1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የእግር ኳስ ቡድኖች ደጋፊዎች በወልዲያ ተጋጩ

እሑድ፣ ኅዳር 24 2010

የወልዲያ ከተማ እና የመቀሌ ከተማ የእግር ኳስ ቡድኖች ደጋፊዎች ወልዲያ ከተማ ውስጥ ዛሬ ተጋጩ። በግጭቱ ሰዎች መቁሰላቸውን እና ሕንፃ መቃጠሉን የዐይን እማኞች ተናግረዋል። ሁኔታውን በጣም አስጊ ነው ሲሉ የገለጹ የዐይን እማኝ እንደሚሉት ግጭቱ በደጋፊዎች መካከል ይፈጠር እንጂ የብሔር ግጭት መልክ ይዟል ብለዋል።

https://p.dw.com/p/2oguI
20.06.2013 DW Online Karten Basis Aethiopien spanisch

የወልዲያ ከተማ እና የመቀሌ ከተማ የእግር ኳስ ቡድኖች ደጋፊዎች ወልዲያ ከተማ ውስጥ ዛሬ ተጋጩ። በግጭቱ ሰዎች መቁሰላቸውን እና ሕንፃ መቃጠሉን የዐይን እማኞች ተናግረዋል። ሁኔታውን በጣም አስጊ ነው ሲሉ የገለጹ የዐይን እማኝ እንደሚሉት ግጭቱ በደጋፊዎች መካከል ይፈጠር እንጂ የብሔር ግጭት መልክ ይዟል ብለዋል። ስድብ እና ግርግር በወልዲያ ከተማ እንደነበር የተናገሩ ሌላ የዐይን እማኝ የጸጥታ ኃይሎች አስለቃሽ ጭስ መተኮሳቸውን እና ውሃ መርጨታቸውን ተናግረዋል።

የደሴ ነዋሪ እንደሆኑ የገለጡልን አድማጫችን ወልድያ የተገኙት በአጋጣሚ ነበር ወዳጃቸውን ለመጠየቅ። ጠዋት ሦስት ሰአት አካባቢ «ግርግር አለ ሲባል ለማየት» መውጣታቸውን ገልጠዋል። «የሆነ ደስ የማይል ስድብ ነበር» ሲሉም በሁለቱ ደጋፊዎች መካከል ግጭት ያጫረውን ምክንያት አክለዋል። «ከአካባቢው ራቅ ለማለት ሞከርን» ያሉት የዐይን እማኝ «ተኩሶቹ እየጨመሩ ነው የመጡት» ብለዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ በበኩላቸው፦ «ያየሁት ነገር፤ አስለቃሽ ጋዝ ይተኮስ ነበር፤ ከየት እንደሆነ ባላውቅም ጥይቶች ድምፅ ይሰሙ ነበር» ብለዋል።

የአማራ መገናኛ ብዙኃን ድርጅት ግጭቱ መከሰቱን አረጋግጦ በሁለቱ ቡድኖች መካከል ሊደረግ የታቀደው ጨዋታ «ላልተወሰነ ጊዜ» መራዘሙን ዘግቧል። የአማራ መገናኛ ብዙኃን ድርጅት ያነጋገራቸው የሰሜን ወሎ ዞን ኮምንኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ልባሴ አሊጋዝ «ጨዋታውን ለማድረግ የሚያበቃ የጸጥታ ቁመና ባለመኖሩ» ምክንያት መራዘሙን ገልጠዋል። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

እሸቴ በቀለ