1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአየር በረራ ደንብና የአዉሮጳ ሕብረት

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 27 2002

የSingel European Sky (አንድ የአዉሮጶች ሠማይ) እንበለዉ ይሆን? ብቻ ሰነድ ፈራሚዎች የበረራ ደንቦችንና መስመሮች መቀናጀታቸዉና በአንድ የኮምፒዉተር ሥርዓት መመራታቸዉን ይቀበሉታል

https://p.dw.com/p/NF9N

የአዉሮጳ ሕብረት የአባል ሐገራቱን የበረራ ሥርዓትና ደንቦች ለማቀናጀት የነደፈዉን እቅድ ገቢራዊ ለማድረግ አባል ሐገራት ተስማሙ።ትናንት ብራሥልስ የተሰበሰቡት የአባል ሐገራት የትራንስፖርት ሚንስትሮች እቅዱ በተያዘለት ጊዜ ገቢር እንዲሆን ወስነዋል።በአዲሱ እቅድ መሠረት የሠላሳ ስምንቱ አባል ሐገራት የበረራ ሕግጋትና ደንቦች በዘጠኝ አካባቢዎች በሚከፈል የጋራ ማዕከል ይቀናጃሉ።Singel European Sky የተሰኘዉን መርሐ-ግብር አባል ሐገራት በሙሉ ቢቀበሉትም ገቢራዉነቱ ብዙ አጠራጥሮ ነበር።ሽስቴፋኒ ሲክ የዘገበዉችን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።


አለም አቀፍ በረራ ሽቴፋኒ ሲክ እንደዘገበችዉ ከሐገር «ሀ» ሐገር «ለ» መድረስ ብቻ አይደለም።በወታደራዊ ቀጣናዎች፥ ጠንካራ ድምፅ በተከለከለበት አካባቢዎች መብረርንም ይጨምራል።አብራሪዉ (ፓይለቱ) በየሚበርበት ሐገር የአየር ክልክል ሲገባ የራዲዮ የሞገድ መስመሩን መቀየር እንዳለበትም ሊዘነጋ አይገባም።የአዉሮጳ ሕብረት የሠላሳ-ስምንት አባል ሐገራቱን ይሕን ሁሉ ጡቃንጡቅ ነዉ-እዘጠኝ አቧድኖ ሊያቀናጅ ያቀዳዉ።

እቅዱ አባል ሐገራት በሙሉ አንድ የአየር መቆጣጠሪያ ሥልት እንዲጋሩ ለማድረግ ያለመ ነዉ።ገቢር ከሆነ የጀርመን የበረራ መቆጣጠሪያ አገልግሎት (DFS) ተጠሪ ክሪስቲና ኬሌክ እንደሚሉት ጥቅሙ እጅግ ነዉ።
«ደንበኞች በጣሙን የአየር መንገዶች ገንዘብ ይቆጥባሉ።ጊዜ ይቆጥባሉ።ሠአት ያከብራሉ።የአሠራር ሥልቶች መሻሻል አየር መንገዶች ይበልጥ አስተማማኝ ያደርጋቸዋል።ይሕ ማለት ሐገራት በሙሉ የበረራዎችን ቴክኒካዊ ሥልት በጋራ የማሻሻል አለማ ይኖራቸዋል ማለት ነዉ።
የSingel European Sky (አንድ የአዉሮጶች ሠማይ) እንበለዉ ይሆን? ብቻ ሰነድ ፈራሚዎች የበረራ ደንቦችንና መስመሮች መቀናጀታቸዉና በአንድ የኮምፒዉተር ሥርዓት መመራታቸዉን ይቀበሉታል። እቅዱን እንዲከታተል የተሰየመዉ ቡድንም እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር እስከ 2012 ድረስ የአዉሮጳን የአየር ክልል በዘጠኝ አካባቢዎች አቀናጅቶ ለማጠናቀቅ ቀን ቆርጧል።
የቡድኑ የአየር መቆጣጠሪያ ክፍል ተጠሪ ቦ ሬድዩ-ቦርን እንደሚሉት ግን ማቀናጀቱ ከችግር የፀዳ አይደለም።
«ሁሉም ሥልታችን በጋራ መደራጀቱ በሚሰጠዉ ጥቅምና ሥራዎቹን በማቀናጀቱ ሐሳብ ይስማማሉ።የሚስማሙት ግን መቀናጀቱ የየራሳቸዉን እቅድ እስካልነካ ድረስ ነዉ።ሥለዚሕ ሁሉም የሚያስቡት ነገሮቹን እነሱ በሚያደርጉበት መንገድ እያደረጉ ቀሪዎቹ ከነሱ አሰራር ጋር ተጣጥመዉ ይሔዳሉ ብለዉ ነዉ።»

ችግሩ ወይም ልዩነቱ በርግጥ ትንሽ ነዉ።ከአይስላንድ የፈለቀዉ የእሳተ ጎመራ አመድ ያደረሰዉ መንገደኞች ትርምስ ግን ትንሹን ልዩነት አንሮ አጠቃላዩን እቅድ ያዘገየዋል የሚል ግምት ነበር።ትናንት የተሰበሰቡት ሚንስትሮች ግን ለ2012 የተያዘዉ እቅድ በተያዘለት ጊዜ እንዲከናወን ተስማምተዋል።

Stefanie Siek

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ