1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኦሮሚያና የሶማሌ ክልል የሰላምና የፍትህ ዉይይት 

Merga Yonas Bula
ሰኞ፣ ሚያዝያ 1 2010

አዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ባለፈው ቅዳሜ ጅግጅጋ ውስጥ ባደረጉት በመጀመሪያ የስራ ጉብኝታቸዉ በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሊ አዋሳኝ ድንበሮች ላይ የተፈጠረዉ ችግር ቶሎ እልባት እንዲያገኝ አሳስበዋል።

https://p.dw.com/p/2vjkf
Abiye Ahmed in Addis Ababa
ምስል Reuters/Stinger

Peace, Justice Debate on Oromia-Somali Conflict - MP3-Stereo

ሚኒስትሩ ቅዳሜ እለት በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ዋና ከተማ በሆነችዉ በጅግጅጋ  ከማህበረሰቡ ጋር ዉይይት አድርገዋል።  የሁለቱ ክልል ህዝቦች የሚሳተፉበት የሰላም ውይይት እንዲዘጋጅ በውይይቱ ላይ የተገኙትባቀረቡላቸው ጥያቄ መስማማታቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት ንግግር ገልጸዋል።

ከዶክተር አብይ የጅጅጋ ጉብኝት በኋላ መጀመርያ ለእርቀ-ሰላም ኮንፍረንስ ቦታ መሰጠት ወይስ በግጭቱ ዉስጥ የተሳተፉትን ጥፋተኞች ለፍርድ ማቅረብ የሚለው በማህበራዊ መገናኛ ብዙሀን የመወያያ ርዕስ ሆኗል። በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ለዶይቼ ቬሌ አስተያየታቸዉን የሰጡም አሉ። ለአብነት በዶይቼ ቬሌ የዋትስኣፕ ገፅ ላይ «ከፍትህ በፈት ሠላም ይቀድማል፣ ምክንያቱም ሠላም ሲኖር ፍትህ ይኖራል» ሲሉ አስተያየታቸዉን በፅሁፍ የላኩልን አሉ።

ሞሃመድ ኢብራሂም የተሰኘ የፌስቡክ ስም የያዘ «መጀመሪያ ሠላም ይስፈን፣ ከዛ በጥንቃቀ ሕዝቡን አወያይቶ፣ ህዝቡ ራሡ ሤራ ሲሸርቡ የነበሩትን ህወሓቶችና ተላላኪ የነበሩትንም ያጋልጣሉ ብየ አምናለው» ሲል የፅሁፍ እስተያየቱን በዶይቼ ቬሌ የፌስቡክ ገፅ አስፍረዋል።

የተለየ አስተያየት የላኩልንም አሉ። ለምሳሌ ሃቤሻ ሊቤን የሚል የፌስቡክ ስም የያዘ ግለሰብ «ፍትህ ሳይኖር እንዴት ሰላም ይኖራል ብለህ ታስባለህ። ወንጀለኞች እንደ ንፁሕና ሰላማዊ ዜጋ አሁንም በሥልጣን ላይ እያሉ ስለ ሰላም ማውራት ማሾፍ ወይም ማታለያ ፕሮፓጋንዳ ከመሆን አያልፍም። ፍትህ ሲሰፍን ሁሉም ሰላም ይሆናል» ስሉም አስተያየታቸዉን ልከውልናል።

ስጀመር በህዝቦች መካከል ቅራኔ የለም የሚሉት ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለጉ ሌላ አስተያየት ሰጭ ግን  «ችግሩ ያለዉ አመራሩ ላይ ነዉ» ይላሉ።

የሕግ ባለሙያዉና ጠበቃ አቶ ተማም አባቡልጉ መጀመርያ ያጠፉት ሰዎች ወደ ለፍትህ መቅረብ አለባቸዉ ይላሉ።

«ፍትህ ይቀድማል ወይም ሰላም ይቀድማል እያሉ ቅደም ተከተል መስጠቱ ግዜ ማባከን ይሆናል» ሲሉ በዋትስአፕ ለየት ያለ አስተያየት የላኩልንም አሉ።  «እርቀ ሰላም ሲካሄድ አግረ መንገዱን በሂደት ፍትሀዊ ውሳኔዎች መካሄድ አለባቸው።» ካሉ በኋላ ሰላም የፍትህ አንዱ ክፍል ነው ብዬ አስባለሁ። ፍትህ ለመስጠት ደሞ ዜጎች በሰላም፣በሰከነ ሁኔታ  መነጋገር አለባቸው። ባለፈው በታዩት ልምዶች፣ በሰላም ስም ህዝብን አረጋግቶ፣ እንደገና ኢፍትሀዊ ስራ ለመስራት፣ ወይም ስልጣንን ለማራዘም ከሆነ ግን፣ አሁን ጊዜው ያለፈበት ይመስለኛል» ብለዋል።

መርጋ ዮናስ

ሂሩት መለሰ