1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ መሪዎች እና ICC

ሰኞ፣ ጥቅምት 4 2006

በዘር ማጥፋት፥በሰብአዊ ፍጡር ላይ በተፈፀመ ወንጀል እና በጦር ወንጀል የሚጠረጠሩ ፖለቲከኞችን እንዲመረርምር፥ በተረጋገጠባቸዉ ላይ እንዲፈርድ የተቋቋመዉ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ግን እስካሁን ክስ የመሠረተዉ በስምት የወንጀል ጭብጦች ነዉ።በስምንቱም ጉዳዮች የከሰሳቸዉ፥ ወይም የፈረደባቸዉ ፖለቲከኞች በሙሉ ግን አፍሪቃዉያን ናቸዉ።

https://p.dw.com/p/19zOm
African Union in Addis Abeba, Ethiopia Bild: Autor/Copyright: Getachew Tedla HAILEGIORGIS( Äthiopien DW Korri.)
የአፍሪቃ ሕብረት ጽ/ቤትምስል DW

በ1919 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያን አቆጣጠር ነዉ) የጦር ወንጀለኞችን የሚቀጣ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት እንዲቋቋም ሐሳቡ ሲነሳ፣ ሲወድቅ፣ በ1948 ዳግም ሲነሳ፣ ደንቡ ሲረቀቅ፣ ረቂቁ ሲወድቅም አብዛኞቹ አፍሪቃዉያን ከአዉሮጳ ቅኝ ገዢዎች ነፃ ለመዉጣት ገና እየገደሉ ይሞቱ ነበር።1975 በደራዉ ክርክር ዉስጥም አፍሪቃዉያን አልነበሩበትም።በ1998 የመመሥረቻ ዉሉን ለመፈረም፣ በ2002 ለማፅደቅ ግን አፍሪቃ ይንጋጋ ገባ።ለፍርድ ቤቱ በርካታ አባላትን በማሰለፍ አፍሪቃ አንደኛ ናት።ፍርድ ቤቱ ከአፍሪቃዊ ዉጪ በአንድም የሌላ አሐጉር ወንጀለኛ ላይ አልበየነም።አንድም የሌላ አሐጉር ተጠርጣሪ አልተከሰሰም። ከአፍሪቃዉያን ሌላ አንድም ሐገር ፍርድ ቤቱን አልተቃወመም። ድንቅ መስተጋብር።እንበል ይሆን?

የአፍሪቃ መሪዎች የዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት (ICC) አባል ለመሆን ሲሽቀዳደሙ ከዚያ በፊትና በሕዋላም-ዩጋንዳ አንድ መሪ ነበሯት።አሏትምም።ፕሬዝዳት ዩዌሪ ካጉታ ሙሴቬኒ።ፍርድ ቤቱ የሱዳኑ ፕሬዝዳት ዑመር ሐሰን አልበሽር በተገኙበት እንዲያዙ የእስራት ዋራንት ሲቆርጥባቸዉም ሙሴቬኒ በነበሩ-ባሉበትም ሥልጣን ላይ ነበሩ።ምናልባት የረጅም ጊዜ ተቀናቃኛቸዉ በመዋረድ፥ መከሰሳቸዉ ተደስተዉ ይሆን-ይሆናል።በይፋ ያሉት ግን አልነበረም።

የሙሴቪንን መንግሥት በሐይል አስወግዶ ዩጋንዳን በመፅፍ ቅዱሱ አስርቱ ትዕዛዛት መሠረት ለመግዛት የሚፋለመዉ የሐሪቱ አማፂ ቡድን መሪዎች በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት እንዲዳኙ የጠየቁትም ራሳቸዉ ሙሴቬኒ ነበሩ።የኬንያ ፖለቲከኞች በምርጫ ዉጤት ሰበብ ጎሳን ከጎሳ አጋጭተዋል፥ ሰዉ አስገድለዋል በሚል ጥርጣሬ ሲከሰሱም የዩጋንዳ መሪ በይፋ ያሉት አልነበረም።

ተከሳሾቹ የኬንያን የፕሬዝዳትነትና የምክትል ፕሬዝዳትነት ሥልጣን ከያዙ በኋላ ግን አንጋፋዉ ፕሬዝዳንት የደገፉትን፥ ሐገራቸዉን አባል ያደረጉበትን፥ ተቃዋሚዎቻቸዉ እንዲከሰሱ የጠየቁትን፥ ፍርድ ቤት ይተቹ፥ በዘረኝነት ይወቅሱ ገቡ።

«(የኬንያዉ ግጭት) ሕጋዊ ጉዳይ አይደለም።ርዕዮተ-ዓለማዊ ነዉ።መያዝ ያለበትም በዚሕ መሠረት ነዉ።እነዚሕ የICC ሰዎች ግልብ ናቸዉ።»ሌላ ጊዜም ቀጠሉ።ጠንከር፥ ከረርም አሉ።«እኒያ ሥለ ጎሳ እና ሐራጥቃ የሚያወሩ የአፍሪቃ ጠላቶች ናቸዉ።በግል ደግሞ የኔ፥ የእናንተም ጠላቶች ናቸዉ።»

የተከበሩት የዩጋንዳ መሪ አይነቱ አቋም በጎቲንገን-ጀርመን ዩኒቨርስቲ የወንጀለኝ ጉዳይ የሕግ-ባለሙያ ካይ አምቦስ እርስ በርሱ የሚቃረን ይሉታል።«ICC የዩጋንዳ አማፂያንን እንዲከስ ጉዳዩን ለፍርድ ቤቱ የመሩት የዩጋንዳዉ ፕሬዝዳት ራሳቸዉ ናቸዉ።እና አሁን የሚሰነዘረዉ ትችት በጣም (ከድርጊቱ) የሚቃረን ነዉ።አሁን የአፍሪቃ ሕብረት ዉስጥ የሚደረገዉ ICC የመቃወም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ነዉ።በተለይ በግልፅ የሚታየዉ ጉዳዩ ከነካቸዉ (ከተከሠሱት) መንግሥታት።»

በሴራሊዮኑ የርስ በርስ ጦርነት የተደረሰዉን ግፍ የሚመረምረዉ የሴራሊዮን ጉዳይ ፍርድ ቤት የቀድሞዉን የላይቤሪያ ፕሬዝዳት ቻርልስ ቴለርን የከሰሰ፥ ያሰረዉም፥ የቀድሞዉ የየኮትዲቯር ፕሬዝዳት ሎራ ባግቦም ከሥልጣን የተወገዱ፥ የተከሰሱ የታሰሩትም በአፍሪቃዉያን መሪዎች ትብብር ነበር።በዚሕም ሰበብ ያኔ ፍርድ ቤቱን የወቀሰ፥ የተቸም አልነበረም።

የሱዳኑ ፕሬዝዳት ዑመር ሐሰን አልበሽር ዳርፉር ዉስጥ ተፈፅሟል በተባለዉ ወንጀል ጥርጣሬ ሲከሰሱ፥ በተገኙበት እንዲያዙ ፍርድ ቤቱ ሲያዝ ግን አንዳድ የአፍሪቃ መሪዎች ማንገራገር ጀመሩ።አፍሪቃ ዉስጥ በሥልጣን ላይ ያለዉን መንግሥት በጠመንጃ ዉጊያ አለያም በፖለቲካዊ አመፅ፥ ወይም በምርጫ ለማስወገድ የተደራጀ ሐይል የሌለበት ሐገር ጥቂት ነዉ።

አል-በሽር የዳርፉር አማፂዎችን ለመቅጣት በወሰዱት እርምጃ ከተከሰሱ ጠላት ወይም ተቃዋሚዎቹን ለማጥፋት የሚታገለዉ አፍሪቃዊ መሪ ነግ በኔ ማለቱ አይቀርም።የነቻርልስ ቴለርን ጉዳይ ችላ ያሉት ብዙዎቹ የአፍሪቃ መሪዎች ክሱ አልበሽር ላይ ሲደርስ የማንገራገራቸዉ ትክክለኛ ምክንያት ነግ በኔ የማለት ሥጋት ሊሆን ይችላል።በይፋ የተሰጠዉ ሰበብ ግን ISS በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ ዓለም አቀፍ የፀጥታ ጥናት ተቋም ባልደረባ ዶክተር ሰለሞን ደርሶ እንደሚሉት የዳርፉርን የሠላም ሒደት ያደናቅፈዋል የሚል ነበር።

የመጀመሪያዉ የዓለም ጦርነት አሸናፊዎች ብሪታንያ፥ ፈረንሳይና ዩናይትድ ስቴትስ ሌሎች ሠላሳ ሁለት ወዳጆቻቸዉን አስከትለዉ ዓለም የጦር ወንጀለኞች የሚዳኙበት የጋራ ፍርድ ቤት እንዲኖራት በ1919 ሲመክሩ አብዛኞቹ አፍሪቃዉን በአዉሮጳዉያን ቅኝ ገዢዎች ይረገጡ ነበር።ፍርድ ቤት ይቋቋም የሚለዉን ሐሳብ ቀድመዉ ያነሱት የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናት ነበሩ።የፍርድ ቤቱ ማቋቋሚያ ጥናት ሲቀርብ ግን አሜሪካኖች ተቃዋሚ ሆኑ።ሐሳቡም፥ በሐሳብ ቀረ።

ሐሳቡ በ1948 በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አማካይነት ዳግም ተነስቶ የፍርድ ቤቱ ማቋቋሚያ ደንብ እስከ መረቀቅ ደርሶ ነበር።ረቂቁ በሁለተኛ ዓመቱ ሲጠናቀቅ ግን ዓለም በቀዝቃዛዉ ጦርነት በምትናጥበት በዚሕ ወቅት የጋራ ፍርድ ቤት ማቋቋም አይቻልም ተብሎ ቀረ።

በ1975 እንደገና ሐሳቡ ተነሳ፥ እንደገና ተዳፈነ።የኮሚንስቱ ጎራ ከተፈረካከሰ በሕዋላ ግን ፍርድ ቤቱን የማቋቋሚያዉ ዉል በ1998 ተፈረመ።በሁለት ሺሕ ሁለት ፍርድ ቤቱ ተቋቋመ።የፍርድ ቤቱን መቋቋም የተቃወሙት ሰባት ሐገራት ብቻ ነበሩ።ቻይና፥ ኢራቅ፥ እስራኤል፥ ሊቢያ፥ ቀጠር፥ ዩናይትድ ስቴትስ እና የመን።ሐሳቡን ስታነሳ-ስትጥል፥ ሥታስረቀቅ-ስታግድ የነበረችዉ ዩናይትድ ስቴትስ የፍርድ ቤቱን መቋቋም ስትቃወም አብዛኞቹ አፍሪቃዉያን ግን መስራቾች ሆኑ።

የዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሑዩማን ራይትስ ወች ባልደረባ ኤልዛቤት ኤቬንሰን እንደሚሉት አፍሪቃዉያን ከፍርድ ቤቱ አባል ሐገራት መካከል ከፍተኛዉን ቁጥር የያዙ ናቸዉ።

«የአፍሪቃ ሐገራት ከመሥራቾቹ ሐገራት መሐል ናቸዉ።እነሱ (ICC) ለመቋቋሙ መንገድ ጠርገዋል።ከፍተኛ ቡድንም ናቸዉ።»

እርግጥ ነዉ፥ የዩጎዝላቪያ፥ የሩዋንዳ፥ የሴራሊዮን ወዘተ እየተባሉ የተቋቋሙት ፍርድ ቤቶች በየሐገራቱ የተፈፀሙ ወንጀሎችን መርምረዉ ብይን ሰጥተዋል።ይሰጣሉም።በዘር ማጥፋት፥በሰብአዊ ፍጡር ላይ በተፈፀመ ወንጀል እና በጦር ወንጀል የሚጠረጠሩ ፖለቲከኞችን እንዲመረርምር፥ በተረጋገጠባቸዉ ላይ እንዲፈርድ የተቋቋመዉ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ግን እስካሁን ክስ የመሠረተዉ በስምት የወንጀል ጭብጦች ነዉ።

የከሰሳቸዉ፥ ወይም የፈረደባቸዉ ፖለቲከኞች በሙሉ ግን አፍሪቃዉያን ናቸዉ።ክስና ብይኑ በተለይ የኬንያ ፕሬዝዳት ኡሁሩ ኬንያታንና ምክትላቸዉን ዊሊያም ሩቶን መንካቱ ያስቆጣቸዉ የአፍሪቃ መሪዎች ፍርድ ቤቱን በዘረኝነት ለመወቅስ ሰበብ-ምክንያታቸዉም ይኸዉ ነዉ።የአፍሪቃ ሕብረትን ተዘዋዋሪ የሊቀመንበርነት ሥልጣን የያዘችዉ የኢትዮጵያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ቴዎድሮስ አድሐኖም ፍርድ ቤቱን የፖለቲካ መሳሪያ ሆኗል እስከማለት ደርሰዋልም።

የኬንያ ምክር ቤት ሐገሪቱ ከፍርድ ቤቱ አባልነቷ እንድትወጣ በቅርቡ ወስኗል።ሌሎቹ የፍርድ ቤቱ አባላት የሆኑት ሠላሳ ሰወስቱ የአፍሪቃ ሐገራትም የኬንያን ፈለግ ይከተላሉ የሚል ሥጋት ነበር። አፍሪቃ ከፍርድ ቤቱ ጋር ሥለሚኖራት ግንኘት ለመነጋገር ባለፈዉ ቅዳሜ ተሰይሞ የነበረዉ የአፍሪቃ ሕብረት አባል ሐገራት የመሪዎች ጉባኤ ግን አባል ሐገራት ከፍርድ ቤቱ አባልነት እንዲወጡ አልወሰነም።

ይሁንና ጉባኤዉ በስልጣን ላይ ያሉ አፍሪቃዉያን መሪዎች እንዳይከሰሱ ጠይቋል።ጥያቄዉን ዓለም አቀፉን ፍርድ ቤት ባንድ ወይም በሌላ መልኩ በበላይነት ለሚመራዉ ለፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት የሚያቀርቡ መልዕክተኞችም ወደ ኒዮርክ እንዲሔዱ ጉባኤዉ ወስነዋል።ዶክተር ሰለሞን ደርሶ እንደሚሉት የአፍሪቃ መሪዎች የቅዳሜ ዉሳኔ በጎም-መጥፎም ነዉ።

«ከፍርድ ቤቱ አባልነት በጅምላ መዉጣት የለም።ይሕ ቀና ነገር ነዉ።ይሁንና ከቀረበዉ ጥያቄ አኳያ ማለት በሥልጣን ላይ ያሉ መሪዎች እንዳይከሰሱ መጠየቁ ሲታይ፥ የአፍሪቃ ሕብረት ወይም አባላቱ ከICC ጋር የፈጠሩትን የልዩነት ክፍተት ለመድፈን በጣም አስቸጋሪ ያደርገዋል።»

የሕግ ባለሙያ ሐርሜን ፋን ዴር ቪልት እንደሚሉት ደግሞ በወንጀል የሚጠረጠርን ሰዉ ሥልጣን እሰከሚለቅ መከሰስ የለበትም ማለት ተገቢ አይደለም።ሥልጣን የወንጀለኞች ወይም የተጠርታሪዎች መሸሸጊያ መሆን የለበትምና።

«ሥልጣን ላይ እስካለሕ ድረስ ሥልጣንሕ በወንጀል ከመከሰስ መከታ ሊሆን አይገባም።እንደሚመስለኝ የአፍሪቃ ሕብረት ዓላማ ዓለም አቀፉን ፍርድ ቤት ከተገቢዉ ተልዕኮዉ ማሳት ነዉ።»

አሳተም-አላሳተ የአፍሪቃ መሪዎች ጉዳዩን ሥራዬ ብለዉ መያዛቸዉ እርግጥ ነዉ።መሪዎቹ ለቅዳሜዉ ጉባኤና ዉሳኔ የደረሱትም ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት በተለይ በኬንያ መሪዎች ላይ የመሠረተዉን ክስና የሚያደርገዉን ምርመራ ለሌላ ጊዜ እንዲያስተላልፍ ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ነዉ።

አሁን ማስጠንቀቂያ አዘል ጥያቄያቸዉን የሚያቀርቡት ለፍርድ ቤቱ አይደለም።ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ነዉ።በምክር ቤቱ ዉስጥ ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ካላቸዉ ከአምስቱ ሐያላን በጣም ሐይለኞቹ፥ ቻይና፥ ሩሲያና ዩናይትድ ስቴትስ የፍርድ ቤቱ አባላት አይደሉም።

ይሁንና የአፍሪቃዉያኑ ጥያቄ ለድምፅ ከቀረበ ሐርሜን ፋን ዴር ቪልት እንደሚሉት ጥያቄዉን ዉድቅ ለማድረግ ፍርድ ቤቱን ከሚደግፉት ከፈረንሳይና ከብሪታንያ ያንዳቸዉ ተቃዉሞ በቂ ነዉ።

«ብሪታንያና ፈረንሳይ የዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ደጋፊዎች ናቸዉ።ዉሳኔዉን ሊሽሩት ይችላሉ።»

የአፍሪቃ መሪዎች አምባገነን ሊሆኑ ይችላሉ።ያሁን ጥያቄያቸዉ ከቀድሞ አቋማቸዉ መቃራኑም አያነጋግርም።ጥያቄቸዉን ለመስማት ወይም ላለስማት፥ ለመቀበልም-ሆነ ላለመቀበል በፍትሑም፥ በዓለም ማሕበሩም መድረክ ዛሬም ወሳኞቹ አፍሪቃን ለዘመናት በቅኝ ገዢነት ሲረግጡ የነበሩት የለንደን እና የፓርስ መንግሥታት መሆናቸዉ በርግጥ ያስተዛዝባል።ግን ለዛሬ ይብቃን።ከዛሬ ጀምሮ ሥለ ዝግጅታችን ያላችሁን አስተያት፥ እንጠብቃለን።ማሕደረ ዜና ቢያስተናገደዉ ጥሩ ነዉ ብላችሁ የምታስቡትን ጉዳይም ጠቁሙን።የሥልክ፥ የደብዳቤና የኤስ ኤም ኤስ አድራሽችን የተለመደዉ ነዉ።

Congolese warlord Thomas Lubanga sits in the courtroom of the International Criminal Court (ICC) in The Hague, Netherlands, Thursday, Aug. 25, 2011. Prosecution lawyers are wrapping up the ICC's landmark first trial by urging judges to convict a Congolese warlord of recruiting child soldiers and sending them to fight in his country's brutal conflict. Lubanga's trial was the first international case to focus exclusively on child soldiers. (Foto:Michael Kooren, Pool/AP/dapd)
ቶማስ ሉባንጋ-የተፈረደባቸዉምስል dapd
Former Kenyan Education Minister William Samoei Ruto sits in the courtroom of the International Criminal Court (ICC) in The Hague, Netherlands, Thursday, Sept. 1, 2011. Ruto is one of three senior Kenyan leaders appearing at the International Criminal Court for a hearing at which judges will decide whether evidence against them is strong enough to merit putting them on trial on charges of orchestrating deadly violence in the aftermath of disputed 2007 elections. (Foto:Bas Czerwinski/AP/dapd)
ዊሊያም ሩቶ-ተከሳሽምስል AP
epa02623841 (FILE) A file photo dated 15 December 2010 shows Kenya's Finance Minister and Deputy Prime Minister Uhuru Kenyatta arriving at a press conference on the day the International Criminal Court (ICC) announced six prominent Kenyans, which included Kenyatta, who are said to be responsible for masterminding the country's 2007/08 post-election violence that left some 1,300 dead. According to a local report, five suspects, Kenyatta, former higher education minister William Ruto, suspended Industrialisation Minister Henry Kosgey, former police commissioner Maj-Gen Hussein Ali, and Head of Operation at KASS FM radio Joshua Arap Sang said on 09 March 2011 that they will honor summonses issued for the charges of crimes against humanity by the pre-trial chamber of the ICC. The sixth suspect is the Secretary to the Cabinet and Head of the Civil Service Francis Muthaura. EPA/DAI KUROKAWA
ኡሁሩ ኬንያታ-ተከሳሽምስል picture-alliance/dpa
Former International Criminal Court's chief prosecutor Luis Moreno-Ocampo (L) listens as Fatou Bensouda (R) is holding her first speech as new prosecutor after her swearing-in ceremony as the International Criminal Court's new chief prosecutor in The Hague, on June 15, 2012. The 51-year-old Bensouda is the first woman and the first African to head the team of prosecutors at the tribunal, which is currently investigating 15 cases in seven countries, all of them African. Taking the oath before ICC judges and a public gallery packed with foreign diplomats and dignitaries, Bensouda vowed to continue to pursue those wanted for crimes of genocide, war crimes and crimes against humanity. AFP PHOTO/POOL/BAS CZERWINSKI netherlands out (Photo credit should read BAS CZERWINSKI/AFP/GettyImages)
አዲሲቱ የፍርድ ቤቱ ጠቅላይ አቃቢት ሕግ ፋቶ ቤንሶዳ-ምስል Bas Czerwinski/AFP/GettyImages)
Sudan's President Omar al-Bashir attends the African Union summit in Addis Ababa, Ethiopia, Sunday, July 15, 2012. Delegates at the African Union summit are likely to focus attention on continuing hostilities between Sudan and the year-old state of South Sudan. (Foto:Elias Asmare/AP/dapd)
አል-በሽር፤ የእስራት ዋራንት የተቆረጠባቸዉምስል dapd

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ