1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤርትራ መንግስት በጋዜጠኞች ላይ የጀመረዉ ዘመቻ

ዓርብ፣ ኅዳር 15 1999

የኤርትራዉ መንግስት በመገናኛ ብዙሃን ላይ በሚያደርገዉ ተደጋጋሚ ጥቃት በያዝነዉ ወር ብቻ ቢያንስ ዘጠኝ ጋዜጠኞች እንዳሰረ Reporters without Borders ማለትም ድንበር የለሹ የጋዜጠኞች ድርጅት ረቡዕ እለት አስታዉቋል።

https://p.dw.com/p/E0hg

ባለፈዉ ሳምንት ይህ የጋዜጠኞች ድርጅት በኤርትራ ከታሰሩት ጋዜጠኞች መካከል ሶስቱ ሳይሞቱ አልቀሩም ሲል መግለጫ ማዉጣቱ የሚታወስ ነዉ። በዚህ ጉዳይ ዙርያ አዜብ ታደሰ ወደ ፓሪስ RSF በመደወል የአፍሪቃ ክፍል ሃላፊ Leonard Vincent ን አነጋግራለች


በፓሪስ ለሚገኘዉ የድንበር የለሹ የጋዜጠኖች ቡድን ለአፍሪቃ ክፍል ኃላፊ የመጀመርያዉ ጥያቄ ቢያንስ ዘጠኝ ጋዜጠኖች የኤርትራ መንግስት ማሰሩን የሚገልጸዉ ዜና ምን ያህል እዉነት ነዉ የሚል ነበር

ከባለፉት ሳምንታት ማለት ከህዳር 3 ጀምሮ፣ በአስመራ፣ ፖሊስ በህዝብ ግንኙነት መስሪያ ቤት በመምጣት እና ጋዜጠኞችን ያለምንም ምክንያት እያሰረ መዉሰዱ ተረጋግጦአል። እስካሁን ድረስ በደረሰን ጥቆማ መሰረት ዘጠኝ ጋዜጠኞች ተይዘዉ በማይታወቅ እና አስቸጋሪ በሆነ ቦታ እንዳሉ ነዉ። አሁን መጨረሻ አዲስ ጥቆማ በደረሰን መሰረት እነዚህ ታፍነዉ ተወስደዋል ከተባሉት ጋዜጠኞች መካከል የተለቀቁ እንዳሉ ነዉ። ነገር ግን እስካሁን ድረስ ተያይዞ ምንም አይነት ማረጋገጫ አልደረሰንም። ስለዚህም እዉነታዉን ለማግኘት እየሰራን ነዉ። በርግጥ! የምናዉቀዉ ግን እነዚህ በፖሊስ ተይዘዉ ወደ አልታወቀ ቦታ የተወሰዱት ጋዜጠኞች ከተያዙበት ቀን ጀምሮ እስካሁኑ ሰአት ድረስ በስራ ገበታቸዉ ላይ አልተገኙም ።

በመቀጠልም የአፍሪቃ ክፍል ሃላፊ Leonard Vincent ን ድርጅታቸዉም ሆነ በተለይ የአዉሮፓዉ ህብረት የአስመራዉ መንግስት ይህን አይነቱን ግፍ ከመስራት እንዲቆጠብ የሚያደርገዉ ጫና እንዳለ ለተጠየቁት
በፓለቲካዉ ዕረገድ በዚሁ ጉዳይ ዙርያ ስለሚደረገዉ ጫና በዝርዝር የምናዉቀዉ ነገር የለም። ነገር ግን የአዉሮፓዉ ህብረት በኤርትራዉ መንግስት ላይ ጠንካራ ነቀፊታን እያሳደረ መሆኑን እናዉቃለን የአፍሪቃዉ ህብረትም ቢሆን መግለጫ አዉጥቶ በዚህ መንግስት ላይ እርምጃ ለመዉሰድ ጥረት አድርጎአል። ነገር ግን ምንም አይነት ፍሪ ያለዉ ነገር አልተገኘም! ፕሪዝደንት የኢሳያስ አፈወርቄን ዉሳኔ ወደኳላ ለመመለስ አልተቻለም።
እና ይላሉ Leonard Vincent አሁን ለማለት የምንፈልገዉ እስካሁን ከተደረገዉ እና ከተሞከረዉ በላይ በጣንካራ እንቅስቃሴ በማድረግ፣ የአስመራዉን መንግስት፣ በሰባዊ ጉዳዮች ላይ፣ የፈለገዉን ነገር እንዳይሰራ፣ ማስቆም ነዉ! ይፋም መነገር አለበት! የአለም አቀፉም ህብረተሰብ፣ ይህንን የሚታየዉን ችግር ማስቆም መቻል አለበት ብለዋል። በመቀጠልም እ.አ አቆጣጠር ከ 2001 ጀምሮ በሚደርሰን ዘገባ እና መረጃ መሰረት ከመቶ በላይ የፖለቲካ እስረኞች ታፍነዉ በእስር ላይ እንዳሉ፣ ቢያንስ 13 ጋዜጠኞች በማይታወቅ እና በጣም አስቸጋሪ እና ፈታኝ ቦታ ላይ ታስረዉ እንዳሉ፣ ከነዚህም መካከል የሞቱም እንዳሉ ነዉ የምናዉቀዉ ብለዋል።

ዋና መስራቤቱን በፈረንሳይ ያደረገዉ ድንበር የለሹ የጋዜጠኖች ማህበር፣ ከኤርትራዉ መንግስት ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንደሌለዉ እና፣ አስቸጋሪ መንግስትም ነዉ ካለ፣ ይህን አይነቱን መረጃ ከየት ነዉ የምታገኙት ለሚለዉ ጥያቄዩ

በአስመራ ታማኝ የሆነ የዜና ምንጭ አለን! በተጨማሪ እ.አ 2001 አ.ም የኤርትራ መንግስት በተቀናቃኙ ላይ እና በጋዜጠኖች ላይ ባደረገዉ ዘመቻ ሰበብ በርካቶች ከአገሪቷ ኮብልለዉ በዉጭ አንድነት ፈጥረዉ ይገኛሉ። ለምሳሌ በአሜሪካ በሚገኙት ኤርትራዉያን የሚመራዉ የጋዜጠኞች ማህበር ጋርም፣ በጣም የጠበቀ የወዳጅነት ግንኙነት አለን። እነዚህ መረጃ የሚሰጡን ግለሰቦች በኤርትራ መንግስት እንደሚታደኑ ችግርም እንደሚፈጠርባቸዉ እናዉቃለን። ህዳር ሶስት ቀን የታሰሩትም በኤርትራ ቴሌቭዥን በአማረኛዉ፣ አረብኛዉ እና ትግርኛዉ ቋንቋ ይሰሩ የነበሩ ጋዜጠኞ ሲሆኑ አገር ልትከዱ ነዉ በሚል እንደታሰሩ ነዉ የደረሰን መረጃ ።

ባለፉት ቀናት በወጣዉ የዜና መረጃ መሰረት የኤርትራ መንግስት ከሰራቸዉ ጋዜጠኞች መካከል ሶስቱ ሞተዋል የሚል ጥርጣሪ እንዳለ ድርጅታችሁ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል። በዚህ ጉዳይ ላይ ሌላ አዲስ የተገኘ መረጃ እንዳለ ለሚለዉ

እስከ አሁን ምንም አዲስ ነገር አልሰማንም አዲስ ነገር ቢኖር ይህንን ዜና ይፋ ካደረግን በኳላ የኤርትራዉ ማስታወቅያ ሚኒስትር አሊ አብዱ በበርካታ የዜና አገልግሎት ተከበዉ እና በጥያቄ ተወጥረዉ እንደነበረ ሰምተናል። መልሳቸዉም በዚህ ዜና ላይ ምንም አይነት ሃሳብ አልሰጥም! ምንም አይነት መረጃ የለንም! የሚለዉን ቃል ብቻ እንደተናገሩ ነዉ የምናዉቀዉ። ሁኔታዎችን ለማጣራት ጥረት ላይ እንገኛለን። እነዚህ ሞተዉ ሳይሆን አይቀርም የተባሉት ግለሰቦች እ.አ 2002 አ.ም ጀምሮ ከቤተሰቦቻቸዉ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የላቸዉም ቤተሰቦቻቸዉም ለማግኘት ጥረት ቢያደርጉ አልተሳካላቸዉም።