1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዩክሬን ቀውስ፣ የአውሮፓ ህብረትና የሩስያ ግንኙነት

ማክሰኞ፣ የካቲት 25 2006

ትናንት ብራሰልስ ቤልጅየም የተሰበሰቡት የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሩስያ ጦሯን ከዩክሬን ካላስወጣች ከሩስያ ጋር የተጀመረው ንግግር እንደሚቋረጥ እንዲሁም ማዕቀቦች እንደሚጣሉባት አስጠንቅቀዋል ።

https://p.dw.com/p/1BJbu
Ukraine Soldaten Perewalnoje 04.03.2014
ምስል picture-alliance/dpa/RIA Novosti

«አውሮፓ የበርሊኑ ግንብ ከፈረሰ ወዲህ ያለ አንዳች ጥርጥር እጅግ ከባድ ቀውስ ውስጥ ትገኛለች ። ቀዝቃዛው ጦርነት ካበቃ ከ25 ዓመት በኋላ የአውሮፓ አዲስ የመከፋፈል አደጋ እውን ሆኗል »
የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ትናንት በዩክሬን ቀውስ ላይ የተነጋገረው የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች አስቸኳይ ስብሰባ ከመጀመሩ አስቀድሞ የሰጡት አስተያየት ነበር ። በርግጥም ሽታይናማየር እንዳሉት አውሮፓ ከባድ ችግር ውስጥ ነው ያለችው ። በአንድ በኩል በእጇ ልታስገባት በምትፈልገው በዩክሬን የጦርነት ስጋት መስፈኑ በሌላ በኩል በዚሁ ምክንያት ንግድን ጨምሮ በልዩ ልዩ መስኮች ከምትቀራረበው ከሩስያ ጋር ያላት ግንኙነት የመበላሸቱ ስጋት እጅግ አሳሳቢ ሆኗል ። ይህ መነሻ ሆኖ የህብረቱ አባል ሃገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ትናንት ብራሰልስ ቤልጅየም ውስጥ አስቸኳይ ስብሰባ ተቀምጠው በዩክሬን ውጥረቱን በማባባስ በወቀሷት በሩስያ ላይ እርምጃዎችን እንደሚወስዱ አስጠንቅቀዋል ። 28 ሃገራትን በአባልነት ያቀፈው የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳዮች ሃላፊ ካትሪን አሽተን ሩስያ በደቡብ ዩክሬንዋ በክሪምያ ግዛት ወታደሮቿን ማዝመቷን አውግዘዋል ። የሩስያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በዩክሬን ወታደሮችንን ለማስፈር የሩስያ ምክር ቤት ያሳለፈውን ውሳኔ ተጠቅመው ጦራቸውን መላካቸው አሽተን እንዳሉት የአውሮፓ የደህንነትና የትብብር ድርጅት ደንቦችን ጨምሮ ዓለም ዓቀፍ ህግንም የጣሰ እርምጃ ነው ። እንደተቀሩት የህብረቱ አባል ሃገራት የዩክሬን ሉዓላዊነት መከበር አለበት ሲሉ ያሳሰቡት አሽተን ሩስያ ጦሯን ከክሪሚያ ካላስወጣች እንዲሁም በዩክሬኗ ክሪሚያ የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ

እርምጃዎችን ካልወሰደች የአውሮፓ ህብረት ሩስያን እንደሚቀጣ ዝተዋል እንደ አሽተን ህብረቱ በሩስያ ላይ ለመውሰድ ካሰበው እርምጃ እንዱ ለሩስያ ዜጎች የቪዛ አሰጣጥ ደንብን ለማማላት ከሩስያ ጋር የሚያካሂደው ንግግር ለጊዜው እንዲቋረጥ ማድረግ ነው ። በሩስያ ላይ ማዕቀቦችንም የመጣልም አቅድ አለ ።
«የአውሮፓ ህብረትና ሩስያ በቪዛ ጉዳዮች ላይና በአዲስ ስምምነትላይ የሚካሂዱትን ንግግሮች ስለማቋረጥ ተወያይተናል ።በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ ያነጣጠሩ እርምጃዎችንም ለመውሰድ እናስባለን ። »
የአውሮፓ ህብረት በሩስያ ላይ ሊወስድ ያቀዳቸው እርምጃዎች እነዚህ ቢሆኑም ከህብረቱ አባል ሃገራት በተለይ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት በሶቭየት ህብረት ጎራ ስር የነበሩት የምሥራቅ አውሮፓ ሃገራት በሩስያ ላይ ቅጣቱ እንደጠነክርና እንዲፋጠንም ነው የሚሹት ። ሊትዌንያ ፖላንድና ቼክ ሪፐብሊክ ለምሳሌ የሩስያ ዋነኛ ፖለቲከኞች የጉዞ እገዳ እንዲጣልባቸው የባንክ ሂሳቦቻቸውም በአስቸኳይ እንዳይንቀሳቀሱ እንዲደረግ ነበር ፍላጎታቸው ። ይሁንና ህብረቱ ይህን መሰሉንም ሆነ ሌላ የማዕቀብ እርምጃ ተግባራዊ አያደርግም ። ወደዚህ እርምጃ የሚሸጋገረው ሩስያ ወታደራዊውን ውጥረት ለማርገብ ፈጣንና ተዓማኒ የሚሆን አስተዋጽኦ ከማድረግ ከተቆጠበች ነው ። ሌሎች ጠንከር ያሉ እርምጃዎች ማለትም የባለሥልጣናት ገንዘብ እንዳይንቀሳቀስ ማድረግና የመሳሰሉት ደግሞ ከነገ በስተያ የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት መሪዎች ጉባኤ ላይ ሊወሰን ይችል ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል ። የሃንጋሪው ጠቅላይ ሚኒስትር ጃኖስ ማርቶኒ በትናንቱ ስብሰባ ላይ በዩክሬን ሰሞኑን የደረሰው ሃገራቸው እጎአ በ1956 በሶቭየት ህብረት ከተፈፀመባት ወረራ ጋር አመሳስለውታል ። ይህን ንፅፅር በሶቭየት ህብረት ዘመን የተሰቃዩት የሌሎች የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ተወካዮችም ይጋሩታል ። ዩክሬንም በክሪሚያ የተፈፀመብን ህገ ወጥ ድርጊት ነው ስትል አቤቱታዋን ለዓለም አቅርባለች ። ጠቅላይ ሚኒስትር አርስኒ ያትሴንዩክ
«ዛሬ ክሪምያ የሚገኙት ህገወጥ... እደግመዋለሁ በክርሚያ ህገወጥ ኃይልን ነው የሚወክሉት ። የዩክሬኖችን ሃብት ለለመውሰድ ሞክረዋል ፤ የዩክሬኖችን ንብረት ለመውረስም ሞክረዋል ፤ የዩክሬንን ጦር ትጥቅ ለማስፈታት ሞክረዋል ። ለዚህ ድርጊታቸውም በሃገር ውስጥ ና በዓለም ዓቀፍ ህግ ለፍርድ ይቀርባሉ ። ይህን ማወቅ አለባቸው ።»
ሩስያ ግን አሁንም ጦሯን ክሪሚያ ማስገባቴ ህጋዊ እርምጃ ነው ስትል መከራከሯን እንደቀጠለች ነው ። በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሩስያ አምባሳደር ቪታሉ ሹርኪን እንደሚሉት መንግሥታቸው በዚያ የሚገኙ ዜጎቹን ደህንነት ለማስጠበቅ የወሰደው ይህ እርምጃ ህጋዊ ነው ።
«በዩክሬን በተፈጠረው የተለየ ሁኔታ ፣ በጓዶቻችን ላይ ፣ በሩስያ ዜጎች ላይ ፣ በተደቀነው የአደጋ ስጋት በሩስያ ህግ መሰረት እርምጃው ሙሉ በሙሉ ህጋዊ ነው »
የሩስያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ዛሬ በሰጡት መግለጫ የአምባሳደራቸውን ማብራሪያ በሌላ አባባል ተናግረውታል «በዩክሬን የተካሄደው የመንግስት ለውጥ ኢ-ህገመንግሥታዊ መፈንቅለ መንግሥት ነው ሞስኮም የሩስያውያንን ደህንነት ለማስጠበቅ ጦሯን የመጠቀም መብት አላት አሁን ግን እስከዚያ መድረስ ላያስፈልግ ይችላል ሲሉ ። በፑቲን አባባል የምዕራባውያኑ እርምጃ ዩክሬን ወደ ስርዓተ አልበኝነት እንድታመራ አድርጓታል ። ሩስያ በዩክሬን በምትወስደው እርምጃ ምክንያት ምዕራባውያን የሚጥሉት ማንኛውም ማዕቀብ ደግሞ በራሳቸው ላይ መልሶ ችግር የሚያስከትል ሊሆን እንደሚችልም አስጠንቅቀዋል ።
የዩክሬኑ ቀውስ ለመፍታት ጀርመን በምታደርገው ጥረት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽትይናሚር ዛሬ ጄኔቫ ስዊትዘርላንድ ውስጥ ከሩስያው አቻቸው ሰርጌይ ላቫሮቭ ተወያይተው ነበር ። ከውይይቱ በኋላ እንደተናገሩት ግን ለዩክሬኑ ቀውስ በቅርቡ ሊገኝ የሚችል መፍትሄ የለም ነው ያሉት ።እንደ ሽታይንማየር በአሁኑ ሁኔታ ዩክሬንና ሩስያ እንዲነጋገሩ ማድረግ እንኳን አልቻሉም ። ይህ ደግሞ እንደርሳቸው ወደ መጥፎ ውሳኔ ሊያመራ ይችላል ። እናም መፍትሄ ሊያመጡ ይችላሉ ተብለው የሚታሰቡ እርምጃዎችን ሁሉ መሞከር እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት ።
« በዩክሬን ውጥረቱ ቀጥሏል ። ሁኔታውም በጣም የተረበሸ ነው ። በየቀኑ በየሰዓቱ ጭምጭምታዎች ይሰማሉ ። በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ሰዎች ራሳቸውን መቆጣጠር ያለመቻላቸው ስጋት ሊጨምር ይችላል ። ይህ ደግሞ ፖለቲካዊውን ግጭት ወደ አዲስ ደም ማፋሰስ ሊቀይረው ይችላል ። በዩክሬን ብጥብጥ እንዳይከሰት ለመከላከል ሁሉንም አማራጮች መፈተሽ ጠቃሚ ነው ። »
ይህን ማሳካቱ ግን እንዲህ ቀላል እንዳልሆነ የተናገሩት ሽታይንማየር ዛሬ ጄኔቫ የተገኙበት ምክንያት ይህንኑ ጫፍ ለማድረስ መሆኑን አስረድተዋል ። ምንም እንኳን ሩስያ አሁን ከያዘችው አቋም የምትለሳለስ ባይመስልም ሽታይንማየር እንዳሉት ሩስያም የችግሩን ከባድነት ተረድታለች ።
«ከውይይቱ የተረዳሁት ነገር ቢኖር ሩስያዎች የሁኔታውን ከባድነት ተገንዝበዋል ። በዩክሬን ሉዓላዊ ግዛት ውስጥ ምንም ዓይነት የኃይል እርምጃ እንደማይወስዱ ለተናገሩትም ይህ ሩስያውያን በሚወስዷቸው እርምጃዎች መታየትና ተመዝግበውም መቀመጥ እንደሚገባቸው ተንግያለሁ ። እኛ አሁን የምናየው ከእነርሱ ጋር የሚሄድ አይደለም ።»
ሩስያ ጦሯን ወደ ደቡብ ምሥራቅ ዩክሬኗ ግዛት ክሪሚያ ካስገባች ወዲህ ምዕራባውያን ዛቻና ማስጠንቀቂያቸውን ማዥጎድጎድ ቀጥለዋል ። የአውሮፓ ህብረትና ሌሎችም የሩስያ እርምጃ ተቃዋሚ ምዕራባውያን ሩስያ በክሪምያ ወረራዋን ብታራዝም ወይም በሩስያና በዩክሬን መካከል ጦርነት ቢነሳ ምን እንደሚያደርጉ ግን ያሉት ነገር የለም ። የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን እንደሚለው ሩስያ የአውሮፓ ህብረት ሶስተኛው ትልቅ የንግድ አጋር ናት ። በአውሮፓ ህብረትና በሩስያ መካከል 300 ቢሊዮን ዩሮ ወይም 413 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የንግድ ልውውጥ ያካሄዳል ። የአብዛኛዎቹ የዩክሬን ምርቶች ገበያ አውሮፓ ነው ። ሃገሪቱ የሚያስፈልጋት የኃይል አቅርቦት በተለይ የነዳጅ ዘይት ና የተፈጥሮ ጋዝ ፍጆታዋ በአብዛኛው የሚገኘው ከሩስያ በመሆኑ የዚያች ሃገር ጥገኛ ናት ። 25 በመቶ የተፈጥሮ ጋዝ ከሃገር ውስጥ ስታገኝ ፣35 በመቶውን ከሩስያ የተቀረውን 40 በመቶው በሩስያ በኩል ከመካከለኛው እስያ ሃገራት ታስገባለች ። በሌላ በኩል ሩስያ ለምዕራብ አውሮፓ ከምታቀርበው የተፈጥሮ ጋዝ 85 በመቶው የሚያልፈው በዩክሬን በኩል ነው ። ይህ ርስ በርሱ የተሳሰረ የንግድ ግንኙነት አሁን በተፈጠረው ውጥረት ምክንያት አደጋ ላይ ወድቋል ። በአሁኑ ውዝግብ ምክንያት የንግድ ማዕቀብ ቢጣል ሁለቱንም ወገን የሚጎዳ ነው የሚሆነው ። ህብረቱ ማዕቀብ ቢጥል ሩስያም አፀፋውን መመለሷ እንደማይቀር የህብረቱ ኮሚሽን አባላት ጠንቅቀው የሚረዱት ጉዳይ ነው ። ከዚህ ሌላ በማናቸውም ንግድ ላይ የሚጣል ማዕቀብን ተግባራዊ ማድረጉም ሩስያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል በመሆኗ የተለያዩ ደንቦች በሚያደርጉላት ጥበቃ ምክንያት ቀላል አይሆንም ። የአውሮፓ ህብረት ከሩስያ በሚመጣው ነዳጅ ጥገኛ በመሆኑ ይህኛው እርምጃ የሚያዋጣው አይደለም ። ሩስያም ብትሆን የደንበኛዋን የአውሮፓ ህብረት ጥገኛ ናት ። ይህን ገበያ ማጣት አትፈልግም ።አንድ ዓለም ዓቀፍ ጥናት እንደጠቆመው ከሩስያ የውጭ ንግድ ገቢ የ 2/3 ተኛው ምንጭ ከኃይል ሽያጭ ነው የሚገኘው ። ርበርሱ የተሳሰረው የአውሮፖ ህብረት የይክሬንና የሩስያ የንግድ ግንኙነት አሁን በተፈጠረው ቀውስ ምክንያት እንዳይጎዳ የአውሮፓ ህብረት እርምጃውን ቆጥቧል ። ሩስያም እንዲሁ ለጊዜው ብትዝትም የምታጣውን በማስላት አቋሟን ልታለሳልስ መቻል አለመቻሏ ለጊዜው ግልፅ አይደለም ። አንድ ግልጽ ነገር ቢኖር ለወራት በቀጠለው አሁንም ማብቂያ ባላገኘው ውዝግብም ምክንያት የዩክሬን ኤኮኖሚ መጎዳቱን የሃገሪቱም እጣ ፈንታውም ምን እንደሚሆን አለመታወቁ ነው።

EU Außenminister Treffen zur Ukraine 20.02.2014 Brüssel Ashton
ካትሪን አሽተንምስል picture-alliance/dpa
Krim Ukraine Russland Konflikt Soldaten Militärbasis Ukraine
ምስል picture-alliance/dpa
Wladimir Putin Pressekonferenz 4.3.14
ቭላድሚር ፑቲንምስል Reuters
Ukraine Steinmeier in Berlin nach Gespräch mit Lawrow 04.03.2014
ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየርምስል John Macdougall/AFP/Getty Images

ሂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ