የአውሮጳ ኅብረት ፀረ-ሽብር ትግል በሳህል
ሰኞ፣ ሐምሌ 23 2004እስላማዊ አሸባሪዎቹ የሳህል ግዛትን በስፋት እየተቆጣጠሩ እንደሆነ የሚታወቅ ነው። ሳህል ውስጥ ወደምትገኘው አነስተኛዋ የምዕራብ አፍሪቃ ግዛት ያቀኑት የአውሮጳ ህብረት የፀጥታ አማካሪዎች ኒዠር ውስጥ የሚጠብቃቸው ከፍተኛ የቤት ስራ ነው። በሳህል ግዛት ውስጥ በፍጥነት እየተስፋፋ የመጣውን እስላማዊ ቡድን ሲቻል እንዲያጠፉ አለያም ከግስጋሴው እንዲገቱ ለኒዠራውያን አፋጣኝ የፀረ ሽብር ስልጠና መስጠት ይኖርባቸዋል። አንሳር ዲኔ የተሰኘው እስላማዊ ቡድን በግስጋሴው ገፍቶበት በሰሜን ማሊ የፈረንሳይን የቆዳ ስፋት የሚስተካከል መሬት በቁጥጥሩ አስገብቷል። ያ በኒዠር እንዲደገም የሀገሪቱ መንግስት የሚፈቅድ አይመስልም። ኒዠሮች ከአውሮጳ ህብረት ጋር በመተባበር አማፂያኑን መግታት ይፈልጋሉ። የአውሮጳ ህብረት ቃል አቀባይ ሚካኤል ማን።
«በአውሮጳ ህብረት የባለሙያ ልዑካናታችን በኩል የደህንነት እና አሸባሪነትን የመዋጋት ክህሎታቸውን ለማሻሻል ርዳታ ልናደርግላቸው እንችል እንደሆን በኒጀር ባለስልጣናት ተጠይቀናል»
ሳህል ላይ እየበረታ የመጣው አንሳር ዲኔ የተሰኘው እስላማዊ ቡድን የአልቃይዳ የአካባቢው ህዋስ እንደሆነ ከሚነገርለት እስላማዊ ማግሬብ ጋር ግንኙነት አለው ተብሏል። ያ ደግሞ ስጋቱ ለማሊ ብቻ ሳይሆን በሳህል ግዛት ውስጥ ለሚገኙት እንደ ኒዠር ላሉ የምዕራብ አፍሪቃ ሀገራት ጭምር ነው። የአልቃይዳ ሰሜን አፍሪቃ ክንፉ እስላማዊው ማግሬብ ጠረፍ የሚገድበው አይነት አይደለም። በአልጀሪያ ቦንብ አንጉዷል፣ በሞሪታንያ የኬላ ጠባቂ ወታደሮችን ተኩሶ ገድሏል፣ አሁን ደግሞ ኒዠር ላይ የቅዱስ ጦርነት ማካሄድ ይፈልጋል። ኒዠር ደሀ ሀገር ከመሆኗ አንፃር እንደ ሞሪታኒያ እና ማሊ በቀላሉ አደጋ ላይ ልትወድቅ የምትችል ሀገር ናት። በብሩስል የዩነቨርሲቲ መምህር እና የሳህል ጠበብቷ አሜሊያ ሀድፊልድ።
«በተለይ ሞሪታንያ፣ ማሊ እና ኒጀር ከፍተኛ የሀገር አለመረጋጋት እና የአቅም ችግር አለባቸው። ስለዚህ ሀገራቱ በቀላሉ አደጋ ላይ ሊወድቁ የሚችሉ ናቸው። በሀገራቱ ከደህንነት ስጋት ባሻገር እንደ ውሃ፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ ትምህርት እና የጤና እንክብካቤን የመሳሰሉ ህዝባዊ አቅርቦቶች ዕጦትም የተባባሰ ነው።»
በአጠቃላይ 23 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች በዚሁ የሳህል ግዛት ውስጥ ይኖራሉ። ከነዋሪዎቹ መካከል አብዛኞቹ በድህነት አረንቋ ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ያም በመሆኑ የአውሮጳ ህብረት የሳህል አካባቢን በወታደራዊ ማማከር ተልዕኮው ከመርዳት ይልቅ በማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ቢያተኩር ይሻለው ነበር ሲሉ በጀርመን የሊንከ ፓርቲ የምክር ቤት አባሉ ሞቫሳት ኒየማ ይገልፃሉ።
«እንደሚመስለኝ እሳት የማጥፋት አይነት የፖለቲካ አካሄዱን ትተን አሸባሪነትን መከላከል የሚያስችል ብሎም በእንጭጩ የሚቀጭ አሰራርን የሚከተል ፖለቲካ መጀመር ይኖርብናል።»
50 አባላትን ያቀፈው የአውሮጳ ህብረት የሳህል ልዑክ ይፋዊ ስያሜው «የአውሮጳ ህብረት የአቅም ግንባት ልዑክ» በእንግሊዘኛ ምህፃሩ EUCAP ነው የሚሰኘው። የልዑኩ ዋነኛ ዓላማ ሽብርን መከላከል ከመሆኑ አንፃር ከፖሊሶች እና ከወታደራዊ ባለስልጣናት ባሻገር የፖለቲካ አማካሪዎች እና የአውሮጳ የፍትህ ባለሙያዎችም ወደ አካባቢው እንደሚጓዙ ተጠቅሷል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ተክሌ የኋላ