የዩኒቲ ነዋሪዎች እና የመፈናቀል ዕጣቸው
ቅዳሜ፣ ጥቅምት 9 2006
የሱዳን መንግሥት ሰዎቹ የሚሰፍሩበትን ቦታ እንዲያፈላልግለት ኩባንያው ጠይቋል፡ ነዋሪዎቹ ግን ኩባንያው ለቀውት ለሚወጡት የትውልድ ቦታቸው ካሳ እስካልከፈላቸው ድረስ እንደማይወጡ ነው ያስታወቁት።ነዋሪዎቹ እንዲወጡ የሚፈልገው ኩባንያ በደቡብ ሱዳን የሚገኙ የነዳጅ ዘይት ንጣፎችን በሰሜን ካሉት የነዳጅ ዘይት ማጣሪያዎች ጋ የሚያገናኘውን ቧምቧ ገንብቶዋል። ከዚህ በተጨማሪም በሌሎች የነዳጅ ዘይት ንጣፍ ባለባቸው የደቡብ ሱዳንን ከፊሎችም ይንቀሳቀሳል።
የኩባንያው የመስክ ማኔጀር ቤኒ ንጎር ቹል ነዎቹ ለምን እንዲነሱ የፈለገበትን ምክንያት ሲያስረዱ፡« ነዋሪዎቹ ነዳጅ ዘይቱ በሚወጣበት አካባቢ እንዳይኖሩ የሚያስገድዱ በርካታ ምክንያቶች አሉ። በዚህም የተነሳ የደህነነት ጉዳይ ተመልካቹ ክፍላችን እና ልማት ሰራተኞቻችን ነዋሪዎቹ ወደ ደህና አስተማማኝ ቦታ ቢሄዱ የተሻለ መሆኑን ለማስረዳት ካካባቢ እና ከማዕከላዩ መንግሥት ጋ ባንድነት በመስራት ላይ ይገኛሉ። »
የመስኩ ዋና ስራ አስኪያጅ ቹል ምንም እንኳን የዩኒቲ ነዋሪዎች ቀያቸውን ለምን ለቀው የሚወጡበትን ምክንያት በዝርዝር ባይገልጹም፣ በዩኤስ አሜሪካ በካሊፎርንያ ዩኒቨርሲቲ በሀይድሮጅን ሰልፋይድ፣ በድፍድፍ ነዳጅ ዘይት እና ጋዞች ላይ ምርምር ያደረጉት ላና ስክሪቲክ ነዳጅ ዘይት የሚወጣበትን የዩኒቲ ግዛት አካባቢ በተመለከተ ባካሄዱት ጥናት ጠቃሚ መረጃ ሰጥተዋል። ስክሪቲክ እንዳስታወቁት፣ በዚሁ አካባቢ የነዳጅ ዘይት በሚወጣበት ሂደት ወቅት የጤና እክል የሚያስከትለው ሀይድሮጅን ሰልፋይድ የተባለው ንጥረ ነገር ወዳካባቢው ይበተናል። ይህም፣ በጥናቱ መሠረት፣ ቆዳነ፡ ዓይንን እና የመተንፈሻ አካላትን ይጎዳል።
የዩኒቲ የማህበራዊ ጉዳዮች ሚንስትር መንግሥት የነዋሪዎቹን ደህንነት ለመጠበቅ ከኩባንያው ጋ እንደሚሰራ አመልክተዋል። « መንግሥታችን ፣ ማለትም፣ ማዕከላዩ መንግሥት ያወጣው ፖሊሲ ነዋሪዎች ከኩባንያው ጋ የሚተባበሩበት ድርጊት ለሕፃናቱ እና ለራሳቸው ለአካለ መጠን ለደረሱትም ሁሉ ጠቃሚ መሆኑን ያሳያል። ይህ ያካባቢው ነዋሪዎች ኩባንያው ለነዳጅ ዘይቱ ማውጣት ስራው በሚጠቀምባቸው ንጥረ ነገሮች እንዳይጎዱ ለመከላከል የሚያስችል ሌላ መንገድ ነው። »
በዚሁ ግዛት ከሚኖሩት መካከል አንዱ የሆኑት ማኻር ኩባንያው ነዋሪዎችን ወደ ሌላ ቦታ ከማስፈሩ በፊት ትምህርት እና ሀኪም ቤቶችን፡ ንፁሕ የመጠጥ ውኃን፡ የጤና አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎችን እንዲያሟላ ጠይቀዋል።
አርያም ተክሌ
ልደት አበበ