1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

 የኦሮሚያ ልዩ ጥቅምና የተለያዩ ወገኖች አስተያየት

ሐሙስ፣ ሰኔ 22 2009

የኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ከተማ የሚያገኘዉን ልዩ ህገ መንግስታዊ ጥቅም የሚያስፈፅም ዝርዝር ረቂቅ ህግ ተዘጋጅቶ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መመራቱ ትናንት ይፋ መሆኑ ይታወቃል። የረቂቁ ህግ መዘግየት የክልሉን ህዝብ ያገኝ የነበረዉን ጥቅም አሳጥቶታል ሲሉ አንዳንዶቹ ደግሞ  ከአዋጁ ምንም አዲስ ጥቅም አይገኝም ሲሉ ለዶይቼ ቬለ ገልፀዋል።  

https://p.dw.com/p/2feuQ
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Englisch

Rxn-Special interest of Oromia Region in Addis Ababa - MP3-Stereo



የኦሮሚያ ክልል ከአዲስ ከተማ የሚያገኘዉ  ህገ መንግስታዊ ልዩ ጥቅም በ1987 አ/ም በጸደቀዉ የኢትጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ህገ መንግስት ሰፍሮ የቆዬ ቢሆንም ፤ይህንን የተመለከተ ዝርዝር ረቂቅ ህግ እስካሁን  አልወጣም ነበር። ጉዳዩን በተመለከተ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ መረጃወች ሲሰራጩ ቢቆይም በሀገሪቱ መንግስት እዉቅና እንደሌላቸዉ ሲገለፅ ቆይቷል። በዚህ ያዝነዉ ሳምንት ግን የህገ መንግስቱን መንፈስ ተከትሎ ረቂቅ ህግ መዘጋጀቱ ይፋ ሆኗል። በክልሉ ገዥ ፓርቲ ኦህዴድና በኦሮሚያ ክልል ፣ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና በፌደራል ደረጃ የተለያዩ  አካላት ዉይይት  ሲካሄድ ቆይቶ በመጨረሻ በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ደረጃ ዝርዝሩ ታይቶና የመንግስት ህጋዊ ተቋማት መክረዉበት ህግ ሆኖ እንዲወጣ ስምምነት መደረሱን ሰኔ 20 ቀን 2009 አ/ም በወጣዉ የመንግስት መግለጫ ተመልክቷል።የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያዘጋጀዉን  ረቂቅ ህግ ለተወካዮች ምክር ቤት መምራቱም ተገልጿል፡፡
ረቂቅ ህጉን  በተመለከተ ዶቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ም/ሊቀመንበርና የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ እንዲሁም የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/ ኦፌኮ/ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ገብሩ ገብረማርያም ኡቱራ ፤ረቂቅ ህጉን በተመለከተ ዶቼ ቬለ ካነጋገራቸዉ ዉስጥ አንዱ ናቸዉ ። ድንጋጌዉ አንቀጽ በአንቀጽ ምን እንደሚመስል በዝርዝር ካልታወቀ በስተቀር ስለ ረቂቁ ህግ የተሟላ አስተያየት ለመስጠት አስቸጋሪ መሆኑን ገልጸዉ፤ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 49 ንዑስ አንቀፅ 5 ለኦሮሚያ ተደገገዉን ልዩ ጥቅም የሚያስፈጽም ዝርዝር ህግ ከብዙ አመታት ቆይታ በኋላ በመዉጣቱ  የኦሮሞ ህዝብ ያገኝ የነበረዉን ጥቅም አሳጥቶታል ለተለያዩ ችግሮችም ዳርጎታል ብለዋል። ይሁን እንጅ ዘግይቶም ቢሆን ረቂቅ ህጉ መዉጣቱን በአወንታዊ መልኩ ያዩታል። በህዝቡ በተለይም በወጣቱ  ትግል የተገኜ በመሆኑም እንደሚኮሩበት ገልጸዋል።አተገባበሩ ላይ ግን ስጋት አላቸዉ።
ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ የኦሮሚያ ክልል ነዋሪ በበኩላቸዉ አዋጁ የወጣበት ጊዜ መዘግየት እንዳለ ሆኖ የአዲስ አበባ ከተማን የድንበር ወሰንና ከከተማዋ የሚገኘዉን ገቢ የሚመለከቱ ነገሮች በረቂቅ ህጉ ውስጥ አለመካተታቸዉን እንደ ጉድለት ያነሳሉ።
ረቂቁ ህጉ ፀድቆ  ስራ ላይ ከመዋሉ  በፊት ለዉይይት ወደ ህዝቡ መዉረድ አለበት ሲሉም አስተያየት ሰጩ አክለዋል።
ነዋሪነቱ በሆላንድ ሀገር የሆነዉ የሰብአዊ መብት አቀንቃኝ አቶ ገረሱ ቱፋ  እንደሚለዉ ረቂቅ አዋጁ  ከመሬት የመፈናቀልና የአካባቢ ብክለትን የመሳሰሉ የክልሉ ዋና ዋና ችግሮች የሚመልስ ሆኖ አላገኘዉም ።በመሆኑም አዋጁ ችግር ፈቺ አይደለም ባይ ነዉ።የክልሉ ቋንቋ በአዲስ አበባ ስራ ላይ ይዉላል ከመባሉ በቀር በአዋጁ አዲስ ነገር  አልተቀመጠም ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል።
በረቂቅ ህጉ ከአገልግሎት አቅርቦት ፣ከተፈጥሮ ሀብትና የአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም ተቋማትን ከማደራጀት አኳያ የኦሮሚያ ክልል ከከተማዋ ሊያገኝ የሚባዉ ዋናዋና ጥቅሞች ተብለዉ የተካተቱ ሲሆን ዝርዝሩ ከሁሉም ህዝቦች ጥቅም አኳያ ተዘርዝሮ የተዘጋጀ  መሆኑም ተመልክቷል።ህጉ ከመፅደቁ በፊትም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሳተፉበት  በመግለጫዉ ተገልጿል። 

Stadtansicht von Addis Abeba Hauptstadt von Aethiopien
ምስል Imago/photothek

ፀሐይ ጫኔ

አርያም ተክሌ