1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር

ሰኞ፣ ጥር 6 2005

ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ የሚካሄደው 29ኛው የአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር በፊታችን ቅዳሜ ይጀመራል። በጆሃንስበርጉ የዓለም ዋንጫ ስታዲዮም ጨዋታውን የሚከፍቱት አስተናጋጇ አገር ደቡብ አፍሪቃና ካፕ ቬርዴ ናቸው።

https://p.dw.com/p/17Jjd
ምስል Getty Images/AFP

ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ የሚካሄደው 29ኛው የአፍሪቃ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር በፊታችን ቅዳሜ ይጀመራል። በጆሃንስበርጉ የዓለም ዋንጫ ስታዲዮም ጨዋታውን የሚከፍቱት አስተናጋጇ አገር ደቡብ አፍሪቃና ካፕ ቬርዴ ናቸው። የዘንድሮው የአፍሪቃ ዋንጫ ፍጻሜ ውድድር ኢትዮጵያም ከ 31 ዓመታት ቆይታ በኋላ ለተሳትፎ የበቃችበት በመሆኑ በእግር ኳስ አፍቃሪዎቿ ዘንድ የቀሰቀሰው ስሜት እጅግ ከፍተኛ ነው። ኢትዮጵያ እንደ ግብጽና ሱዳን ከጎርጎሮሳውያኑ 1957 ዓ-ም አንስቶ የአፍሪቃ ዋንጫ ውድድር ጀማሪ ከነበሩት ሃገራት እንዷ ስትሆን በ 1962 የሶሥተኛው የአፍሪቃ ዋንጫ አሸናፊ መሆኗም ይታወሳል።

በጊዜውአዲስ አበባ ውስጥ ከግብጽ ጋር በተካሄደው ፍጻሜ ግጥሚያ ኢትዮጵያ በተጨማሪ ሰዓት 4-2 ስታሸንፍና ዝነኛው መንግሥቱ ወርቁም ወሣኟን ጎል ሲያስቀጥር ኢትዮጵያ ለብዙ ዓመታት የበላይነቱን ይዛ የምትቀጥል ነበር የመሰለው። ግን እንደገና ኢትዮጵያ ውስጥ ከተካሄደው የ 1968 ስድሥተኛ የአፍሪቃ ዋንጫ ውድድር በኋላ ሂደቱ ቀስ በቀስ አቆልቋይ ይሆናል።

የሶሥተኛው የአፍሪቃ ዋንጫ ከዋክብት መንግሥቱ ወርቁ፣ ወንድማማቾቹ ሉቺያኖና ኢታሎ፤ እንዲሁም መሰሎቻቸው በዚሁ ታሪክ ሆነው ሲያልፉ በአፍሪቃ ዋንጫ ውድድር ውስጥ ለኢትዮጵያ በጥቂቱ መነሻ-መታወሻ ሆኖ የቀረ ሌላ ነገር ካለ የመንግሥቱ ወርቁ በሶሥተኛው የአፍሪቃ ዋንጫ ቀደምት ጎል አግቢ ለመሆን መብቃትና ሉቺያኖ ቫሳሎም የስድሥተኛው አፍሪቃ ዋንጫ ድንቅ ተጫዋች ተብሎ መሰየሙ ነበሩ።

በወቅቱ ደግሞ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ትንሣዔ በአገር ውስጥ የታላቁን ዘመን ትውስትና ስሜት መልሶ ሲቀሰቅስ ቡድኑም ታሪክ ለመስራት ቆርጦ ተነስቷል። ብሄራዊው ቡድን በምን ሁኔታ ላይ ይገኛል?ተሥፋውስ እስከምን ድረስ ነው? የቡድኑን አምበል ደጉ ደበበን ዛሬ በስልክ አነጋግሬ ነበር። የኢትዮጵያን እግር ኳስ ፌደሬሺን የግንኙነት ክፍል ሃላፊ የአቶ መላኩ አየለንና የእግር ኳስ አፍቃሪዎች አስተያየቶችንም በዝግጅቱ አጠቃለናል፤ ያድምጡ!

መሥፍን መኮንን

አርያም ተክሌ