የዓለም የገንዘብ ድርጅት ዕዳ እና ኬንያ
ረቡዕ፣ መጋቢት 22 1996ያለፈው ዓመት ታህሳስ ስልጣን የጨበጡት የኬንያው ፕሬዝዳንት ሙያዊ ኪባኪ ለህዝባቸው ከገቡዋቸው ቃል ኪዳኖች ውስጥ የተራባውን እና በቀን ከአንድ ዶላር በታች ገቢ የሚያገኘውን ህዝብ ህይወት ለማሻሻል የሚለው አንዱ ነበር ። ሥራቸው ለመመዘን ጊዜው አጭር ቢሆንም የሃገሪቱ የፖለቲካ ሂደት አቅጣጫ አያስተማምንም የሚሉት በርካታ ኬንያውያን ናቸው ። ኪባኪ ከዚህ በተጨማሪ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ርዳታ ሰጪዎችን እና የውጭ ባለሃብቶችን ቀልብ ለመሳብ የሚያደርጉት ጥረት ኑሮው ይሻሻላል የሚባልለትን ህዝብ እየጎዳ እንደሆነ እና ወደፊትም እንደሚጎዳ ይነገራል ።
ባለፈው ሳምንት በኬንያ ምዋለ ንዋይ ፍሰት ላይ ያተኮረ ጉባኤ ተካሂዶ ነበር ። መንግስት ለጉባኤው ታዳሚዎች ኬንያ ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረች እንደሆነ ገልጿል ። ከዚህ ቀደምም በሙስና ላይ ዘመቻ መጀመሩን አስታውቆ ተቃዋሚ ድርጅቶች ያላመኑበት ነገር ግን በሙስና የተጠረጠሩ ያላቸውን ሃያ ሶስት ዳኞችንም አስሯል ። ተቃዋሚዎች ከዓለም የገንዘብ ድርጅት እና ከለጋሽ ድርጅቶች ርዳታ ለማግኘት የተጠነሰሰ ነው በሚል የዳኞቹን መታሰር ይቃወማሉ ። የዓለም የገንዘብ ድርጅት ከሶስት ዓመት በኃላ በኬንያ ላይ ጥሎ የቆየው ማዕቀብ እንዲነሳ ማድረጉ ተቃዋሚዎች የሚሉትን ሃሳብ የሚያጠናክር ይመስላል ። አይ ኤም ኤፍ ባለፈው ህዳር ዕገዳውን ከማንሳቱ በተጨማሪ የ250 ሚሊዮን ዶላር ፈቅዷል ። ሌሎች የገንዘብ ለጋሾችም አይ ኤም ኤፍ የከፈተውን በር ተከትለው በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ውስጥ አራት ነጥብ አንድ ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት ቃል የገቡት በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ነበር ።
ነገር ግን ይህ ለመንግስት ባለስልጣናት አስደሳች ዜና ፤ ለሲቪክ ማህበራት ደግሞ ጭንቀትን ፈጥሯል ። የኬንያ የሲቪክ ማህበራት መንግስት ብድር ከመቀበል ይልቅ የነበረውን ዕዳ ማሰረዝ አለበት የሚል አቋም አላቸው ። የኬንያ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ብሄራዊ ምክር ቤት የቀድሞው ሊቀመንበር የሆኑት ኦውር ኦንጋዌን ሲናገሩ መንግስት የሚበደረው ገንዘብ መጠኑ ከፍ ካለ ወለድ ጋ በመሆኑ ሸክሙ የህዝብ ነው ። ስለሆነም ልክ ለአካባቢ ሃገራት እንደተደረገው ሁሉ ለኬንያም ሌላ ብድር ከመስጠት ፤ መንግስትም ከመቀበል ይልቅ ሀገሪቱ ያለባት ዕዳ ሊሰረዝ ይገባል ብለዋል ። ኬንያ ያለባት የብድር ዕዳ እንዲሰረዝላት በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው ሌላው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ሃገሪቱ አብዛኛውን ዓመታዊ ገቢዋን ለዕዳ ክፍያ እንደምታውል ገልጾ ይህ አካሄድ እንዲቀየር ይጠይቃል ። የፍትህ ምክር ቤት የተባለው ይኸው ድርጅት ባለፈው ዓመት የወጣውን የሃገሪቱን የበጀት ሰነድ ተመርኩዞ እንደሚለው ለትምህርት ሰላሳ በመቶ ፤ ለጤና አገልግሎት ስምንት በመቶ የሚጠጋ የወጪ ኪሳራ እንዳለባት ያሳያል ። የዚህ ዋነኛ ተጎጂውም ደሃው ህብረተሰብ ነው ። የፍትህ ምክር ቤት ኬንያ ያለባትን ዕዳ እና ገቢ በማነጻጸር እንደሚያስቀምጠው ዕዳዋ ዘጠኝ ቢሊዮን ዶላር ሲሆን ይህ ደግሞ ከብሄራዊ ዓመታዊ ገቢ ሁለት ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ዶላር በሶስት እጥፍ ይበልጣል ።
የሃገሪቱ መንግስት ግን ይህን አሃዛዊ መረጃ እንደ መጨረሻ ማጠቃለያ አይቀበልም ። ኬንያ በርግጥ የ605 ቢሊዮን ዶላር ዕዳ እንዳለባት አምኖ ከዚህ ውስጥ ግማሹ የሃገር ውስጥ ብድር በመሆኑ የሚያሰጋ አይደለም ይላል ። ይንደ ሚንስቴር መስሪያ ቤቱ አሃዛዊ መረጃ ሶስት ነጥብ ሶስቱ ቢሊዮን ዶላር ከሃገር ውስጥ ባንኮች እና አበዳሪዎች የተወሰደ ገንዘብ ነው ። ዕዳው ከሃገር ውስጥ ይወሰድ ከውጭ ይምጣ ብድሩ ሃገሪቱ በዕዳ የምትንቀሳቀስ እንደሆነች ያሳያል እና አንቀበለውም ። የዓለም የገንዘብ ድርጅ እና የዓለም ባንክ የብድር አካሄዱን እንደገና ይመርምሩ የሚለው የኬንያ ሲቪክ ማህበራት እና ድርጅቶች ጥያቄም እንደጨመረ ነው ።