1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ትምህርት

የወጣት ትውልድ አስተዋፅዎውና ተግዳሮቶቹ

ሐሙስ፣ ኅዳር 21 2010

ከሰሀራ በስተ ደቡብ ባሉ ሀገራት ከሚገኘው ህዝብ መካከል 77 ከመቶው እድሜው ከ 35 ዓመት በታች ነው። ለአንድ ሀገር የኢኮኖሚ እድገት መጨመር ወጣቱ ትውልድ ትልቅ ሚና ይጫወታል። የኢትዮጵያ ወጣት ለትውልዱ የሚያበረክተው አስተዋፅዎ እና የሚገጥሙት ተግዳሮቶች ምንድን ናቸው?

https://p.dw.com/p/2oVZy
Angola Jugendliche & Kinder in Luanda, Boa Vista Slum
ምስል Getty Images/AFP/S. de Sakutin

ወጣቱ ትውልድ

ኢትዮጵያ እንደ ጀርመን ካሉ ሀገራት ጋር ስትነፃፀር ብዙ ወጣት ትውልድ ያላት ሀገር ናት። በኢትዮጵያ ማእከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ መረጃ ከመሰረት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሶስት ዓመት በፊት እድሜው ከ 30 ዓመት በታች የሆነው የማህበረሰብ ቁጥር 71 ከመቶው ነበር። እነዚህ ወጣቶች ለሀገሪቱ ቀጣይ እድገት ጠንካራ መሰረት በመሆናቸው፣ ለወጣቱ አስፈላጊ በሆኑ ነገሮች ላይ  አስቀድሞ መስራት የግድ ነው።  ዋና ከሚባሉት መካከል የጤናው እና የትምህርት ዘርፎች፣ እንዲሁም፣ ለወጣቱ አስተማማኝ የሆነ የስራ እድል መፍጠርም  ይጠቀሳሉ።

የ27 ዓመቱ ወጣት በድሩ ከማል ኢትዮጵያ ውስጥ በህግ ትምህርት ተመርቋል። የተማረውን ግን እስካሁን በተግባር ላይ ማዋል አልቻለም። ያለፉትን አራት ወራት ስራ በማፈላለግ ላይ ይገኛል።

Junge Menschen in Äthiopien
ምስል picture-alliance/ dpa

ኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስተምራ የምታስመርቃቸው ወጣቶች ቁጥር ቢጨምርም የስራ ቦታው ከተመራቂው ቁጥር ጋር ሊመጣጠን አልቻለም። በኢትዮጵያ ስላለው የስራ አጥነት ደረጃ ላይ ከአምስት ዓመት በፊት የተካሄደ አንድ ጥናት እንደሚያመለክተው፣  ሰባት ከመቶ የሚሆነው ወጣት ስራ የለውም። እድሜያቸው በ15 እና በ 29 ዓመት መካከል የሚገኙ 25 ከመቶ ያህሉ ወጣቶች ደግሞ ከሚገባቸው ባነሰ የስራ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ለዚህም በምሳሌነት ሊጠቀስ የሚችለው ከአመታት በፊት ብዙ ክርክር ያስነሳው በኮብል ስቶን ስራ ላይ የተሰማሩ ምሩቃን ጉዳይ ነው።  የህግ ምሩቁ በድሩ በኢትዮጵያ ያለው ወጣት በአግባቡና በተገቢው መንገድ በመብቱ  እንዲጠቀም ከተደረገ ወጣቱ ለትውልድ ሊያበረክት የሚችለው አያሌ ተግባራት ይኖራሉ።

እንደ ኢትዮጵያ ባለች ሀገር የወጣት ተፎካካሪው ቁጥር ከፍ ማለቱ እና በዚህም ምክንያት ስራ የማግኘት እድሉ ቢጣበብም በሀገር ደረጃ ሲታይ ወጣት የሰው ኃይል የሀገሪቷ ሀብት ነው። በአንፃሩ፣ ጀርመን ከበለፀጉት ሀገሮች ተርታ ብትሰለፍም በእድሜ የገፋ ማህበረሰብ መብዛት ፈተና ሆኖባታል። ከ 82 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ባላት ጀርመን ውስጥ እድሜያቸው ከ40 በላይ የሆኑት 60 ከመቶ ይጠጋሉ።  አማካዩ እድሜ 44,3 ዓመት ነው። ምንም እንኳን የስራ አጡ ቁጥር ጀርመን ውስጥ እጅጉን ቢቀንስ እና 3,7 ከመቶ ላይ ቢገኝም የጀርመን ወጣት እና ጎልማሳው ህብረተሰብ የወደፊቱ ህይወቱ ያሳስበዋል።   ምክንያቱም ወጣቱ ትውልድ እንደ አያቶቹ እና ወላጆቹ ከመንግሥት በሚያገኘው የጡረታ ገንዘብ ራሱን ማስተዳደር አዳጋች ሆኖበታል። በአሁኑ ወቅት አንድ አራተኛው የጀርመን ማህበረሰብ በጡረታ ላይ ይገኛል። ጡረተኞቹ የሚያገኙትን የጡረታ ገንዘብ የሚገኘው ደግሞ ዛሬ በስራ ላይ ከሚገኘው ትውልድ ነው። ጀርመን ውስጥ በአማካይ አንድ እናት 1,47 ልጆች ትወልዳለች። የልጆች ቁጥር በቶሎ የማያድግበት እና የሰራተኛው ኃይል ቁጥር ከፍ የማይልበት ሁኔታ በጡረታ  አከፋፈል ላይ ተፅዕኖ ስለሚያሳርፍ፣  የመድህን ዋስትና ድርጅቶች ወጣቱ ከወዲሁ ለጡረታው የሚሆነውን ገንዘብ ራሱ እንዲያጠራቅም ይመክራሉ። ይህ ኢትዮጵያን  አያሰጋትም። ኢትዮጵያ የህዝብ ብዛታቸው በፍጥነት በማደግ ላይ ካሉ 10 ሀገራት ተርታ ነው የምትሰለፈው።

Deutschland Bevölkerung Generationen Partnerschaft und ältere Menschen
ከ 82 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ባላት ጀርመን ውስጥ እድሜያቸው ከ40 በላይ የሆኑት 60 ከመቶ ይጠጋሉምስል picture-alliance/dpa

አብረሃም ተስፋዬ «ወጣቱ የለውጥ ኃይል ነው ካለበለዚያ ግን እንደ ተጠመደ ፈንጅ ነው ይላል»። በ30ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ላይ የሚገኘው አብረኃም ወታደር ነበር። አሁን ግን በግል ስራ ይተዳደራል። ኢትዮጵያ ውስጥ በወጣቱ አካባቢ የሚታየውን ስራ አጥነት ችግር ለመቅረፍ በርካታ እየተሰሩ ያሉ ነገሮች ቢኖሩም አፈፃጸሙ ላይ ችግር እንዳለ ይናገራል።

ከሰሀራ በስተ ደቡብ ባሉ ሀገራት ከሚገኘው ህዝብ መካከል 77 ከመቶው እድሜው ከ 35 ዓመት በታች ነው። ይሁንና የወጣቱ ተሰሚነት አናሳ ነው። እስከ ቅርብ ጊዜ የዚምባዌው መሪ የነበሩት ሮበርት ሙጋቤ ስልጣን ሲለቁ 93 ዓመታቸው ነበር። የበርካታ አፍሪቃ ሀገራት መሪዎች ስልጣን በፍቃደኝነታቸው አለቀቁም ወይም አይለቁም። ስለሆነም ወጣቱ በፖለቲካው ዓለም እምብዛም  ተካፋይ ሊሆን አልቻለም። ይህ ኢትዮጵያም ውስጥ ብዙ የተለየ አይደለም ይላሉ አንድ በሳውዲ አረቢያ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊ ።

Bildergalerie langjährige Herrscher Robert Mugabe
እስከ ቅርብ ጊዜ የዚምባዌው መሪ የነበሩት ሮበርት ሙጋቤ ስልጣን ሲለቁ 93 ዓመታቸው ነበርምስል Getty Images/AFP/J. Njikizana

በአሁኑ ሰዓት በሱዳን ሀገር እንደሚኖሩ የገለፁልን እና ለዚህ ዘገባ መሰረት ብላችሁ ጥሩኝ ያሉንም ወይዘሮ ያለው የኢትዮጵያ መንግሥት ለወጣቱ እድል ይሰጣል ብለው አያምኑም።መሠረት በደርግ ስርዓት ከስራ እንደተሰናበቱ እና ኢትዮጵያም ውስጥ ስራ ማግኘት ስላልቻሉ ሀገር ጥለው እንደተሰደዱ ይናገራሉ። ወይዘሮዋ ለአፍሪቃውያን ወጣቶች ስራ አጥነት ተጠያቂ የሚያደርጉት የአፍሪቃን መሪዎች ነው።

በሀዲያ ዞን የኮሌጅ ተማሪ የሆነው የ 19 ዓመቱ ወጣት   ኢሲያት ጌታቸው በአንፃሩ ጥፋቱን መንግሥት ላይ ሳይሆን ወጣቱ ላይ ነው የሚያየው። እንደሱ ከሆነ ወጣቱ በርትቶ እየሰራ አይደለም። በርካታ ኢትዮጵያውያን ስራ ፍለጋ ከተሰደሱባቸው የአረብ ሀገራት አንዷ ሳውዲ አረቢያ ናት። ሀገሩ ውስጥ ስራ በማጣቱ የተሰደደው አብዱ ሀመድ በለጠም ቢሆን ችግሩን የሚያየው ወጣቱ ላይ ነው። እሱ እንደሚለው ወጣቱ የጥፋት ኃይል ሆኗል።

ልደት አበበ

አርያም ተክሌ