1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዮርዳኖሳዊው አብራሪ ዘግናኛ አማሟት

ሐሙስ፣ ጥር 28 2007

ዮርዳኖሳውያን፣ ከትናንት በስቲያ ማክሰኞ ማታ ፤ ራሱን «እስላማዊ መንግሥት » ያለው አሸባሪ ቡድን የጭካኔ ተግባሩ እስከምን ድረስ እንደሆነ ባዩት ቪዲዮ ከጥልቅ ሐዘን ጋር ለመገንዘብ ችለዋል። የጦር አይሮፕላን አብራሪ፣ ሙዓስ ኧል ካሳባ፤ ባለፈው

https://p.dw.com/p/1EWFC
ምስል picture-alliance/dpa

ታኅሳስ ወር ነበረ ሰሜን ሶሪያ ላይ አኤሮፕላኑ ሲመታ በዣንጥላ ወርዶ ፤ የ IS ምርኮኛ የሆነው። ማራኪዎቹ ፤ በአሰቃቂ ሁኔታ መግደላቸው ፤ ዮርዳኖስም በአጸፋው ሁለት የ IS ወገኖችን ከእሥር ቤት አውጥታ በስቅላት መቅጣቷ በዓረቡ ዓለም ብቻ አይደለም፣ በቀሪውም የዓለም ክፍል በማነጋገር ላይ ነው።

Jordanien König Abdullah trifft den Vater des ermordeten Piloten Al-Kaseasbeh 05.02.2015
ምስል picture-alliance/AP Photo/Nasser Nasser

የ F-16 ጦር አይሮፕላን አብራሪ ሙዓስ ኧል ካሳባ ፣ በሕይወት እያለ በእሳት ተንጨርጭሮ እንዲሞት መደረጉ ፤ ቤተሰቡንና ቤተ-ዘመዱን ብቻ አይደለም፤ ከሞላ ጎደል መላውን የሀገሪቱን ሕዝብ እጅግ እንዳናደደና እንዳሳዘነ ነው የሚነገረው። ኧል ገሐድ የተሰኘው የአገሪቱ ጋዜጣ ፣ « እነዚህን አሸባሪዎች ለማሸነፍ አስፈላጊው ሁሉ መሣሪያ አለን፤ የመጀመሪያው መሣሪያ ዛሬ የተወሰደው የስቅላት ርምጃ ነው ማለቱም ተጠቅሷል። ከተገደሉት አንዷ ፣ ወ/ሮ ሳጂዳ ኧል ሪሻዊ የተባሉት ናቸው። እ ጎ አ በ 2005 ማለቂያ ላይ፤ አማን ውስጥ በተለያዩ ሆቴሎች በተጣለና 60 ሰዎች ሕይወታቸውን ባጡበት አደጋ ሴትዮዋ መሳተፋቸው ታውቋል። ከዚያም እንደ ባለቤታቸው ራሳቸውን በሚፈነዳ ቀበቶ ለመግደል ሞክረው ሳይሳካ ቀረና ቆስለው ተያዙ። እናም ሙት በቃ ተበይኖባቸው በእሥር ላይ ነበሩ። የሟች አብራሪ አባት ለልጄ አገዳደል የሁለት ሰው ስቅላት በፍጹም በቂ አይደለም ነው ያሉት። በማድሪድ እስፓኝ የአንድ የዓለም አቀፍ የፖለቲካ ግንኙነት ተማራማሪ ቡድን ባልደረባ ባራሕ ሚካኢል---

«ለዚህ ግንዛቤ ቢኖርም፤ የዮርዳኖስን መንግሥት ርምጃ መገንዘብ ይቻላል። ይሁንና አሁን ለምንገኝበት ሁኔታ መፍትኄ ማስገኘት ስለመቻሉ እርግጠኛ አይደለሁም። የ IS ን (እስላማዊውን መንግሥት) የኃይል ርምጃን በኃይል መመለሱ ወይም መበቃቀሉ የሚያመጣው መፍትኄ አይኖርም።»

«ዐይን ለዐይን ፤፣ ጥርስ ለጥርስ » የሚሰኘው የመበቃቀል መርሕ ለሁለቱም ወገኖች እንደማይበጅ ቢነገርም፣ ዮርዳኖስ ውስጥ ጥቂት ይሁኑ እንጂ ፤ IS አሁንም የሚተማመንባቸው ድጋፊዎች እንዳሉት የሚካድ አይደለም። ወደ ሶሪያ በመዝመት ለ IS የሚዋጉት ዮርዳኖሳውያን በሺ የሚቆጠሩ ናቸው።

Trauer um Moaz Al Kasasbeh
ምስል Jordanische Gemeinde

«ይበልጥ አክራሪ የሆኑ የእስላማዊው መንግሥት ማን ማንጸባረቂያ የሆኑት አቋማቸውን ይለውጣሉ ብዬ አልጠበቅም፣ እስከ ዕለተ ሞታቸው ነው የሚፋለሙት። ሌላ አማራጭ ያላቸው ሆኖ አይታየኝም። ችግሩ ግን፤ በጥሞና እንዴት እንደምንወጣው መልሰን መላልሰን ካላሰብንበት (በምዕራቡ አመለካከት ጭምር ማለት ነው) የውጭ ተወላጆች የሆኑ ሰዎች ይበልጥ ዘና ብለው እንዲኖሩ በዚያ ሀገር የመኖር ዕጣ ፈታቸው እንዴት ሊሰምር እንደሚችል የመንግሥት አቋምም ፤ በሙስሊሙ ዓለም በመላ የሥራ ዕድል በመፍጠር፤ ሙስናን፣ እጅግ በመቀነስ፤ ተስፋ አስጨባጭ የኤኮኖሚ ትልም በመትለም፤ ለህዝቡ አድማሱን ብሩሕ ካላደረጉለት ፣ IS ን ( «እስላማዊውን መንግሥት) አርአያ በማድረግ የሚከተሉት ቁጥር እየጨመረ ነው የሚኼደው።»

የ IS ተዋጊዎች፤ የዮርዳኖስ ተዋላጅ የሆነውን የጦር አይሮፕላን አብራሪ በአሠቃቂ ሁኔታ ሲገድሉ ፣ ማስተላለፍ የፈለጉት መልእክት መኖሩንም ነው ባራሕ ሚካኢል የገለጹት።

«እስላማዊው አገዛዝ በፈጸመው ድርጊት ሳቢያ፤ አብዛኛው የዐረቡ ዓለም ሕዝብ አመለካከት ፣ መንግሥቶቻቸው ሁኔታዎችን ለማስለወጥ፤ ታጋቹን ለማስለቀቅ አለመቻላቸውን እንዲገነዘብ ማብቃት ፤ ዓላማው እንደነበረ ነው የሚጠቁመው።

ከምዕራባውያን አመለካከት አኳያ፣ ድርጊቱ በአስላማዊው መንግሥት ላይ ተቃውሞ እንዲያይል ያደርጋል ተብሎ ነው የሚታሰበው። እስላማዊው መንግሥት ግን ከዚህ በተቃራኒው፤ ጎንኑ ነው የሚመለከተው። ሕዝቡ እነሱን ከመውቀሱ በፊት በመንግሥት ተግባር ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ነው የሚሹት። ይህን አመለካከት መዳሰሱ ጠቃሚነት ይኖረዋል። የእስላማዊውን መንግሥት፣ የአገዛዙ ደንቦች ያልተቀበለ ተመሳሳይ ዕጣ እንደሚያጋጥመው ነው ማስገንዘብ የፈለጉት።

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ