1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ እና የግብፅ ውጭ ጉዳይ ሚንስትሮች ውይይት

ማክሰኞ፣ ሰኔ 11 2005

የኢትዮጵያ እና የግብፅ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በአባይ ተፋሰስ የግድብ ግንባታ ላይ ከትናንት ጀምረው ሲወያዩ ከቆዩ በኋላ ዛሬ የጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

https://p.dw.com/p/18rsG
ምስል DW

ኢትዮጵያና ግብፅ፣ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ በምታስገነባዉ ግድብ ሠበብ የገጠሙትን አተካራ በዉይይት ለመፍታት መስማማታቸዉን የሁለቱ ሐገራት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮች አስታወቁ። ኢትዮጵያ የምታስገነባዉ ግዙፍ ግድብ የአባይን ወንዝ የፍሰት መጠን ይቀንሰዋል የሚለዉ ሥጋት ሁለቱን መንግሥታት ሲያወዛግብ ነበር።የሁለቱ ሐገራት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮች ትናንት አዲስ አበባ ዉስጥ ከተናገገሩ በኋላ ዛሬ በጋራ ባወጡት መግለጫ እንዳሉት ዉዝግቡን ለማስወገድ ተጨማሪ ዉይይት ለማድረግ ተስማምተዋል።

«የዉይይቱን ዉጤት መከታተል ይቻል ዘንድ ሁለቱ ሚንስትሮች ዉይይቱን ለመቀጠል እና አንዳቸዉ ከሌላቸዉ ጋር በተከታታይ ለመገናኘት ተስማምተዋል።በዚሕም መሠረት የኢትዮጵያ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ካይሮን እንዲጎበኙ የግብፅ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ያደረጉላቸዉን ግብዣ ተቀብለዋል።»

የኢትዮጵያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ቴዎድሮስ አድሐኖም በንባብ ካሰሙት የጋራ መግለጫ የተወሰደ ነበር።የግብፅ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር መሐመድ ከማል አምር ለጋዜጠኞች እንደነገሩትም ዉይይቱ በቀና እና በመተሳሰብ መንፈስ የተደረገ ነበር።

«ሁል ጊዜ የምለዉ ነገር አለ።አባይ የለም፥ ግብፅ የለችም።ኢትዮጵያዉያን ወንድሞቻችን ይሕን እንደሚገነዘቡት፥ እንደሚቀበሉትና የአባባይን ወደ ግብፅ ፍሰት እንዲቀጥል እንደሚያደርጉ እርግጠኛ ነኝ።ይሕ ዉይይት በትብብር መንፈስ፥ በወዳጅነት፥ በጋራ ፍላጎት እና ሁለቱም በሚጠቀሙበት ስሜት የተደረገ መሆኑን ላረጋግጥ እወዳለሁ።»

ሱዳንን ጨምሮ ሰወስቱ ሐገራት ቴክኒካዊ እና ፖለቲካዊዉን ዉይይት ባስቸኳይ ለመጀመር ሁለቱ ሚንስትሮች ተስማምተዋል።ኢትዮጵያ ለግድቡ ሥራ የአባይ ወንዝን ተፈጥሯዊ የፍሰት አቅጣጫ በአንድ ኪሎ ሜትር ያክል ከቀየረች ወዲሕ የካይሮና የአዲስ አበባ ፖለቲከኞች የቃላት እንኪያ ሠላንቲያ ገጥመዉ ነበር።ሁለቱ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮች ግን የሁለቱን ሐገራት ግንኙነት «ወድማዊ» ብለዉታል።

ጌታቸው ተድላ ኋይለ ጊዮርጊስ

ልደት አበበ

አርያም ተክሌ