1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባት አረፈች

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 20 2005

ህንድ ዋና ከተማ ኒዉዴሊ ዉስጥ ከአስራ ሁለት ቀናት በፊት በበርካታ ወንዶች አደገኛ የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባት ወጣት ከዚህ አለም መለየትዋ ተገለፀ። የወሲብ ጥቃት የተፈፀመባት የ 23 ዓመት ወጣት ህልፈትን ተከትሎ በህንድ ከፍተኛ ቁጣና ሃዘን መቀስቀሱም እየተነገረ ነዉ።

https://p.dw.com/p/17B6l
ኒውዴልሂ፥ በወጣቷ ሞት ህዝቡ ቁጣውን ሲገልፅ
ኒውዴልሂ፥ በወጣቷ ሞት ህዝቡ ቁጣውን ሲገልፅምስል Reuters

ህንድ ዋና ከተማ ኒዉዴሊ ዉስጥ ከአስራ ሁለት ቀናት በፊት በበርካታ ወንዶች አደገኛ የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባት ወጣት ከዚህ አለም በሞት መለየትዋ ተገለፀ። የወሲብ ጥቃት የተፈፀመባት የ 23 ዓመት ወጣት ህልፈትን ተከትሎ በህንድ ከፍተኛ ቁጣና ሃዘን መቀስቀሱም እየተነገረ ነዉ። በአደባባይ ለተቃዉሞ የወጡ ሰልፈኞች ሟች ፍትህ እንድታገኝ እና በአገሪቷ የሚታየዉ ከፍተኛ የወሲብ ጥቃት እንዲቆም እንዲሁም ለሴቶች የበለጠ መብት እንዲሰጥ በርካታ ሴቶች በአደባባይ  መጠየቃቸዉም ተመልክቶአል። በዋና ከተማዋ ኒዉዴሊ የተቃዉሞ ሰልፉን ተከትሎ ከፍተኛ የፀጥታ ሃይላት በየመንገዱ የተሰማሩ ሲሆን፤ የከርሰ ምድር የህዝብ ማመላለሻ ባቡሮች መዘጋታቸዉ ታዉቋል። ከአንድ ሳምንት በፊት የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባትን ወጣት በማስመልከት በተነሳዉ ከፍተኛ ተቃዉሞ ሰልፍ ከ 100 ሰዎች በላይ መጎዳታቸዉና  አንድ ጸጥታ አስከባሪ ፖሊስ ህይወት ማለፉ ይታወሳል።  የ 23 ዓመትዋ ህንዳዊት ወጣት ከ ሁለት ሳምንት በፊት በኒዉዴሊ መዲና በአንድ አዉቶቡስ ዉስጥ ተሳፍራ ሳለ በስድስት ወንዶች በብረት ዱላ ተደብድባና ተደፍራ ከአዉቶቡሱ መወርወርዋ ይታወሳል። ዘግናኝ የወሲብ ጥቃት የተፈፀመባት ወጣት የዉስጥ አካላት ክፍሎችዋ ክፉኛ በመጎዳታቸዉ የህክምና ባለሞያዎች ለማዳን ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ መቅረቱም ተያይዞ ተገልጾአል።    

አዜብ ታደሰ

ማንተጋፍቶት ስለሺ