1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪካ ጸጥታ

እሑድ፣ ጥር 25 2006

ለዘመናት ቀጣይነት ያለው የተሟላ ሰላምና መረጋጋትን ኣጣጥማ የማታውቀው ኣፍሪካ፤ ኣንዳንድ የኣህጉሪቱ ፖለቲከኞች እንደሚሉት አመጹም ሆነ ጦርነቱ በቅኝ ኣገዛዝ ዘመን ለነጻነት ነው የነበረው። ከዚያ ወዲህም ቢሆን ቅኝ ገዢዎችን ከተኩት አምባገነኖች ጋር እስከሆነ ድረስ ለዲሞክራሲ እና ለፍትህ በመሆኑ የሚጠበቅ እንጂ ኣስገራሚ ሊሆን ኣይገባም።

https://p.dw.com/p/1AzkS
Afrika - Beginn des Gipfels der Afrikanische Union
ምስል picture-alliance/dpa

ይሁን እንጂ አመጹም ሆነ ጦርነቱ በአብዛኛው ማለት ይቻላል የብሔር ኣሊያም ኃይማኖታዊ ፈርጅ እየያዘ በሰላማዊው ህዝብ ላይ ማነጣጠሩ እጅግ ኣሳሳቢ እንደሚያደርገው ብዙዎች ይስማሙበታል። ከብሔር ደረጃ ኣልፎ ወደ ጎሳ የወረደውን የሶማሊያን ቀውስም ለዓብነት ያህል መጥቀስ ይቻላል። በእርግጥ የኣፍሪካ ህብረትን ጨምሮ የ ተመድ ም ሆነ ኃያላኑ መንግስታትም ቢሆኑ በቂ ሊባል ባይችልም የሰላም ጥረት ሳያደርጉ ቀርተውም ኣይደለም። ነገር ግን ሰላም ወርዷል ሲባል መልሶ እያገረሸ፣ የሰላም ስምምነት ተፈርሟል ሲባል ውሎ ሳያድር እየተጣሰ እና በኣንዱ አካባቢ የነበረው ሲረግብ ከሌላ አቅጣጫ ሌላ ቀውስ እየፈነዳ ህዝቧ የድህነቱ ድቀት ሳያንሰው በጦርነትም ለዝርፍያ፣ ለስደት እና ለሞት ተዳርጎ ይገኛላ።

Ibrahim Boubacar Keita Präsident Mali
ምስል Reuters

የቅርብ ጊዜዎቹን እንኩዋን ብንመለከት ካቻምና በማሊ የ ቱኣሬግ ኣማጺያን እና የአረብ ዝርያ ያላቸው እስላዊ ጽንፈኞች ሰሜናዊውን የኣገሪቱን ክፍል መቆጣጠራቸው ይታወቃል። የፈረንሳይ ወታደሮች ዓምና ደርሰው ባይገፉኣቸው ኖሮ ርዕሰ ከተማይቱን ለመያዝም ጥቂት ነበር የቀራቸው። 37 የጀርመን ወታደሮችን ጨምሮ MINOSMA የተሰኘው በማሊ የ ተመድ የሰላም ኣስከባሪ ጦር ኣሁንም ድረስ ኣልፍ ኣልፎ ሙጃኦ ከሚባሉት ዓማጺያን ጋር እንደሚዋጉ ይሰማል። ለምሳሌ ያህል በ ቲምቡክቱ ከተማ እና ኢፎጋ ተራሮች አካባቢ ኣማጺያኑ እንደገና እየተደራጁ ነው የሚል ዜናም ኣለ። በዚሁ በ ተመድ የሰላም ተልዕኮ ቁጥጥር ስር ምርጫ መካሄዱ ባይቀርም በሰላም ንግግር የታጀበ ባለመሆኑ ግን የተገኘ ለውጥ እስከ ኣሁን የለም። ከዚሁ የተነሳ US አሜሪካ አዲሱ የማሊ መንግስት የሰላም ንግግሩን እንዲያፋጥን በፕሬዚደንት ኢብራሂም አቡበካር ላይ ግፊት እያደረገች ሲሆን የ ተመድ ም በሰሜን ማሊ የሚገኙ እና ያገበናል የሚሉ ወገኖች ሁሉ ለዘላቂ ሰላም ሲሉ ወደ ድርድር እንዲመጡ ጥሪ እያደረገ ነው። የማሊውን ቀውስ ውስብስብ የሚያደርገው እንደሚታወቀው የሙጃኦ ዓማጺያን በማግሪብ አካባቢ የአልቃኢዳ መሮዎች ከሆኑት ከእነ ቤልሙክታር ጋር የተቆራኙ መሆናቸው ነው።

Catherine Samba-Panza Zentralafrikanische Republik 20.01.2014 Bangui
ምስል Eric Feferberg/AFP/Getty Images

የማዕከላዊ ኣፍሪካን ቀውስም ብንመለከት በጽንፈኛ ክርስቲያኖች እና ኣክራሪ ሙስሊሞች መካከል ነው ፍልሚያው እየተባባሰ የመጣው። ከዚሁ የተነሳ ዋና ከተማዋን ባንጉዬን ጨምሮ በማይከላዊ ኣፍሪካ እስከኣሁን 1 ሚሊየን የሚጠጋ ህዝብ ለስደት ተዳርጎ ይገኛል። የሞቱትን ቤት ይቁጠረው ማለት ይቀላል። ጸጥታውን ለማስከበር 5000 የኣፍሪካ ህብረት ወታደሮች እና 1,600 የፈረንሳይ ወታደሮች በዚያች ኣገር ይገኛሉ። ሆኖም ግን ሁኔታውን ለመቆጣጠር የተቻላቸው ኣይመስልም። ለምሳሌ ባሳለፍነው ሳምንት በርዕሰ ከተማይቱ ጭምር ከፍተኛ ውጥረት በነበረበት ሁኔታ ነው ወ/ሮ ሳምባ ፓንዛ አዲሷ የኣገሪቱ ፕሬዚደንት ሆነው የተሰየሙት። ሳምባ የ ተመድ የተሟላ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ይዞ ወደ ኣገሪቱ እንዲገባ ጥሪ ለማድረግ ጊዜም ኣልፈጀባቸውም። የእሳቸውን ጥሪ ተከትሎም የጸጥታ ጥበቃው ም/ቤት በዚያች ኣገር የሚገኘው የሰላም ኣእከባር ጦር ሰላማዊውን ህዝብ ለመታደግ ኣስፈላጊውን የኃይል እርምጃ እንዲወስድ ኣዟል።

ወደ ደቡብ ሱዳን ስምመለስ ከዲንቃ ብሔረሰሰብ በሆኑት ፕሬዚደንት ሳልቫኪር እና ከኑዌር ብሔረሰብ በሆኑት የቀድሞው ም/ፕሬዚደንት ሪክ ማቻር ደጋፊዎች መካከል በተቀሰቀሰ ጦርነት በ 5 ሳምንት ውስጥ ብቻ ከ 10 ሺህ በላይ ዜጎች ሲገደሉ 700 ሺህ ያህል ደግሞ ተፈናቅሏል። በእርግጥ ከሁለት ሳምንታት በፊት አዲስ አበባ ውስጥ የተኩስ ኣቁም ስምምነት መፈራረማቸው ቢታወቅም ውለው ሳያድሩ ግን ስምምነቱን ጥሰው እየተታኮሱ እና እየተወነጃጀሉ ይገኛሉ። ደቡብ ሱዳን ውስጥም እንደ ማሊ እና ማዕከላዊ ኣፍሪካ ሪፐብሊክ ሁሉ የ ተመድ ሰላም ኣስከባሪ ጦር ቢኖርም ለየት የሚያደርገው ግን ፕሬዚደንት ኪር ከኔ በተጨማሪ የ ተመድ ም ሌላው የደቡብ ሱዳን መንግስት እየሆነ ነው በሚል የባንኪሙንን ተልዕኮ እየከሰሱ መሆናቸው ነው። የኡጋንዳ ጦር ተንደርድሮ ወደዚያች ኣገር መግባቱም ሌላው ኣከራካሪ ጉዳይ ነው። በእንወያይ ወቅታዊውን የኣፍሪካ የጸጥታ ሁኔታ ከብዙ በጥቂቱ እንቃኛለን። ኢጋድን ጨምሮ የኣፍሪካ ህብረትም ሆነ የ ተመድ እና ኃያላኑ መንግስታት ከዙህ አንጻር የሚኖራቸውን ሚናም እዳስሳለን።

Südsudans Präsident Salva Kiir Mayardit
ምስል Reuters

ጃፈር ዓሊ

ሂሩት መለሰ