1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኮሶቮ ዉጊያ፥ ሰብአዊ መብትና የአለም ሕግ

ማክሰኞ፣ መጋቢት 15 2001

«1999 ሰብአዊ መብትን ከማስከበር አኳያ የሚደረግ ሰብአዊ ጣልቃ ገብነት ሕጋዊ መሆን-አለመሆኑን አሳይቷል

https://p.dw.com/p/HImN
የኮሶቮ ነፃነት ሲታወጅምስል Mimoza Dhima

የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት ኔቶ-በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ የቀድሞዋ ይጎዝላቪያ ሪፐብሊክን ጦር ከኮሶቮ ግዛት ለማስወጣት «ሰብአዊ ጣልቃ ገብነት» ያለዉን ዉጊያ የጀመረዉ-የዛሬ አስር-አመት የዛሬን ዕለት ነበር።ከኔቶ ድብደባ በኋላ ፕሬዝዳት ስሎቮዳን ሜሎሶቪች ይመሩት የነበረዉ የቤልግሬድን መንግሥት ተንኮታኩቷል።ሜሎቬች በአለም አቀፉ ፍርድ ቤት ተወንጀለዋል። ኮሶቮም ነፃ መንግሥት ለማወጅ በቅታለች። የድብደባዉ ሕጋዊና ፍትሐዊነት ግን ፋቢያን ሽሚት እንደሚለዉ አሁንም ባስር አመቱ እንዳከራከረ ነዉ።

የዛሬ-አስር አመቱ መጋቢት ሲጋመስ፥ ከሰላሳ ሺሕ የሚበልጡ የኮሶቮ ተወላጆች ከቤት ንብረታቸዉ ተፈናቅለዉ ነበር።ሌሎች በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ደግሞ ተሰደዋል።

ቀኑ-ቀን ሲተካ የሠላም ተስፋዉ ተሟጠጠ።ራምቡዬ-ፈረንሳይ ተይዞ የነበረዉ የሰላም ድርድር ያለዉጤት አበቃ።ታዛቢዎች ሰርብ መራሹ የይጎዝላቪያ ጦር በኮሶቮ ሠላማዊ ሰዎች ላይ የሚያሰርሰዉ ስቃይና ግድያ እየተባባሰ መምጣቱን በተደጋጋሚ ያስታዉቁ ያዙ።የግጭት፥ ግድያ-ዘር-ማጥፋት፥ ስደቱ ንረት በከፋ-ደም መፋሰስ ያሳርጋል ብሎ የሰጋዉ ኔቶ በታሪኩ አድርጎት የማያዉቀዉን ለማድረግ እንዲወስን ምክንያት ሆነዉ ባዮች ያኔም-ዛሬም ብዙ ናቸዉ።

ኔቶ ከአባል ሐገራቱ የግዛት ክልል ዉጪ ጦሩን ሲያዘምት የያኔዉ የመጀመሪያዉ ነበር።የኔቶ ጦር ዘመቻ «ሰብአዊ ጣልቃ ገብነት» የሚል ሥም የተሰጠዉ ዘመቻ የሰላማዊ ሰዎችን እልቂት ግድያ ለመከላከል ማለሙ ይነገር እንጂ ዘመቻዉን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት አላፀደቀዉም።ከዚሕም ባለፍ ባአንድ ሐገር የዉስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባትን የሚከለክለዉን አለም አቀፍ ደንብ የጣሰ ነዉ-የሚል ትችት አልተለየዉም።

ግራትስ-ኦስትሪያ የሚገኘዉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ባልደረባ ዮሴፍ ማርኮ እንደሚሉት የኮሶቮዉ ዘመቻ አዲስ ታሪክ የታየበት ነዉ።

ድምፅ

«ኮሶቮ ሰብአዊ መብት የማስከበሩ ጥረትን ያጠናከረ አዲስ እመርታ ነዉ።በግልፅ እንደሚታወቀዉ የፅጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ባላቸዉ አዳድ ቋሚ አባላቱ ተቃዉሞ ምክንያት ከዚሕ ቀደም እንደሚያደርገዉ በጉዳዩ ላይ አልተነጋገረም።የኔቶ ሰብአዊ ጣልቃ ገብነት በሐገራት የዉስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባትን በተመለከተ ወሳኝ የሆነ ክርክር እንዲነሳም ምክንያት ሆኗል።»

እስካሁን በተቆጠረዉ አስር አመት ያከራከረዉ ነጥብ ግን ማርኮ እንደሚሉት ዛሬም እልባት አለማግኘቱ ነዉ-እንቆቅልሹ።

ድምፅ

«1999 ሰብአዊ መብትን ከማስከበር አኳያ የሚደረግ ሰብአዊ ጣልቃ ገብነት ሕጋዊ መሆን-አለመሆኑን አሳይቷል።እንደማየዉ ግን ይሕን ጥያቄና ችግር ለመመለስ እስከ ዛሬ ድረስ ተገቢዉ ብያኔ አልተሰጠም።»

የኔቶ ጦር የቀድሞዋ ይጎዝላቪያን መደብደቡን አጥብቃ የተቃወመችዉ ሩሲያ ነበረች።ጉዳዩ ለፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ያልቀረበበትም ምክንያት በምክር ቤቱ ዉስጥ ድምፅን በድምፅ የመሻር ሥልጣን ያላት ሩሲያ ምናልባትም ቻይና ዉድቅ ያደርጉታል በሚል ግምት ነበር።ሁለቱ ሐገሮች በጣሙን ደግሞ ሩሲያ የአንድ ሐገር ሉአላዊነት፥ የግዛት አንድነት መጠበቅ አለበት የሚል ጠንካራ አቋም አላት።

ይሁንና የሞስኮ ባለሥልጣናት በቅርቡ ከጆርጂያ መገንጠላቸዉን ላወጁት ለደቡባዊ ኦስቲያና ለአብኻዚያ ግዛቶች የመንግሥትነት እዉቅና ሰጥተዋል። የቦልካን አካባቢ አዋቂ ፍራንስ ሎተር አልትማን እንደሚሉት የሩሲያ አቋም ርስበርሱ-ከመቃረንም በላይ ግራ-አጋቢ ነዉ።

ድምፅ

«ሩሲያ የሐገራት ሉአላዊነት፥ የግዛት ዳር ድንበር መደበር የለበትም የሚለዉ መርሕ እና ግዛትን መገንጠል የሚሹ ሐይላት አለማ መገታት አለበት የሚለዉ አስተሳሰብ ጠንካራ ተቆርቋሪ ናት።ይሁንና በገቢር ያደረገችዉ ግን ከዚሕ ተፃራሪዉን ነዉ።»

የሩሲያ ተፃራሪ አቋም የዛሬ አስር-አመት ኮሶቮ የተጀመረዉን ጣልቃ ገብነት ትክክለኛነት ወይም ሕገ-ወጥነት የሚያረጋግጥ አልሆነም።ክርክሩም እንደቀጠለ ነዉ።

DW

ነጋሽ መሐመድ

ሂሩት መለሰ

►◄