1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም የምግብ ፕሮግራምና ኢትዮጵያ፧

ማክሰኞ፣ ግንቦት 5 2000

ለጋሽ መንግሥታት የሚፈለገውን ያህል ማቅረብ ባለመቻላቸው፧ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት፧ የዓለም የምግብ መርኀ-ግብር፧ ድርቅ በመታቸው የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚያበረክተውን እርዳታ ከግማሽ በላይ መቀነስ ግድ እንደሆነበት ተገለጠ።

https://p.dw.com/p/E0Wl
ድርቅ ባጠቃው የኢትዮጵያ ክፍል፧ አርብቶ-አደሮች ከግመሎቻቸው ጋር፧
ድርቅ ባጠቃው የኢትዮጵያ ክፍል፧ አርብቶ-አደሮች ከግመሎቻቸው ጋር፧ምስል dpa - Fotoreport
በዚህ ችግር ዙሪያ፧ በኢትዮጵያ የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑትን Vincent Lelie ን ያነጋገረው ተክሌ የኋላ፧ የሚከተለውን ዘገባ አጠናቅሯል።
«በደቡባዊው ኢትዮጵያ፧ ያለው ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ ነው የመጣው። የተመጣጠነ የምግብ እጦት በተለይ፧ በትንንሽ ልጆች ላይ ጎልቶ ይታያል።ምግብ፧ በአስተማማኝ ሁኔታ ማግኘት የሚያዳግትበት ምልክትም በግልጽ እየታዬ ነው። የዓለም የምግብ መርኀ-ግብርና ሌሎች ምግብ የሚያቀርቡላቸው ለጋሾች፧ ምላሽ አልሰጡምና በጣም አሳሳቢ ቀውስ ውስጥ ነው ሊገባ የሚቻለው።«
በአመዛኙ የተጎዱት አካባቢዎች የትኞቹ ናቸው?
«ብዙ፧ ብዙ ወረዳዎች በደቡባዊው ኢትዮጵያ፧ በኦሮሚያ በሚገኙ በዛ ባሉ ወረዳዎች፧...እነዚህ ሁለት አካባቢዎች ናቸው፧ በእጅጉ የተጠቁት።«
ዘንድሮ በ 2000 ዓ ም፧ (እ ጎ አ በ 2008 ዓ ም) በድርቅ ሳቢያ፧ 9 ሚልዮን ያህል ኢትዮጵያውያን ረሃብ እንደሚያሠጋቸው፧ ጥናት ያካሄዱ የውጭ ድርጅቶች በማስተንቀቅ’ ላይ ይገኛሉ። እጅግ አሳሳቢ አደጋ የተደቀነ በመሆኑ እናንተ ምን እያደረጋችሁ ነው?
«WFP ም ሆነ በአጠቃላይ የተ.መ. ድርጅቶች፧ ለሰብአዊ እርዳታ ተገቢውን ምላሽ ይሰጡ ዘንድ ለለጋሾች ተማጽኖ አቅርቧል። በተጨማሪም፧ በተጠና መልኩ፧ ቅድሚያ በሚሰጣቸው የእርዳታ ዓይነቶች ላይ እንዲያተኩሩ፧ በምግብ፧ በጤና እንዲሁም በተመጣጠነ ምግብ አቅርቦት ላይ እንዲያተኩሩ ይሻል። ምግብ ብቻ አይደለም፧ በዋናነት ሊተኮርበት የሚገባ ለልጆች የሚበጅ ተጨማሪ የምግብ ዓይነት ለህጻናትም የሚታዘዝ ምግብ ማቅረብ ይፈለጋል። ስለዚህ፧ ምግብ፧ ቅድሚያ የሚሰጠው አንገብጋቢ ጉዳይ ሲሆን ከዚህ ባልተናነሰ መልኩ ደግሞ የጤና ይዞታበምግብ እጥረት ሳቢያ በተጎዱ ሰዎች ላይ የከፋ ሁኔታ እያስከተለ በመምጣቱ፧ ይህም ዐቢይ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው። ለንፁህ የሚጠጣ ውሃና ለንፅህና አጠባባቅም እንዲሁ!ከዚህ ባሻገር አሁን የተከሠተው እንደገና እንዳያጋጥም፧ ለዘለቄታው የሚበጀውን ማስቀደም ተፈላጊ ነው።«
ዋና ተግባራችሁ፧ ለሚያስፈልጋቸው፧ አስቸኳይ ሰብአዊ እርዳታ ማቅረብ ነው። ኢትዮጵያ ትልቅ አገር ብትሆንም፧ እስካሁን በምግብ ረገድ ራሷን ያልቻለች ለረጅም ጊዜ ከተመጽዋችነት ያልተገላገለች መሆኗ የታወቀ ነው። የተ.መ.ድ ጽህፈት ቤቶች፧ አገሪቱ፧ በቂ እህል እንድታመርት የሚያግዙበት ሁኔታ አለ ወይ?
«ኢትዮጵያ፧ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ / ድርጅቶች እርዳታ፧ ምግብን አስተማማኝ ለማድረግ እጅግ ከፍ ያለ ጥረት ስታደርግ ቆይታለች። እንደእውኑ ከሆነ፧ ባለፉት ዐሠርተ-ዓመታት፧ ከሞላ ጎደል፧ 9 ሚልዮን ሰዎች የምግብ እርዳታ ያስፈልጋቸው ነበር። አሁን 3.4 ሚልዮን ወይም 3.2 ሚልዮን ገደማ ናቸው። ይህ፧ የእርዳታ ፈላጊው ቁጥር በሰፊው መቀነሱን ያመላክታል፧ ይሁንና ከ 10 እስከ 3 ሚሊዮን ወይም እስከመጨረሻው ዝቅተኛ አኀዝም ይጠቀስ፧ ላቅ ያለ ትርጉም የሚሰጠው፧ የምግብ አስተማማኝነት ተጠናክሮ፧ ኢትዮጵያ ውስጥ ድርቅም ሆነ የጎርፍ አደጋ ቢያጋጥም እንኳ፧ ለማንኛውም አካባቢ ህዝብ የምግብ እርዳታ የማያስፈልግበት ሁኔታ ተረጋግጦ ሲገኝ ነው። ይህም ሲሆን፧ በረጅሙ አቅድን ፈር ለማስያዝ አመቺ ሁኔታ ሊኖር ይችላል«።