1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተችዎች ስርዓተ ትምህርቱ እንዲሻሻል ይጠይቃሉ

ሐሙስ፣ ጳጉሜን 2 2009

« ከ10 ትምሕርት ቤቶች አስተማሪዎችን ሰብስበን ፈተና ሰጥተናቸው ነበር። የሂሳብ አስተማሪዎች 50፣ 40 ፣ 30 ከመቶ ነበር ያገኙት። ጥያቄው ፈተናውን ማለፍ ያልቻሉ ሆኖምሌሎችን ለማስተማር የተቀጠሩ አስተማሪዎች እንዴት ነው ተማሪዎቻቸው ፈተናውን እንዲያልፉ ማድረግ የሚችሉት? » ፕሪንስ ንኩቱ ትምህርትን የሚደግፍ አንድ የዩጋንዳ መያድ ሃላፊ

https://p.dw.com/p/2jXKF
Uganda - Sekundarschule in Kampala: Schülerin
ምስል DW/S. Schlindwein

ተችዎች ስርዓተ ትምህርቱ እንዲሻሻል ይጠይቃሉ

የዩጋንዳ የትምሕርት ስርዓት እጅግ ያደገውን የህዝቧን ቁጥር ግምት ውስጥ ያስገባ ማሻሻያ እየተደረገበት መሆኑ ተነግሯል። ይሁን እና ለድሀ ቤተሰብ ሕጻናት ትምህርት በነጻ በሚሰጥባት በዩጋንዳ ለመርሃ ግብሩ የሚሰጠው ድጎማ ግን አናሳ እና በቅጡም የማይካሄድ ነው የሚሉ ትችቶች ይሰነዘሩበታል። በሌላ በኩል የሀገሪቱ የትምሕርት ሚኒስቴር ተጨማሪ የመንግሥት ትምሕርት ቤቶችን ባለ ማስፋፋት እና ለየግል ትምህርት ቤቶች ይሰጥ የነበረውን ድጎማ ለመቀነስ በማቀድ ይተቻል። ከዩጋንዳ ርዕሰ ከተማ ካምፓላ ወጣ ብሎ በሚገኝ ስፍራ ላይ ያለው ሲቲ ሳይድ የተባለው የሁለተኛ ደረጃ  ትምሕርት ቤት ኦና ሆኗል። የተማሪዎች ድምጽ አይሰማም። በየክፍሉ ሕጻናትም ሆኑ ወጣት ተማሪዎች የሉም። የትምሕርት ቤቱ ምክትል ኃላፊ ዴቪድ ዚምቤ ቀደም ብለው 700 ተማሪዎችን ከትምሕርት ቤቱ አስወጥተዋል። ይህን ያደረጉት መንግሥት ከ800 በላይ ለሚሆኑ የግል ትምሕርት ቤቶች የሚሰጠውን ድጎማ እንደሚያቆም በጋዜጣ ላይ ስላነበቡ ነው። ዚምቤ እንደሚሉት የመንግሥት እርምጃ ያሳደረው ተጽእኖ ቀላል አይደለም። «700 ያህል ተማሪዎች አሉን። ከወጪያቸው አብዛኛው ወደ 60 በመቶ የሚሆነው በመንግሥት ነው የሚሸነፈው። የተጀመረውም በጎርጎሮሳዊው 2008 ዓም ነው። ዓላማው ገንዘብ በማጣታቸው ብቻ መማር ያልቻሉ ነጻ የትምሕርት እድል እንዲያገኙ ማድረግ ነው። ይህ ጥሩ ጅማሬ ነበር። ይሁን እና አሁን በብዙዎች ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እያሳደረ ነው። ስለዚህ ብዙዎች ትምሕርት ቤት መሄድ አይችሉም። እኛም ማን ገንዘብ ሊከፍል እንደሚችል ከወላጆች ጋር ቁጭ ብለን መነጋገር ይኖርብናል። አለበለዚያ በርካታ ተማሪዎች ቤታቸው መቅረታቸው ነው።»
ሲቲ ሳይድ ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤት ዩጋንዳ ውስጥ ከሚገኙት 3ሺህ የግል ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤቶች አንዱ ነው። የመንግሥት ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤቶች ቁጥር ደግሞ ወደ አንድ ሺህ ይጠጋል። ይህ ከተማሪው ቁጥር ጋር ሲነጻጸር እጅግ አነስተኛ ነው። የወሊድ መጠን ከፍተኛ ከሆነባት ከዩጋንዳ ህዝብ ግማሽ ያህሉ ወጣት ነው። ሆኖም በሀገሪቱ 260 ወረዳዎች የመንግሥት ትምሕርት ቤቶች የሉም። በአብዛኛዎቹ ደግሞ የግል ትምሕርት ቤቶች እንኳን አይገኙም። ከዚህ በተጨማሪ የ10,000 ያህል መምህራን እጥረት አለ። ከ2007 ዓም አንስቶ የዓለም ባንክ እና ሌሎች ዩጋንዳ የሚገኙ ዓለም አቀፍ ለጋሾች ድሀ ልጆች የሁለተኛ ደረጃ ትምህሕርት በነፃ እንዲማሩ ለሚረዳ መርሀ ግብር  የገንዘብ ድጋፍ እየሰጡ ነው። ያም ሆኖ አሁንም በቂ ትምሕርት ቤቶች የሉም። በዚህ የተነሳም የዩጋንዳ የትምሕርት ሚኒስቴር ከገንዘቡ በከፊል ዚምቢ ለሚያስተዳድሩት ዓይነት የግል ትምሕርት ቤቶች መርሀግብር እንዲውል አድርጓል። እንዲያም ሆኖ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከግል ትምሕርት ቤቶች ጋር የሚደረገው ትብብር የሚመለከታቸው ኢስማኤል ሙሊንድዋ ፣ መንግሥት አሁን አዳዲስ ትምሕርት ቤቶችን ስለሚገነባ ድጎማው አስፈላጊ አይደለም ይላሉ። መንግሥት በየዓመቱ ከ100 በላይ የግል ትምሕርት ቤቶችን በስሩ የማድረግ እቅድ አለው።
« ሃሳቡ ከአሁኑ የበለጠ የመንግሥት ትምሕርት ቤቶች ሲኖሩን ለግል ትምሕርት ቤቶች የሚሰጠውን ድጎማ መቀነስ ነው። ሆኖም የሚነሱትን ትችት አዘል ጥያቄዎች እንገነዘባለን። የግል ትምህርት ቤቶችን ወደ ኛ ስናዛውር እና አማራጭ የግል ትምሕርት ቤቶች በሌሉበት ይህን መርሃ ግብር ስናቆም ተማሪዎቹ ምን ይሆናሉ? ትምህርት ቤቶቹን ወደ ኛ የማዛወሩን ሂደት በጣም በጥንቃቄ ለማካሄድ ነው ያቀድነው።»
የሀገሪቱ የትምህርት ሥርዓት ተችዎች ግን የትምህርት ቤቶችን ቁጥር ማሳደግ ብቻ ሳይሆን ጥራቱም ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው ይላሉ። ፕሪንስ ንኩቱ ድሀው ኅብረተሰብ ትምህርት የሚያገኝበትን ዕድል የሚያመቻች መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት ኃላፊ ናቸው። የሀገሪቱን የትምሕርት ሥርዓት ሲያጠና የነበረው ነጻ ኮሚሽን አባል ነበሩ።
«በአንድ ወቅት ከ10 ትምሕርት ቤቶች አስተማሪዎችን ሰብስበን ፈተና ሰጥተናቸው ነበር። የሂሳብ አስተማሪዎች 50፣ 40 ፣ 30 ከመቶ ነበር ያገኙት። ጥያቄው ፈተናውን ማለፍ ያልቻሉ ሆኖም ሌሎችን ለማስተማር የተቀጠሩ አስተማሪዎች እንዴት ነው ተማሪዎቻቸው ፈተናውን እንዲያልፉ ማድረግ የሚችሉት? በዚህች አገር በተደጋጋሚ መምህራን በትምህርት ክፍለ ጊዜ አይገኙም። አስተማሪዎቹ ሲቀሩ ተማሪዎቹም ይቀራሉ። ይህም ከትምህርት ቤት የሚቀሩ ተማሪዎች ቁጥር እንዲጨምር አድርጓል። ይህ የሚሆነውም የመምህራን ደሞዝ አነስተኛ በመሆኑ ኑሮን ለማሸነፍ ሌላ የገቢ ምንጭ ስለሚያስፈልጋቸው ነው።»
ንኩቱ የዩጋንዳ ወጣት በዓለም አቀፉ የሥራ ገበያ ተፈላጊ እንዲሆን ሥርዓተ ትምሕርቱ እንዲሻሻል ጥሪ አቅርበዋል። የዩጋንዳ የትምሕርት ሚኒስቴር ግን የትምሕርት ቤቶችን ቁጥር ማሳደግ እንዲቀድምና ከጥቂት ዓመታት በኋላ ደግሞ የሥርዓተ ትምሕርቱ ማሻሻያ እንዲደረግ ነው የሚፈልገው።

Uganda - Sekundarschule in Kampala: Direktor David Zzimbe
ምስል DW/S. Schlindwein
g.jpg
ምስል DW

ዚሞነ ሽሊንድቫይን

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ