1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪካ ስደተኞች እጣ

ረቡዕ፣ መጋቢት 13 1998

የስፓኝ ቴሌቪዥን ባለፉት ጥቂት ቀናት ያቀረበዉ ዘገባና በዓለም ዙሪያ ለመታየት የበቃዉ ከአፍሪካ ወደአዉሮፓ ለመግባት የጣሩ ስደተኞች በመሃሉ የደረሰባቸዉ ፈተና አስደንጋጭ ነዉ።

https://p.dw.com/p/E0iv
ፈታኙ ድርብ አጥር
ፈታኙ ድርብ አጥርምስል AP

በመቶ የሚቆጠሩ አብዛኛዎቹ የሞሪታንያ ተወላጆች ናቸዉ በጀልባ ተሳፍረዉ ካሪና ደሴቶች ለመግባት ሲሞክሩ ከ24 የማያንሱ ሰጥመዋል። ባለፈዉ መፀዉ በሰሜን አፍሪካ የእስፓኝ ወስመጣዊ ግዛቶች በሆኑት ኮይታና መሊያ አጥር ጥሰዉ ለመግባት የሞከሩ አፍሪቃዉያን ስደተኞች በይፋ በሰጡት መግለጫ መሰረት 11 መሞታቸዉ መነገሩ ይታወሳል። አሁንም ቢሆን መሊያ አካባቢ ተደብቀዉ ወደስፓኝ ግዛት ለመግባት ያደፈጡ አፍርካዉያን አሉ ይባላል። የዶቼ ቬለዉ ስቴፈን ላይደል በስፍራዉ ተገኝቶ የዘገበዉን ሸዋዬ ለገሠ ታቀርበዋለች።
አሁን የሚታየዉ ግልፅነት ከዚህ ቀደም ያልነበረ ነዉ። እስከቅርብ ጊዜ ድረስ በመሊያ የተጐጠጐጠዉ የሽቦ አጥር Guardia Civil ከሚሰኘዉ የእስፓኝ ወታደራዊ ፖሊስ ጋር ሆኖ ስፍራዉን መጎብኘት የሚታሰብ አልነበረም።
ስለሁኔታዉ ሲጢየቁ እንኳን ለፀጥታ ሲባል ነዉ በሚል ፈሊጥ አንድ ቃል አይተነፍሱም ነበር።
አሁን የስፓኝ ፖሊሶች ስማቸዉን ለማደስ ሲባል 12ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለዉን የድንበር አጥር በአዉቶሞቢል እያዘዋወሩ እንዲያስጎበኙ ተፈቅዶላቸዋል። ጉብኝቱም የሚጀምረዉ ከድንበር መቆጣጠሪያዉ ማዕከል ነዉ።
ዙሪያ ገባዉን ለመቆጣጠር እንዲያስችል ወደድንበር ጠባቂዎቹ ማዕከል መረጃ የሚያስተላልፉ ከመቶ የሚበልጡ ካሜራዎች በድንበሩ ላይ ተተክለዋል።
አሁን ለጊዜዉ ሁሉም ሰላማዊ ነዉ ይላሉ የስፍራዉ ባለስልጣን ሁዋን አንቶኒዮ ሪቬራ
«ማንም ሰዉ ወደሽቦዉ አጥር ሲጠጋ ካሜራዉ በእርሱ ላይ ያተኩራል። ከዚያ የሚቃኝ ኃይል እንልካለን። በእግር የሚንቀሳቀስ ሰዉ ካለም የኮቴዉ ድምፅ በብርሃን ምልክት ሰጪነት በማዕከላዊዉ የመቆታጠሪያ ስፍራ ይመዘገባል።»
ባለፉት ወራት ሁሉት ዙር የታጠረዉ የድንበር አጥር ከአዉሮፓ ህብረት በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ወደላይ ከሶስት ወደ ስድስት ሜትር ከፍ ተደርጓል።
በተጨማሪም ይላሉ ሪቬራ በወፍራም ሽቦ ተደራቢ አጥር የመስራት እቅድ ተይዟል። በዚህም የታሰበዉ እንደእሳቸዉ ገለፃ ከሆነ ስደተኞቹ ለማለፍ የሚያደርጉት ሙከራ በእሾሃማዉ የሽቦ አጥር እንዳይጎዱ ለማድረግ ነዉ።
ከአጥሩ በወዲያኛዉ ወገን ደግሞ የሞሮኮ ወታደሮች የሰፈሩበት መቶ ሜትር የሚሆን ድንኳን ተተክሏል።
ተሰዳጆቹ ሳይታዩ ተደብቀዉ ወደአጥሩ እንዳይቀቡ ለመከላከል ሲባልም በአካባቢዉ የነበዉ ደን ተመንጥሯል።
በትንሽ ጉብታ ላይ እንጨቶች ተጋድመዉ ይታያሉ ያም ወደታጠረዉ የስፓኝ ክልል ለመግባት እንደመሰላል እንዲያገለግላቸዉ ስደተኖቹ ያደረጉት ነዉ።
በስፍራዉ ከሚገኙት ፖሊሶች አንዱ ሁኔታዉን ሲገልፁ
«እዚህ ቦታ ላይ አፍሪካዉያንና የሞሮኮ ወታደሮች ብርቱ ግብግብ ገጥመዉ ነበር። የሞቱና የቆሰሉ ጥቂቶች አልነበሩም። Braverheart የተሰኘዉን ፊልም ያዬ አለ? በፈረስና በሰይፍ ሳይሆን በዱላ ነዉ የዘመቱት። ፎቶግራፍ ማንሳት ይፈልጋሉ?»
ፖሊሶቹ ከበፊቱ በተሻለ ተግባቢ ሆነዋል ቢባልም ግልፅ ሆነዉ የተጠየቀዉን ሁሉ ያስረዳሉ ማለት አይደለም። ለምሳሌ ስለሞቱት ስደተኞች ሁኔታ ሲጠየቁ ዝምታን ነዉ የመረጡት።
በመረጃ ደረጃ ባለስልጣናቱ 11ሰዎች ናቸዉ የሞቱት ቢሉም ፕሮዴን የተባለዉ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ሊቀመንበር ሆሴ ፓላዞን በሞሮኮ በኩል ያለዉን ራሳቸዉ አጣርተዉና ስደተኞቹን ጠይቀዉ እንደደረሱበት ቁጥር ከተጠቀሰዉ በላይ ነዉ።
«የተገደሉ የ22ሰዎች አስከሬን ቆጥረናል። በጫካ ዉስጥ ከተለያዩ የአፍሪካዉያን ቡድኖች ጋር በተለያዩ ቦታዎችና ጊዜያት ተነጋግረናል። እኛዉ ራሳችን በጫካ የአንድ ሟች አስከሬን ፊልም አንስተናል። ፎቶግራፎች አሉን። እርግጥ ባለስልጣናቱ ሁኔታዉ ቢጣራ ባይጣራ ደንታ እንደሌላጨዉ ተገንዝበናል።»
ፓሳዞን እንዳሉት በሜሊላ የድንበር አካባቢ የሚታየዉ የፀጥታ ሁኔታ የሚያሳስት ነዉ። ከድንበር ማዶ ወደሌላ አገር ለመሰደድ የገቡት ወገኖችም በአስከፊ ሁኔታ ላይ ነዉ የሚገኙት።
ፓላዞን ከበርካታ አፍሪካዉያንና ሜሊላ ጫካዎች ዉስጥ ከተደበቁት ስደተኛ አፍሪካዉያን ጋር ይገናኛሉ። የሚያገኟቸዉም ወታደሮቹን ስለሚፈሩ በቡድን በቡድን ሆነዉ ማታ ማታ ብቻ ሲንቀሳቀሱ ነዉ።
አልፎ አልፎም ፓላትዞን ወደኮረብታዉ እየወጡ ምግብ ያቀብሏቸዋል። ስቴፈን ላይደል ሶስት ከካሜሩን የመጡ ወጣት ስደተኞችን አግኝቶ ለማነጋገር ሞክሯል።
ትክክለኛ ስማቸዉን ለመግለጽ አልፈለጉም አንደኛዉ ግን ሮበርት እንደሚባል ገለፆ ሁኔታዉን ሲያስረዳ
«በአሁኑ ቅፅበት እጅግ አስቸጋሪዉ ሁኔታ ትንሽ የሚላስ የሚቀመስ የማግኘቱ ሁኔታ ነዉ። ጥቂት ሰዎች ዳቦ ይሰጡናል። ቀደም ሲል ከቁሻሻ መጣያ እየለቀምን እንበላ ነበር። ከዚህ ቁሻሻ መጣያዉንም ወሰዱት። ትርፍራፊ የተጣለበት የቁሻሻ ማተራቀሚያ ፍለጋ ብዙዎች ራቅ ወዳለ ቦታ ይጓዛሉ።»
ሮበርት በኮረብታዉ ላይ መኖር ከጀመረ ሶስት አመታት ገደማ ሆኖታል።በዚህ ጊዜም ወደሜሊያ ለማለፍ 12 ጊዜ ሞክሯል። ድጋሚ ሙከራዉን ለማድረግ አሁንም ሁኔታዎች እስኪመቹት እየጠበቀ ነዉ።
የሞሮኮ የደህንነት ሰዎች ግን የአካባቢዉ ህዝብ ለስደተኞቹ የሚበላም ሆነ የሚጠጣ እንዳይሰጥ ከልክለዋል። የሶስቱ ሞሮኳዉያን የመያዝ እድላቸዉ እጅግ ሰፊ ነዉ።