1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደሞዝ ጭማሪ እና የመምህራን ቅሬታ

ሐሙስ፣ የካቲት 30 2009

የኢትዮጵያ መንግሥት በቅርቡ ለመንግሥት ሠራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ማድረጉን አስታዉቋል። የደሞዝ ጭማሪዉ ግን ሁሉንም የመንግሥት ሠራተኞች የሚያካትት እንዳልሆነ ነዉ አሁን መነገር የጀመረዉ።  በተለይም መምህራን የደሞዝ ጭማሪዉ እኛን አይመለከትም ወይ የሚል ጥያቄ ወደ ራዲዮ ጣቢያችን መላክ ከጀመሩ ቀናት ተቆጥረዋል።

https://p.dw.com/p/2YuiF
Geldscheine
ምስል DW/E. Bekele Tekle

Salary increment &Teachers complaints - MP3-Stereo

ከወደ ወሎ ትናንት የደረሰን መረጃ ደግሞ የደሞዝ ጭማሪዉ እንዳልተደረገላቸዉ ያስተዋሉ መምህራን ሥራ ማቆማቸዉን ያመለክታል።

ከሰሜን ወሎ ሀብሮ ወረዳ አካባቢ የደረሰን ጥቆማ መምህራን ከጥር 1 ጀምሮ የተደረገዉን የደሞዝ ጭማሪ እንደማያገኙ በመታወቁ ሥራ ማቆማቸዉን ይገልጻል። ወደአካባቢዉ በመደወል ያነጋገርናቸዉ መምህራን ለደህንነታቸዉ ስጋት እንዳላቸዉ በመግለጽ ስማቸዉን እንዳንገልጽ በማሳሰብ ሁኔታዉን አብራሩልን።  ለመምህራኑ ጭማሪዉ ያልተደረገበት ምክንያት በግልጽ አልተነገረምም ነዉ የሚሉት።

ጭማሪዉ አይመለከታቸዉም የተባለዉ እንደእሳቸዉ ገለጻ ከፍተና ትምህርት ተቋማት ፤ የፍርድ ቤት ዳኞች፣ የጉምሩክ ሠራተኞች እና የገቢዎች ሚኒስቴር ሠራተኞችን ያካትታል። የተጠቀሱት መሥሪያ ቤቶች ከአንደኛ እና ከሁለተኛ ደረጃ መምህራን ጋር ሲነፃጸሩ የተሻለ ገቢ እንዳላቸዉም ሳይገልጹ አላለፉም። መምህራን ሥራ ካቆሙባቸዉ ከሰሜን ወሎዎቹ ትምህርት ቤቶች ሌላም በደቡብ ወሎ አካባቢም ተመሳሳይ ቅሬታ መምህራን እያሰሙ መሆኑም ገልጸዉልናል። ከዚሁ አካባቢ ያነጋገርናቸዉ ሌላኛዉ የሁለተኛ ደረጃ መምህር፤ አስተማሪዎች ሰኞ እና ትናንት ሥራቸዉን ቢያቆሙም በትምህርት ቤት አስተዳደር በስልክ ተጠርተዉ ቅሬታቸዉን ፖሊስ በተገኘበት እንደተወያዩ ያስረዳሉ።

ከዚህ ዉይይት በኋላም ለዛሬ ወደ ሥራ ገበታቸዉ ተመልሰዉ የማምር ማስተማሩ ሂደት መጀመሩንም ዛሬ ደዉለን ጠይቀናቸዉ አረጋግጠዉልናል። የሀብሮ ወረዳ የትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሁሴን መሐመድ መምህራኑ ሥራ አቁመዉ እንደነበረ አረጋግጠዉ፤ ጥያቄያቸዉን አግባብ ባለዉ መንገድ እንዲያቀርቡ በዉይይት እንደተማመኑ ይናገራሉ። ሙሉዉን ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ፤

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ