1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም ሎሬት ጥበበ የማነ ብርሃን (ዶ/ር ) ማን ናቸዉ? 

ሐሙስ፣ የካቲት 18 2013

ከምን እንዳገኘዉ አላዉቅም፤ ጥምቀትን በጣም ያከብራል። በጥምቀት ብዙ ሰዉ እየጠራ እቤቱ ድግስ ያደርጋል። እኔ ግን አልሄድኩም በቤቱ በኩል ሳልፍ ግን፤ ቤቱ ጋር የታቦት ማሳረፍያዉ ቦታ ሁሉ ተዘጋጅቶ ነበር እና ደዉዬ፤ ምን ማድረግነህ ነዉ ስለዉ እባክህ አስር ሰዉ ቢሆን ነዉ አለኝ። ገባ ብለህ እንጫወት ምናምን አለኝ። እኔን የሚፀጽተኝ ...»

https://p.dw.com/p/3pozZ
Äthiopien Addis Abeba | Bestattung Tibebe Yemanebirhan
ምስል privat

በሕይወቱ ህፀፅ የሌለበት ሰው ሞቱን የሚቀበለው በልበ ሙሉነት፤ በክብር ነው

«ከምን እንዳገኘዉ አላዉቅም፤ ጥምቀትን በጣም በጣም ያከብራል። በጥምቀት ብዙ ሰዉ እየጠራ እቤቱ ድግስ ያደርጋል። የእዛን እለት በቤቱ በኩል የጥምቀት እድምተኞች፤ ያልፋሉ። እኔ ግን አልሄድኩም በቤቱ በኩል ሳልፍ ግን፤ የታቦት ማሳረፍያዉ ቦታ ተዘጋጅቶ ነበር እና ደዉዬለት፤ ምን ማድረግነህ ነዉ ስለዉ እባክህ አስር ሰዉ ነዉ ፤ ዝም ብለህ ገባ ብለህ እንጫወት ምናምን አለኝ። አልገባም አንተም ተጠንቀቅ ብዬዉ አልፍያለሁ። እንደዉ የሚፀጽተኝ ያን እለት ነዉ የያዘዉ ብዬ ነዉ የማስበዉ።»  
አቶ ታደለ ይድነቃቸዉ ተሰማ እሸቴ ከተናገሩት የተሰደ ነዉ። ከጥቂት በፊት ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት የዓለም ሎሬት የዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን የቅርብ ወዳጅ ናቸዉ። ጤናይስጥልኝ አድማጮች እንደምን አመሻችሁ። ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን ማን ናቸዉ? በዓለም አቀፍ ደረጃ በሥነ ቆዳ ሕክምና (ዴርማቶሎጂ) ታዋቂ ፣ በኅብረተሰብ ጤና አጠባበቅ ባለሙያም ሆነው ኢትዮጵያን ለሃምሳ ዓመታት አገልግለዋል።  የዓለም ሎሬት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን በቀድሞዉ የሶቭየት ሕብረት ትምአጠናቀዉ አጠናቀዉ ወደ ሃገራቸዉ የተመለሱት በደርዝ ዘመነ መንግሥት ነዉ። ወደ ኢትዮጵያ እንደተመለሱ አዲስ አበባ በሚገኘዉ የሥልጠና ማዕከል እና የመላዉ አፍሪቃ የሥጋ ደዌ መልሶ ማቋቋም ማዕከል «አለርት» ሆስፒታል  ተቀጥረዉ አገልግለዋል። ስርዓተ ቀብራቸዉ ማክሰኞ የካቲት 16 ፤ 2013 ዓ.ም በአዲስ አበባ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በተፈፀመ ወቅት በቀረበዉ የሕይወት ታሪካቸዉ የዓለም ሎሬት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን «የቆሰለን ገላ ብቻ ሳይሆን የታወከ አዕምሮን የሚያክም፣ የቀዘቀዘ መንፈስን የሚያሞቅ፣ የተሰበረን ልብ የሚጠግን፣ በሰላም ጎዳና ላይ የተነጠፈን አሜከላ-ሾህ የሚጠርግ ምሁር ዛሬም እንደ ትናንቱ፣ ነገም እንደ ዛሬው አገራችን ትሻለች» ተብሎላቸዋል። የረጅም ዓመታት ባልንጀራቸዉ አቶ ታደለ ይድነቃቸዉ ተሰማ እሸቴ በሰፊዉ ያስታዉሱዋቸዋል። በኮቪድ በሽታ መሞታቸዉ ነዉ የተነገረዉ ? ይህ በሽታ አሁን ዓለም ላይ አሳሳቢ ሆንዋል። 

Äthiopien Addis Abeba | Bestattung Tibebe Yemanebirhan
ምስል privat
Äthiopien Addis Abeba | Bestattung Tibebe Yemanebirhan
ምስል privat

ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን የዓለም ሎሬት ክብር ያገኙት በጎርጎረሳዉያኑ 2000 ዓመት መባቻ ላይ ነበር።  በጎርጎረሳዉያኑ 2014 ዓ.ም ደግሞ ሩስያ ሞስኮ በክሬምሊን መንግሥት ከሩስያዉ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ በሩስያ ተምረዉ ከፍተኛ ስኬትን ላመጡ ዜጎች በሚል የሩስያን ከፍተኛ ኒሻን  ተቀብለዋል። የዓለም ሎሬት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን በቅርቡ በተቋቋመዉ የሰላም ኮሚሽን ዉስጥም እያገለገሉ ነበር። አንጋፋዉ አርቲስት ደበበ እሸቱ ከዶ/ር ጥበበ የማነብርሃን ጋር አብሮ ሰርቶአል። 

Äthiopien Addis Abeba | Bestattung Tibebe Yemanebirhan
ምስል privat

የኢትዮጵያዉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ፤ በዓለም ሎሬት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን ድንገተኛ ከዚህ ዓለም በሞት መለየት የተሰማቸዉን ሃዘን ገልፀዋል። በሰላም ኮሚሽን ሲያገለግሉ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ይተዋወቁ ይሆን? አቶ ታደለ ይድነቃቸዉ ተሰማ እሸቴ አጫዉተዉናል።  
ዓለም አቀፍ እዉቅና የተላበሱት ኢትዮጵያዊዉ የተከበሩት የዓለም ሎሬት ጥበበ የማነብርሃን ከልጅነታቸዉ ጊዜ ጀምሮ ስማቸዉ ይነሳ የነበረዉ ከልግስና ከምግባረ ሰናይጉዳዮች ጋር እንደነበር ብዙዎች ይናገራሉ። ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን በ1941 ዓ.ም የካቲት 22 ቀን የተወለዱት ከአባታቸዉ ከሻለቃ የማነብርሃን ወልደስላሴ እና ከእናታቸዉ ከወይዘሮ የሸዋድንበር ጽጌ በሀረር ጠቅላይ ግዛት እንደሆን የህይወት ታሪካቸዉ ያሳያል። ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን ባለትዳር እና የሁለት ሴቶች ልጆች አባት የሁለት ልጆች አያት ነበሩ። የዓለም ሎሬት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን  የቀብር ስነስርዓት  ማክሰኞ የካቲት 16 ፤ 2013 ዓ.ም በአዲስ አበባ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ዘመድ፤ ወዳጅ ጓደኛ ብሎም የሃገሪቱ ከፍተኛ ባለስለጣናት በተገኙበት ተፈፅሞአል። በቀብር ስነስርዓቱ ላይ ህይወታሪካቸዉ ሲነበብ የመጨረሻዎቹ ምዕራፍ እንዲህ ይላሉ « የጠፋና የባከነ ጊዜ የሚባለዉ ካለፈዉ ሕይወት ደግ ነገር ያልቀሰሙበት እና ለትዉልድ ምንም በጎ ሥራ ያላስተላለፉበት ነዉ። ተስፋዉን በሕይወት ዘመኑ በእዉን ለማየት የቻለ ምሁር ሞቱን ጨርሶ አያስበዉም። በሕይወቱ ህፀጽ የሌለበት ሰዉ ሞቱን የሚቀበለዉ በልበ ሙሉነት በክብር ነዉ፤ ይላል።  

Äthiopien Addis Abeba | Bestattung Tibebe Yemanebirhan
ምስል privat

ሙሉዉን ቅንብር የድምጽ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን! 

አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ