1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብትና የዉጪ ባለሐብቶች

ማክሰኞ፣ የካቲት 11 2006

እየጠረቃ ከመጣዉ የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብት ከብዙዎቹ ቀድማ የገባች ብዙ የተጠቀመችና የምትጠቀም አዲት ሐገር አለች። ቻይና።እንደ ጎሮጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በሁለት ሺሕ አስራ-ሁለት ቻይና ከአፍሪቃ ጋር ያደረገችዉ የንግድ ልዉዉጥ ሁለት መቶ ቢሊዮን ዶላር ነዉ።

https://p.dw.com/p/1B8sU
Sambesi Brücke in Tete
ምስል DW/Johannes Beck

እያደገ የመጣዉ የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብት የበለፀገዉን ዓለም ባለሐብቶች ትኩረት እየሳበ ነዉ።የዚያኑ ያክል ደቡብ ሱዳን እና ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክን የሚያብጠዉ ዓይነት ጦርነት የምጣኔ ሐብቱን ዕድገትም የወራቾችን ፍላጎትም ይቀንሳል የሚል ሥጋት ማሳደሩ አልቀረም።የቻይና ኩባንዮች ግን ግጭት ጦርነት ብዙም የሚያስፈራቸዉ አይመሰሉም።የጀርመን ኩባንዮች ባንፃሩ አፍሪቃ ዉስጥ ለመወረት ድፍረቱም፥ ጉጉት ፍላጎቱም ብዙ የላቸዉም።

ከሠሐራ-በስተደቡብ የሚገኙት የአፍሪቃ ሐገራት ምጣኔ ሐብት ላለፉት ተከታታይ ዓመታት በየዓመቱ በአማካይ ስድስት በመቶ እያደገ ነዉ።ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ) እንደተነበየዉ ዕድገቱ ወደፊትም ይቀጥላል።እየጠረቃ ከመጣዉ የአፍሪቃ ምጣኔ ሐብት ከብዙዎቹ ቀድማ የገባች ብዙ የተጠቀመችና የምትጠቀም አዲት ሐገር አለች። ቻይና።እንደ ጎሮጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በሁለት ሺሕ አስራ-ሁለት ቻይና ከአፍሪቃ ጋር ያደረገችዉ የንግድ ልዉዉጥ ሁለት መቶ ቢሊዮን ዶላር ነዉ።

የሐቻምናዉ የንግድ ልዉዉጥ የዛሬ አስራ-ሰወስት ዓመት ግድም ከነበረዉ በሃያ በመቶ የተንቻረረ ነዉ።የቻይና ኩባንዮች በብዙ የአፍሪቃ ሐገራት መንገዶችን እና ሌሎች የመሠረተ ልማት አዉታሮችን ይገነባሉ።ከዚሕም ጠቀም ያለ ገቢ በተለይም ጥሬ ሐብት ይዝቁበታል።የቻይናዉ የአስመጪና ላኪ ባንክ ባልደረባ ዣኦ ቻንኹይ እንደሚሉት የአፍሪቃን ጥቅም የቻይኖችን ያክል ያወቀ የለም።

«አፍሪቃ ማለት ንግድ ናት።አፍሪቃ ማለት የገበያ ዕድል ናት፥ አፍሪቃ የወደፊት ተስፋም ናት።ብዙ ቻይናዉያን ከዚሕም አልፈዉ የቻይና የወደፊት ተስፋ በአብዛኛዉ ከአፍሪቃ ጋር የተቆራኘ ነዉ ብለዉ ያምናሉ።»

ዣኦ ባንካቸዉ አፍሪቃ ዉስጥ ሊገጥመዉ የሚችለዉን አደጋ ያጠናሉ፥ ይተነትናሉም። ፖለቲካዊ ቀዉስ፥ሙስና የሐይልና የመሠረተ ልማት አዉታር እጥረት ጥንቃቄ የሚያሻቸዉ አደጋዎች ናቸዉ።ቻይኖች እየሰሩ ከአደጋዎቹ ይጠነቀቃሉ።ጀርመኖች ግን ይሸሻሉ።«የግንዛቤ እጥረት» ይሉታል ዣኦ-ሽሽቱን።

«እንደሚመስለኝ ይሕ (ሽሽቱ) ሥለ አፍሪቃ በቂ ግንዛቤ ከመጣት እና እዚያ የሚያጋጥመዉን እዉነተኛ አደጋ አግዝፎ ከማየት የሚመነጭ ነዉ።ሁሉም ሐገር እንደ ጀርመን ይሆናል ብለሕ ተስፋ ልታደርግ አትችልም።»

የደቡብ ሱዳን ጦርነት በርግጥ ከባድ ነዉ።የቻይና መንግሥት የምድር ባቡር ኩባንያ ግን ጦርነት ተጀመረ ብሎ ደቡብ ሱዳን ዉስጥ የጀመረዉን የባቡር ሐዲድ ግንባታ አላቋረጠም።ግንባታዉ አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር ያወጣል።ጀርመኖች ቢሆኑ ግን አያደርጉትም።በደቡባዊ አፍሪቃ የጀርመን ምጣኔ ሐብታዊ ጉዳይ ተቋም ዋና ፀሐፊ አንድሪያስ ቬትስል የጀርመኖች ከአፍሪቃ መራቅ የቆጫቸዉ ይመስላሉ።

«እነዚሕ ሐገራትን በኢንዱትሪ ለማበልፀግ በሚደረገዉ ሒደት መሳተፊያዉ ወቅት አሁን ነዉ። ተሳትፎዉ ከተጠናከረ በከፍተኛ ቴክኖሎጂ ላይ የተመሠረተዉን የጀርመንን ምጣኔ ሐብትን ማራኪ ያደርገዋል።»

ጀርመን ከቻይና ጋር ሲነፃፀር ከአፍሪቃ ጋር ያላት የንግድ ልዉዉጥ ኢምንት ነዉ።አብዛኖቹ (ስድስት መቶ ያሕሉ) የጀርመን ኩባንዮች የሚሠሩት ደቡብ አፍሪቃ ዉስጥ ነዉ።ደቡብ አፍሪቃም ቢሆን ቻይናን የመሳሰሉ ሌሎች ተፎካካሪዎች በሰፊዉ ሥለሚሳተፉ የጀርመን ድርሻ የወትሮዉን ያክል አይደለም።

አሁን ደግሞ፥ ፍሮንታየር አድቫይሰሪ የተሰኘዉ ተቋም የጅሐንስበርግ ባልደረባ ማርቲን ዴቪስ እንደሚሉት ደቡብ አፍሪቃም የዉጪዉን ኩባንያ በሞኖፖል የምትቆጣጠርበት ዘመን አብቅቷል።

«የአንዳድ የአፍሪቃ ሐገራት ምጣኔ ሐብት የደቡብ ምሥራቅ እስያን ምጣኔ ሐብት ደረጃን ሲይዝ እናያለን።ማነዉ ተጠቃሚዉ? ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ ናት።ሌሎች ሐገራት ምናልባት ኬንያም ስትዳብር እናያለን።እርግጥ ነዉ ደቡብ አፍሪቃ ከፍተኛዉን ድርሻ እንደያዘች ትቀጥለለች።ይሕ ግን በትልቅነቷ እንጂ በዕድገቷ አይደለም።»

Symbolbild - Indien Afrika Wirtschaftsbeziehungen
ሕንዶችም ያማትራሉምስል Getty Images
China Investition in Afrika
ቻይኖች አፍሪቃ ዉስጥ ይሠራሉምስል John Lukuwi/AFP/Getty Images

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ