1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ ሴት የንግድ ሥራ ፈጣሪዎችና ተግዳሮቶቻቸው

ቅዳሜ፣ ኅዳር 24 2015

የአፍሪቃ አኅጉር ነጻ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) ከ2 ዓመት በፊት ይፋ ሲደረግ በርካታ በአኅጉሪቱ የሚኖሩ ሴት የንግድ ሥራ ፈጠራ ባለሞያዎች ብዙ ተስፋ ሰንቀው ነበር። በዓለማችን ግዙፍ ይሆናል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው የንግድ ቀጠና ታኅሣስ 23 ቀን፣ 2013 ዓ.ም ይፋ ሲደረግ ለ1.2 ቢሊዮን ሰዎች ገበያ ይፈጥራል ተብሎም ነበር።

https://p.dw.com/p/4KPZG
Straßenverkauf Afrika l Madagaskar, Imbiss
ምስል Wiese/Helga Lade Fotoagentur GmbH, Ger/picture-alliance

የ350 ቢሊዮን ዶላር አስተዋጽዖ አድርገዋል

የአፍሪቃ አኅጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) ከሁለት ዓመት ግድም በፊት ይፋ ሲደረግ በርካታ በአኅጉሪቱ ውስጥ የሚኖሩ ሴት የሥራ ፈጠራ ባለሞያዎች ብዙ ተስፋ ሰንቀው ነበር። ይህ በዓለማችን ግዙፍ ይሆናል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው የንግድ ቀጣና ታኅሣስ 23 ቀን፣ 2013 ዓ.ም ይፋ ሲደረግ ለ1.2 ቢሊዮን ሰዎች ገበያ ይፈጥራል ተብሎም ነበር። የንግድ ቀጣናው የሴት የንግድ ሥራ ፈጠራ ባለሞያዎች ንግድ እንዲያብብ እና ድህነት እንዲቀንስም ያግዛል ተብሎለት ነበር። 

ሆኖም በርካታ ሴቶች ለዶይቸ ቬለ እንደተናገሩት፦ ንግዳቸው በአብዛኛው አነስተኛ፤ የምርት ውጤታቸውም ዝቅተኛ ነው። ከመንግሥታት እና ኩባንያዎች የሚደረግላቸው ድጋፍም አነስተኛ በመሆኑ ዕድሉ እንዳመለጣቸው ገልጠዋል። ሴት የንግድ ባለቤቶች ምርቶቻቸውን ወደ ውጭ ሃገራት ለመላክ የቪዛ እና የተለያዩ ሠነዶችን ለማግኘት መቸገራቸውን ይናገራሉ።

ካሜሩን ዋና ከተማ ያውንዴ ውስጥ የሚገኘው የዶሮ እርባታ ጣቢያ ባለቤት የሆነችው የ33 ዓመቷ ባለሐብት 30,000 ግድም ዶሮዎቿ ጋቦን ውስጥ ወደ ሚገኙ ገበያዎች ለመላክ ዝግጁ ቢሆኑም እስካሁን እንዳልተላኩ ተናግራለች። ምክንያቱ ደግሞ ዶሮዎቹን ለመላክ ቪዛ እና የጉዞ ሠነዶች ለማግኘት መቸገሯ ነው።

ጾታ ላይ ያተኮሩ ተግዳሮቶች

ከ35 የአፍሪቃ ሃገራት የተሰባሰቡ ሴት ባለሐብቶች ካሜሩን ውስጥ በቅርቡ በተባበሩት መንግሥታት በተደገፈው የንግድ ጉባኤ ላይ ተሳትፈው ነበር። ባለሐብቶቹ በወቅቱ ችግሩ እንዳለ በመግለጥ አማረዋል። የኒጀር የገጠር ተቋማት ማስፋፊያ ኃላፊ ቢሶ ናካቱማ ሴት ባለሐብቶ ሀገራቸው ውስጥ ችግሮች እንደሚደርስባቸው ተናግረዋል።

Senegal 60. Unabhängigkeitstag | Markt Dakar
ሴኔጋል፦ ገበያ ውስጥ ሴቶች በሥራ ላይ ምስል picture-alliance/Godong/P. Lissac

የአፍሪቃ አኅጉራዊ የንግድ ቀጣና ተግባራት ከ2 ዓመት በፊት ምን ይመስል ነበር?

«ሴት ባለሐብቶች በአፍሪቃ አኅጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የተመቻቸውን ዕድል በመጠቀም ምርታቸውን ወደ ውጪ በሚልኩበት ወቅት በጉምሩክ ባለሥልጣናት በኩል ከፍተኛ ማንገላታት ይገጥማቸዋል። በተለይ በጉምርክ ሠራተኞች እና ፖሊሶች ጉቦ እንዲከፍሉም ዒላማ ይደረግባቸዋል። ባንኮች ለሴቶች ማበደር አይፈልጉም። ስለዚህ ሙሉ ለሙሉ በቤተሰብ፤ በማኅበረሰባቸው እና ትንሽ ባጠራቀሟት ጥሪት ላይ ጥገኞች ናቸው።»

ትውልደ-ካሜሩን የምጣኔ ሐብት ባለሞያው ሠርጌይ ጉይፎ ሴቶች የመሬት ይዞታዎች ላይ ሰፋ ያለ ዋስትና እንደሚያሻቸው ከዶይቸ ቬለ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ተናግረዋል።

«ሴቶችን ከተመለከትህ የሚመግቡን እነሱ ናቸው። መሬቱን ይጠቀማሉ ግን ባለቤት አይሆኑም። ሩዝ ከታይላንድ፤ ስንዴ ከዩክሬን ነው የምንገዛው። ያን መቀየር አለብን። ያን ለመቀየርም መሬት እና ዋስትና ያስፈልገናል።»

የንግድ ቀጣናው ከሦስት ዓመታት በፊት የነበረበት ሁኔታ

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አፍሪቃ ውስጥ ካለው ኢመደበኛ ድንበር ተሻጋሪ ንግድ 70 በመቶው የሚደረገው በሴቶች ነው ሲል ይገምታል።

ሴት የንግድ ሥራ ፈጠራ ባለሞያዎች እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር በ2022 በአፍሪቃ ኤኮኖሚ ውስጥ የ350 ቢሊዮን ዶላር አስተዋጽዖ አድርገዋል። ይህም ከአኅጉሪቱ 13 ከመቶ አጠቃላይ የምርት መጠን (GDP)ጋር የሚመጣጠን ነው ተብሏል። እናም የአፍሪቃ ሴቶች ከአፍሪቃ ነጻ የንግድ ቀጣና እድል ተጠቃሚ በመሆን አኅጉሪቱን ለማልማት ተጨማሪ እድሎች ሊመቻችላቸው ይገባል።  

ሞኪ ኪንዴዜካ

ማንተጋፍቶት ስለሺ

እሸቴ በቀለ