1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የችሎት ውሎ

ሐሙስ፣ ግንቦት 8 2011

በእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የክስ መዝገብ የተከሰሱ የቀድሞ የደኅንነት መሥሪያ ቤት ኃላፊዎች እና ሠራተኞች ያቀረቡት የዋስትና መብት ጥያቄ ውድቅ ሆነ። አቶ ጌታቸውን ጨምሮ አራት ተከሳሾች በጸጥታ ኃይሎች በቁጥጥጥር ሥር ውለው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ታዘዋል የሚል መረጃ ያሰራጩ ሬድዮ ጣቢያዎች እና ጠቅላይ አቃቤ ሕግ በችሎት ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል።

https://p.dw.com/p/3IcU2
Äthiopien Journalisten Martin Schibbye und Johan Persson
ምስል AP

የእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የችሎት ውሎ

በዛሬው ዕለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት በቁጥጥር ሥር ውለው ክስ የተመሰረተባቸው 22 የቀድሞ የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት ከፍተኛ አመራሮች የተከሰሱበት ወንጀል ዋስትና የሚያስከለክል በመሆኑ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ያቀረቡትን ጥያቄ ውድቅ አድርጓል። የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ከተደረገባቸው መካከል የደህንነት መስሪያ ቤቱ ምክትል ኃላፊ የነበሩት አቶ ያሬድ ዘሪሁን፣ የቀድሞው የአገር ውስጥ ደህንነት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ኡርጌ ይገኙበታል።

ፍርድ ቤቱ አቶ መአሾ ኪዳኔ እና አቶ አማኑኤል ኪሮስ ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄም አልተቀበለውም። የዋስትና መብታቸው ውድቅ የተደረገባቸው እና በዛሬው ዕለት ችሎት የቀረቡ 22 ተከሳሾች ወደ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንዲዘዋወሩ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል። 

ፍርድ ቤቱ በሌሉበት የተከሰሱት አራት የቀድሞው የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት ከፍተኛ አመራሮች በድጋሚ መጥሪያ እንዲሰጣቸው ትዕዛዝ አስተላልፏል። አቶ ጌታቸው አሰፋ፣ አቶ አጽብሃ ግደይ፣ አቶ አሠፋ በላይ እና አቶ ሽሻይ ልዑል የተባሉ የቀድሞ የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ የሥራ ኃላፊዎች በከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት በሌሉበት ክስ የተመሰረተባቸው ሚያዝያ 29 ቀን 2011 ዓ.ም.  ነበር። 

ለአራቱ የቀድሞ ሹማምንት የመጥሪያ ደብዳቤ የማድረስ ትዕዛዝ የተሰጠው የፌድራል ፖሊስ በዛሬው ዕለት ከችሎት ሳይገኝ ቀርቷል። ዐቃቤ-ሕግ በበኩሉ "ለእኛ ትዕዛዝ አልተሰጠንም፤ የመስጠት ግዴታም የለብንም" የሚል ምላሽ ሰጥቷል። "ጋዜጠኞች እንዳትሳሳቱ" የሚል ማስጠንቀቂያ የሰጡት ዳኞች የፌድራል ፖሊስ ለአቶ ጌታቸው አሰፋ እና በሌሉበት የተከሰሱ ሶስት ተጠርጣሪዎች ባሉበት መጥሪያ እንዲያደርስ ድጋሚ ትዕዛዝ ሰጥተዋል። 

በዛሬው ዕለት ፍርድ ቤቱ ለፌድራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ፅህፈት ቤት፣ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እና ሸገር ራዲዮ ጣቢያ "የውሸት ዜና ለምን አስተላለፋችሁ?"  የሚል ጥያቄ አቅርቧል። ከችሎት የቀረቡት የሶስቱ ተቋማት ተወካዮች ያሰራጩት መረጃ ስህተት መሆኑን አምነው ይቅርታ ጠይቀዋል። ይቅርታቸውን የተቀበለው ችሎት ሶስቱን ተቋማት በከባድ ተግሳፅ አልፏቸዋል።

አቶ ጌታቸው አሰፋን ጨምሮ 26ቱ ተከሳሾች "የተሰጣቸውን ኃላፊነት ወደጎን በመተው ከአሰራርና መመሪያ ውጭ ስልጣንን አላግባብ በመጠቀም የግል ተበዳዮችን በሽብርተኝነት በመፈረጅ ወደ አዲስ አበበባ የወንጀል ምርመራ ቢሮ በተለምዶ ማዕከላዊ ተብሎ ወደ ሚጠራው ስፍራ እንዲወሰዱ በማድረግ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት" እንዲፈጸምባቸው አድርገዋል የሚል ክስ ቀርቦባቸዋል።

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።  

ዩሐንስ ገብረ እግዚአብሔር 

ተስፋለም ወልደየስ 

ኂሩት መለሰ