናከር ሰዎች ከመጡበት ቦታ እንዲኖሩ ለማድረግ ያቀደ ነዉ። ይህ ሃሳብ ግን ቀደም ሲል እንደነበረዉ የአዉሮጳ ለአፍሪቃ የእድገት ርዳታ ተራድዖ መረሃ -ግብር ጋር አንድ አይነት ሲሆን፤ ያም ቢሆን ዉጤታማ ሆኖ አለመገኘቱ እሙን ነዉ። እዚህ ላይ አሳዛኙ ነገር የአዉሮጳ ኅብረት ለትብብሩ ዝግጁ ያልሆኑ ሃገራት ላይ የንግድ ማዕቀብ አሳርፋለሁ ሲል ማስፈራራቱ ነዉ። በ100 ሺህ የሚቆጠሩ የአፍሪቃ ገበሪዎችና የአሳ አጥማጆች በገፍ ፊታቸዉን ወደ አዉሮጳ እንዲዞሩ ያደረገዉ የአዉሮጳ ኅብረት የያዘዉ የንግድ ፖለቲካ ይሆን?
በሰሜን አፍሪቃና በሳህል አካባቢ አገራት በሕገ-ወጥ ሰዎችን የሚያዘዋዉሩ ሠዎች ሥራ ለማገድ እንዲሁም በባህር ላይ ህይወታቸዉን የሚያጡትን የጀልባ ስደተኞች ለመግታት የአዉሮጳ ኅብረት ማዕከል ይገኛል።

Brüssel Europäische Kommission Außenansicht
ምስል picture-alliance/dpa/D. Kalker

ሌላዉ የ «ብሉ ካርድ » መረሃ ግብርን በመጠቀም፤ የአፍሪቃ ባለሞያዎች ወደ አዉሮጳ እንዲመጡ ማድረግ ነዉ። መራራ እዉነቱን እንናገር ካልን ግን የአዉሮጳ የስደተኞች ፖለቲካ ማለት ስደተኞች ወደ አዉሮጳ እንዳይገቡ የሚከለክል ፖለቲካ ነዉ። የሚያሳዝነዉ የአዉሮጳ ኅብረት አባል ሃገራት መካከል ጥልቅ የሆነ ልዩነት መኖሩ በገሃድ የሚያሳይ ነዉ። በገንዘብ ችግሩን ለመቅረፍ ቢታቀድም ገንዘቡ በተባለዉ ሰዓት ወጭ አልተደረገም። በጎርጎረሳዉያኑ 2015ዓ,ም ከታቀደዉ 1,8 ቢሊዮን ይሮ የአስቸኳይ ጊዜ ርዳታ ዉስጥ 28ቱ የአዉሮጳ ሃገራት መንግሥታት 80 ሚሊዮን ይሮ ብቻ ነዉ ወጭ ያደረጉት። በያዝነዉ ሳምንት ማክሰኞ ይፋ በሆነዉ የአዉሮጳ ኅብረት ከአፍሪቃ ጋር ላቀደዉ «የስደተኞች ጉዳይ ዉል» 8 ቢሊዮን ይሮ እስከ 2020 ዓ,ም ድረስ ወጭ ይደረጋል። ይህ የተባለዉን ገንዘብ ከየት እንደሚመጣ የሚያዉቀዉ ግን የአዉሮጳ ኅብረት ኮሚሽን ብቻ ነዉ።

ሉድገር ሻዶምስኪ / አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ