1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ምስቅልቅል

ሰኞ፣ መጋቢት 9 2011

ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ፖለቲካዊ-ምጣኔ ሐብታዊ-ጎሳዊ-ማሕበራዊ-ፍትሐዊ ቀዉስ ግን ሐገሪቱን አቅጣጫ ጠቋሚ እንዴላት መርከብ ከማዕበል ወጀቦ፣ ከከበረዶ ቋጥኝ ክምር እንዳያላጋት፣የዐቢይ መንግሥትም እንደቀዳሚዎቹ ሁለቱ ጅምር ምግባሩን እንደዘከረ እድሜ እንዳይቆጥር ነዉ የብዙዎች ሥጋት።

https://p.dw.com/p/3FGXy
Abiy Ahmed Äthiopien
ምስል Reuters/T. Negeri

የኢትዮጵያ ምስቅልቅል


«ወጣቱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር» ይላል፣ ዘ-ኢኮኖሚስት የተባለዉ የብሪታንያ እዉቅ መፅሔት፣ ዶር ዐቢይ አሕመድን ማለቱ ነዉ። «ኢትዮጵያን ዴሞክራሲያዊ አደርጋለሁ ሲሉ ከልባቸዉ ነዉ።»የእስካሁኑ ጉዞ ግን ቀጠለ የመፅሔቱ አጭር መጣጥፍ «በአስፈሪ የጎሳ ግጭት የታጀበ ነዉ።» ለምን? እንዴት? እና ከእንግዴሕስ?
የደርግ መንግስት ባለሥልጣናት ለሶሻሊስታዊ ጥሩ እርምጃቸዉ አብነት የሚጠቅሷቸዉ ሶስት ነገሮች ነበሩ።መሬት ላራሹ፣ የከተማ ቦታና ትርፍ ቤቶችን፣ትላልቅ ኢንዱስትሪና የገንዘብ ተቋማትን መዉረስ ወይም በያኔዉ ቋንቋ የሕዝብ ማድረግ።
የሶስቱን «ድል» ጧት ማታ እንደተናገሩ አስራ-ሰባት ዐመት ገዙ።ኢሐዴጎችም መጀመሪያ ላይ አንድ፣ ኋላ ሶስት እርምጃዎቻቸዉን የጥሩ ሥራቸዉ አብነት ያደርጉ ነበር።የደርግን ሥርዓት ማስወገዳቸዉን-አንድ፣ የብሔር ብሔረሰብ እኩልነት ማስረፃቸዉን-ሁለት፣ የምጣኔ ሐብት እድገት የሚሉት-ሶስት።
ሁለቱም ስርዓቶች የየጠቃሚ እርምጃቸዉ ምሳሌ የሚያደርጓቸዉን ጉዳዮች በርግጥ ሠሩም አልሰሩ፣ የሠሩት ሕዝብን ጠቀመም ጎዳ ለኢትዮጵያ ህዝብ ከሠሩለት ይልቅ የጎዱት በመብለጡ በሕዝብ ግፊት የየዘመኑ ሥርዓታቸዉ ፈርሷል።
ዘኤኮኖሚስት እንደዘገበዉ ኢትዮጵያ አንድም ከሁለቱ ሥርዓቶች በፊት ንጉሳዊ፣ሁለትም አምባገነናዊ አገዛዞች ወይም ደም አፋሳሽ አብዮት እንጂ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አታዉቅም።እዉነተኛ ዴሞክራሲያዊና ነፃ  ሥርዓት ለማስፈን አንድ ሁለት ማለት የጀመረዉ የጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ መንግስት የፖለቲካ እስረኞችን ከመልቀቅ-የመገናኛ ዘዴዎችን ነፃነት እስከ መፍቀድ፣ ስደተኛ ተቃዋሚዎችን ከመጋበዝ-ከኤርትራ ጋር ሠላም እስከ ማዉረድ የሚደርሱ የሕዝብ ድጋፍ ያገኙ እርምጃዎችን ወስዷል።

Äthiopien Vertriebene
ምስል Tizalegn Tesfaye

ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ፖለቲካዊ-ምጣኔ ሐብታዊ-ጎሳዊ-ማሕበራዊ-ፍትሐዊ ቀዉስ ግን ሐገሪቱን አቅጣጫ ጠቋሚ እንዴላት መርከብ ከማዕበል ወጀቦ፣ ከከበረዶ ቋጥኝ ክምር እንዳያላጋት፣የዐብይ መንግስትም እንደቀዳሚዎቹ ሁለቱ ጅምር ምግባሩን እንደዘከረ እድሜ እንዳይቆጥር ነዉ የብዙዎች ሥጋት።
ታሕሳስ ማብቂያ በተሰናበተዉ በጎርጎሪያኑ 2018 ብዙ ሕዝብ ከቤት ንብረቱ የተፈናቀለዉ በጦርነት በሚወድሙት ሶሪያ፤የመን፣ደቡብ ሱዳን አይደለም።ኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ አይደለም።አሸባሪ የሚባሉት አል-ሸባብ፣ ቦኮ ሐራም ወይም ታሊባን በሸመቁባቸዉ ሶማሊያ፣ናይጄሪያ ወይም አፍቃኒስታን አይደለም-Internal Displacement Monitoring Centre  (IDMC) እንደዘገበዉ አጓጊ ለዉጥ በተጀመረባት፣ የዚያኑ ያሕል የጎሳ ግጭት ባየለባት ኢትዮጵያ እንጂ።
ዓለም አቀፉ የተፈናቃዮች ጉዳይ አጥኚ ተቋም ባለፈዉ መስከረም እንደዘገበዉ፣ በ2018 የመጀመሪያ ስድስት ወር ብቻ ከ1.4 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ተፈናቅሏል።
ዩሮ ኒዊስ ባለፈዉ ጥር እንደዘገበዉ ደግሞ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከ3 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ተፈናቅሏል።የጎሳ ግጭት፣ግድያ፣መፈናቀል አሁንም እንደቀጠለ ነዉ።«አስጊ ሰብአዊ ቀዉስ» ይሉታል የስብስብ ለሰብአዊ መብት በኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ ያሬድ ኃይለማርያም።
                                        
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የመግባባት፣የአንድነትና የሠላም ማሕበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ብርሐኑ ፋንታሁን እንደሚሉት ደግሞ ከለዉጡ ማግሥት ጀምሮ ኢትዮጵያ ዉስጥ የተከሰተዉ የጎሳ ግጭትና ግድያ ዘግናኝ መልክና ባሕሪም አለዉ።
                                  
ከጎንደር እስከ ጋምቤላ፣ ከኦጋዴን እስከ በኒ ሻንጉል፤ ከሞያሌ እስከ ራያ፣ ከቡራዬ-እስከ ጌድኦ የተፈፀሙ ግፍ በደሎችን ለማጣራት እንኳን እስካሁን አልተቻለም።ምክንያቱ እንደከዚሕ ቀደሙ ማዕከላዊዉ መንግስት ሥለከለከለ አይደለም።ገለልተኛ አጣሪዎች ጥቃት ይደርስብናል በሚል ፍርሐት ወደየአካባቢዎቹ መጓዝ ባለመቻላቸዉ ነዉ።የአስጊዉ ጠብ፣ግጭት ግድያ ሰበብ ምክንያት ብዙዎች እንደሚሉት ብዙ ነዉ። አቶ ያሬድ ሶስቱን ይጠቅሳሉ።
                                      
ኢትዮጵያ ዉስጥ እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ከ2015 ጀምሮ 8 ሚሊዮን ሕዝብ የዕለት ጉርስ የሚያገኘዉ ከዉጪ በሚለመን ምፅዋት ነዉ።በዚሕ ቁጥር ላይ 3 ሚሊዮን ተፈናቆዮች ተጨምርዉበታል።ድምር 11 ሚሊዮን።በየስፍራዉ በተደረጉ ግጭቶች የሞተ የቆሰለዉን እስካሁን በትክክል የቆጠረዉ የለም።
አስጊ፣ዘግናኝ ምናልባትም ሐገር አጥፊዉ ጠብ፣ግጭት፣ግድያ አዲስ አበባ የታጨቁ ልሒቃንን ልብ የነካ  አይመስልም።እንዲያዉም የኢትዮጵያ ልሒቃን የተቃዋሚ ፖለቲከኛ ይሁኑ-የመንግሥት፣ ምሁር ይባሉ፣ ተንታኝ ወይም ሌላ አንዳቸዉ ከሌላቸዉ እየተናቆሩ፣፣ አስፈሪዉን ግጭት እያጋጋሙት ነዉ።አምና  የፈነጠቀዉ የዴሞክራሲ፣የነፃነት፤ የፍትሕ፤ የልማት፣እድገት ተስፋ ባይጠፋ መንምኗል።አቶ ፋንታሁን እንደሚሉትማ በጎ-ተስፋ የፈነጠቀዉ ለዉጥ ራሱ«ተቀልብሷል።»
ኢትዮጵያ ዛሬ ጋዜጠኛዉን ከፖለቲከኛዉ፣ የመብት ተሟጋቹን ከጎሰኛዉ፣ የፖለቲካ አቀንቃኙን፣ ከሕግ ሙያተኛዉ ሌላዉ ቀርቶ ኃይማኖት ሰባኪዉን ከጦረኛዉ መለየት የማይቻልባት ሐገር ሆናለች።ምስቅልቅል ሐገር።የግራ-አጋቢዎች ግራ አጋቢ ምድር።
                             
ጠብ ግጭት ግድያዉን ማስቆም፣ ሕግና ሥርዓትን ማከበር ይሁን ሙያዊ-ሥነ-ምግባር፣ ሐላፊነት ወይም ተጠያቂነቱን ጥሶ ባሻዉ «የሚዘባርቀዉን» ግለሰብ ወይም ቡድንን አደብ ማስገዛት ያለበት መግስት ነዉ።መግሥት፣ ያዉም ከራሱ ሕዝብም ከዉጪም ድጋፍ ማበረታቻዉ ሞልቶ የተረፈዉ የኢትዮጵያ መንግስት አደገኛዉን ግጭት፤ሥርዓተ አልበኝነቱን ሆነ መንግስታዊ ያልሆኑ ልሒቃንን እርምጃ «ኃይ» ማለት ያልቻለበት ምክንያት በርግጥ ያጠያይቃል።

Äthiopien Vertriebene
ምስል Tizalegn Tesfaye

አንዳዶች የጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ መንግሥት ማድረግ ያለበትን እንዳያደርግ በቅርብ ደጋፊዎቹ «ታግቷል» ወይም ተቀይዷል ይላሉ።አቅም የለዉም ባዮችም ብዙ ናቸዉ።አቶ ፋንታሁን መንግስትንም፣ ተቃዋሚ ፖለቲከኞችንም ተጠያቂ ያደርጋሉ።ይጠይቃሉም።«ሐገር አለ» እያሉ።
                                   
አቶ ያሬድ ግን ሁሉንም አይቀበሉትም።መንግስት እስካሁን ትዕግሥት አብዝቷል ወይም ዳተኛ ሆኗል ባይ ናቸዉ።ትዕግስቱ ግን ሊያልቅ-ይገባል።አብዛኛዉ ኢትዮጵያዊ «ሟርት» እያለ የሚሸሸዉን ግን ሁሌም አብሮት የሚኖረዉን እዉነት ጠየቅን?-ኢትዮጵያ ትበታተን ይሆን? ጥያቄ፣ አንድ።
አቶ ፋንታዉን ብርሐኑ ናቸዉ።ሁለት-አቶ ያሬድ።

Äthiopien Diskussion Medien und Demokratie in Addis Abeba
ምስል DW/Y. Gebregziabher

ተስፈኛ ናቸዉ።ዶክተር ዐብይ «እዉነተኛ ዴሞክራሲን ገቢር ካደረጉ» ይላል መገቢያችን ላይ የጠቀስነዉ ዘ ኤኮኖሚስት መፅሔት «የቀጠናዉን ፖለቲካዊ ልምድ መገለባበጥ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን የእስካሁን ይትበሐልም ጨርሶ ይለዉጡታል።»

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ