የኢትዮጵያን ኢንዱስትሪ የማንቃት ጥረት
ረቡዕ፣ የካቲት 16 2008የቻይና ሲቪል ምህንድስና ኮርፖሬሽን በ246 ሚሊዮን ዶላር ከአዋሳ ሐይቅ አቅራቢያ 35 መካከለኛ ማምረቻዎች የሚያስተናግድ የኢንዱስትሪ ፓርክ ወይም ዞን በመገንባት ላይ ይገኛል። ከስምንት ወራት በፊት የግንባታ ውል ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የተፈራረመው የቻይናው ኩባንያ ሥራውን በዘጠኝ ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ አቅዷል።
ከአዲስ አበባ 275 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ በምትገኘው የአዋሳ ከተማ በመገንባት ላይ የሚገኘው እና መካከለኛ የማምረቻ ፋብሪካዎችን በአንድ ቦታ የሚያሰባስበው የኢንዱስትሪ ዞን በ250,000ሔክታር ላይ የተንጣለለ ይሆናል። እንደ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ከሆነ ማዕከሉ በውስጡ ለሚይዛቸው ማምረቻዎች ኃይል የሚያገኘው ከታዳሽ የኃይል ማመንጫዎች ይሆናል።
የኢትዮጵያ መንግስት በአገሪቱ መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ ለሚፈልጉ የውጭ ኩባንያዎች የሚያዘጋጃቸው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ ናቸው።ከግንባታ እስከ ኩባንያ መረጣ ድረስ ያለውን ሥራ የሚያከናውነው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በጎርጎሮሳዊው 2014 ዓ.ም. የተቋቋመ ሲሆን የአገር ውስጥ እና የውጭ ባለሃብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ የሚደረገውን ጥረት በበላይነት ይመራል። የኢንዱስትሪ ፓርኮቹን የማልማት እና የማስተዳደር ኃላፊነትም ተጥሎበታል። የሪፖርተር ጋዜጣ እንግሊዘኛ እትም ዋና አርታዒ አቶ አስራት ሥዩም አሁን መንግስት የጀመረው የኢንዱስትሪ ፓርኮችን መሰረተ-ልማት በተሟላለት አንድ ቦታ የማሰባሰብ ጥረት የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው ይናገራሉ።
የኢትዮጵያ መንግስት በመጀመሪያው የእድገት እና የለውጥ እቅድ ሊገነባቸው ካቀዳቸው የኢንዱስትሪ ፓርኮች መካከል ማሳካት የቻለው አንዱን ብቻ ነበር። በኢኮኖሚ ባለሙያዎች የተለጠጠ እየተባለ በተተቸው የመጀመሪያው የእድገት እና የለውጥ ውጥን ከታቀዱት ግዙፍ ግንባታዎች መካከል አንዳቸውም አልተሳኩም። ግዙፍ የስኳር ፋብሪካዎች፤ የኃይል ማመንጫዎች እና አገሪቱን ያስተሳስራሉ የሚል ተስፋ ተጥሎባቸው የነበሩት የባቡር መጓጓዣዎች ይጠቀሳሉ። አቶ አስራት ሥዩም የኢትዮጵያ መንግስት አሁን እየገነባቸው የሚገኙትን ፓርኮች እስከ ዘጠኝ ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ ማቀዱን ይናገራሉ።
የኢትዮጵያ መንግስት የኢንዱስትሪ ፓርኮቹን ለመገንባት በቦንድ ሽያጭ እና ከዓለም ባንክ የተገኙ ብድሮችን ተጠቅሟል። የፓርኮቹ መገንባት ብቻውን ግን በቂ አይመስልም። የውጭ ኩባንያዎች ከሌሎች መሰል አገሮች ኢትዮጵያን እንዲመርጡ ያሚያደርጋቸው ውድድርም አለ። የፋብሪካዎች የተረፈ ምርት አወጋገድ እና የማምረቻ ቦታዎች ጥራትም ሁነኛ ድርሻ አላቸው።
እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሠ