1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኮትዲቯር ዉዝግብና ሽምግልናዉ

ረቡዕ፣ ታኅሣሥ 27 2003

ታሕሳ አልፎ-ጥርም አምስት አለ።የመጀመሪያዉ ድርድር ከሽፎ-ሁለተኛዉም ተደገመ። እና እስከ መቼ-ይዛታል?ፕሬዝዳት ጆናታን ራሳቸዉም ድርድሩ ጊዜ ይወስዳል ከማለት ባለፍ መልስ የላቸዉም።

https://p.dw.com/p/QnpQ
ባግቦምስል picture alliance / dpa

05 01 11

የአፍሪቃ ሕብረትና የምዕራብ አፍሪቃ የምጣኔ ሐብት ማሕበረሰ(ECOWAS) መልዕክተኞች በምርጫ የተሸነፉት የኮትዲቯሩ ፕሬዝዳት ሎራ ባግቦ ሥልጣን እንዲለቁ ለማግባባት ያደረጉት ያለ ተጨባጭ ዉጤት አብቅቷል።ይሁንና የኮትዲቯርን ተቀናቃኝ ሐይላት መሪዎች ያነጋገሩት የሁለቱ ተቋማት መልዕክተኞች ባግቦን በሠላም ሥልጣን ለማስለቀቅ አሁንም ተስፋ አለ ባዮች ናቸዉ። መልዕክተኞቹ የሚወክሉት ማሕበረሰብ ባንፃሩ ባግቦን በሐይል ከሥልጣን ለማስወገድ ከዚሕ ቀደም ያሳለፈዉ ዉሳኔ አሁንም እንዳልታጠፈ እያስጠነቀቀ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ የዜና መልዕክቶችን አሰባስቧል።


ሰዉዬዉ የጠንካራዉ ጦር፥ የደፋሮቹ ወጣቶች፥ ምናልባትም ጠንካራ ድጋፍ ያልተለያቸዉ ጠንካራ ናቸዉ።ሎራ ኮዉዶዉ ባግቦ።በምርጫ መሸነፋቸዉ እንደታወጀ ሥልጣን አለቅም ሲሉ አዉሮጳ፥ አሜሪካ፥ አፍሪቃም የመዘዋወርና የገንዘብ ማዕቀብ ሲጥሉባቸዉ ሐይላቸዉ ተፍረክርኮ በትረ-መንግሥቱን ለማስረከብ ይገደዳሉ ነበር ስሌቱ።

Elfenbeinküste / Ouattara / Odinga
ዋታራና ኦዲንጋምስል AP

እስካሁን አልያዘም።ለዓለም ቸኮሌት አርባ ከመቶዉ ኮኮኦ የሚለቀምባት ሐገር አስር አመት ለመሯት ሰዉዬ ለደጋፊዎቻቸዉ የሚሰጡትን ገንዘብ አልነፈገቻቸዉም።የማዕቀቡ ሥልት መሳቱ እንደታየ ራስዋ ኮትዲቯርን ጨምሮ አስራ-ሰባት የምዕራብ አፍሪቃ ሐገራትን የሚያስተናብረዉ ማሕበረሰብ ECOWAS ባግቦን በሐይል ለማስወገድ መዛቱ እንደ ጥሩ ማስፈራሪያ ታይቶ ነበር።

ሰዉዬዉ ፈርተዉ ይሆን-ይሆናል። ግን አስር አመት እንደ ባልጀራ የሚያዉቋቸዉን አቻዎቻቸዉን ዛቻ-ምንነት ገቢር የሚያደርጉበትን አቅም-ብልሐት ከሚዝቱት እኩል ሥለሚያቁት ፍንክች አላሉም።የኤኮዋሱ ፕሬዝዳት ጄምስ ቪክቶር ቤሆ ትናንትም ዛቱ
«ተከታዩን በማያሻማ ሁኔታ ልናገር፥-ወታደራዊዉ አማራጭ ካርዱቹ ላይ ነዉ።ኤኮዋስ ባለፈዉ ታሕሳስ ባወጣቸዉ መግለጫዎቹ ካረጋገጠዉ ከዚሕ አቋሙ ፈቅ አላለም።»

የወቅቱ ሊቀመንበርና የናይጄሪያዉ ፕሬዝዳት ጉድላክ ጆናታንም ተመሳሳይዩን ነዉ-ያሉት።
«በመግለጫችን ያስታወቅነዉ የኤኮዋስ አቋም አሁንም እንደፀና ነዉ።»

ታሕሳ አልፎ-ጥርም አምስት አለ።የመጀመሪያዉ ድርድር ከሽፎ-ሁለተኛዉም ተደገመ። እና እስከ መቼ-ይዛታል?ፕሬዝዳት ጆናታን ራሳቸዉም ድርድሩ ጊዜ ይወስዳል ከማለት ባለፍ መልስ የላቸዉም።
«ጊዜ ይወስዳል።አናዉቅም።በዚያች ሐገር ሰወስት አመት ያስቆጠረዉን የርስ በርስ ጦርነት ለማስቆም አለም የፈጀበትን ጊዜ እናዉቃለን።»

በገቢር ግን ኤኮዋስ-ብዙዎች እንደሚሉት፥- ያለ አቅም-ዝግጅት በመዛቱ፥ይሁን በባግቦ ብልጠት ከዛቻዉ ተንፏቆ-የአፍሪቃ ሕብረትን ድጋፍ መጠየቅ እናም ድሩድሩን «እንዳሞሌ-ዛቻዉን እንደ እንዳርጩሜ» መጠቀም ግድ ሆኖበታል።እንደገና የኤኮዋሱ ፕሬዝዳት።

«ኤኮዋስና የአፍሪቃ ሕብረት የሚነግሯችሁ ችግሩን በሰላም ለማስወገድ ያለዉ እድል ግማሽ ከመቶ ብቻ ቢሆን እንኳን ያንን ለመጠቀም መስማማታቸዉን ነዉ።ከሁለቱ፥-ከፕሬዝዳት ባግቦና ከፕሬዝዳንት ዋታራ ጋር በተደረገዉ በመጀመሪያዉ ግንኙነትም የሐይሉን አማራጭ ለማስወገድ የሚረዱ የመግባባት ፍንጮች ታይተዋል።»

የአፍሪቃ ሕብረቱ መልዕክተኛ የኬንያዉ ጠቅላይ ሚንስትር ራይላ ኦዲንጋ ደግሞ የድርድሩ ተስፋ ከግማሽ በመቶም ብዙ የላቀ ነዉ-ባይ ናቸዉ።
«ከሚስተር ዋታራ ጋር ይደራደሩ እንደሆነ ጠየቅናቸዉ።ከቅድመ ሁኔታ ጋር ድርድሩን ተቀበሉት። ዋታራንና ቡድናቸዉንም ጠቅይቀናቸዉ ሁለት ነገሮች ከተሟሉ እንደሚደራደሩ ነገሩን።»

Elfenbeinküste / Odinga / Yayi / Koroma / Pires / Gbagbo
መልዕክተኞቹምስል AP

ዋታራ አስቀመጧቸዉ የተባሉት ሁለቱ ቅድመ ሁኔታዎች ዋታራ በምርጫዉ ማሸነፋቸዉ ባግቦ እንዲቀበሉና የዋታራን ጠቅላይ ፅሕፈት ቤት የከበበዉን ጦር እንዲያነሱ የሚሉ ናቸዉ።ኦዲንጋ እንዳሉት ባግቦ ሁለቱንም ቅድመ ሁኔታዎች ተቀብለዋቸዋል።

እናም በኦዲንጋ እምነት የድድሩ መፍትሔ ሩቅ አይደለም።የዋታራ ግን ድርድሩ አለቀ-ነዉ ያሉት በቃ።
«በኛ በኩል ዉይይቱ አብቅቷል።ለርዕሳነ ብሔራቱ (ለኢኮዋስ መልዕክተኞች) ብዙ የሚሰሩት እንዳለ ጠቁመናቸዋል።ላደረጉት ጥረት ሁሉ በጣም እናመሰግናቸዋለን።»

ዉዝግብ-ፍጥጫዉ ግን እንደቀጠለ ነዉ።

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ