1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም ስደተኞች መታሰቢያ ቀን፣

ዓርብ፣ ሰኔ 13 2006

ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በጦርነትና ቀዉስ ምክንያት ከቤት ንብረታቸዉ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 50 ሚሊዮን መድረሱን የተመ የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን UNHCR አስታወቀ።

https://p.dw.com/p/1CNF1
Zentralafrikanische Republik Trinkwasser in Bangui 07.01.2014
ምስል picture-alliance/AP Photo

ድርጅቱ ባለፈዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2013 ማለቂያ በግዳጅ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 51,2 ሚሊዮን መድረሱን ገልጿል። አብዛኞቹም የአፍጋኒስታን፣ ሶርያና ሶማሊያ ዜጎች ናቸዉ። የUNHCR የበላይ ኃላፊ አንቶኒዮ ጉቴሬሽ ዛሬ እንዳስታወቁት እነዚህ ተፈናቃዮችም ወይ ድንበር ተሻግረዉ ወደሌላ ሀገር ለመሰደድ ተገደዋል አለያም በሀገራቸዉ መኖሪያቸዉን ጥለዉ ሸሽተዋል። በእርስ በርስ ጦርነት ከተተራመሠችዉ ሶርያ ግጭት ከተጀመረበት ከጎርጎሪዮሳዊዉ 2011ዓ,ም ወዲህ 2,5 ሚሊዮን ህዝብ ተሰዷል፤ 6,5 ሚሊዮኖች ደግሞ በሀገር ዉስጥ ከመኖሪያ ቀያቸዉ ተፈናቅለዋል። የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፑብሊክና ደቡብ ሱዳን ቀዉስም እንዲሁ አዲስ የስደተኞች ጎርፍ አስከትሏል። አፍጋኒስታንና ሶማሊያ የቀጠለዉ አመፅም የስደተኛዉን ቁጥር ከፍ እንዲል የበኩሉን ማድረጉን UNHCR አመልክቷል። ጉተሬስ ዓለም ግጭቶችን ለመከላከልና በጊዜዉም መፍትሄ የመፈለግ አቅሙ ዉሱን መሆኑን አሳይቷል ብለዋል።

Flüchtlingsboot vor der australischen Küste
ምስል picture-alliance/dpa

የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽነር አንቶኒዮ ጉቴሬሽ በአሁኑ ጊዜ ከሁሉም አስከፊ የመከራ ገፈት በመቅመስ ላይ ያሉ ሶሪያውያን ስደተኞች ናቸው ሲሉም ተደምጠዋል።ከአፍሪቃ ፣ ማዕከላዊት አፍሪቃ ሪፓብሊክ፣ ደቡብ ሱዳንና ሶማልያ፣ ለህዝብ ከቀየው መፈናቀል በምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው። ከሰሐራ በስተደቡብ በሚገኙ የአፍሪቃ አገሮች በአጠቃላይ 2,9 ሚሊዮን ስደተኞች ይገኛሉ። ኢትዮጵያ ብዙ ዜጎቿ የሚሰደዱባት ሀገር ስትሆን ፣ በሌላ በኩል የሌሎች ጎረቤት ሃራትን ስደተኞች ተቀብላ የምታስተናግድ ሀገርም ናት። ስለዓለም የስደተኞች መታሰቢያ ቀን ፤ ጌታቸው ተድላ ኃ/ጊዮርጊስ የላከልን ዘገባ ቀጥሎ ይቀርባል።

ጌታቸው ተድላ ኃ/ጊዮርጊስ

ተክሌ የኋላ

ኂሩት መለሰ