1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዶሃው የአየር ንብረት ጉባዔና አፍሪቃ፣

ዓርብ፣ ኅዳር 28 2005

በቐጠር መዲና በዶሃ ፣ ለ 2 ሳምንታት ሲካሄድ የሰነበተው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ጥበቃ-ነክ ዐቢያ ጉባዔ፣ ዛሬ ያከትማል ተብሎ ቢጠበቅም፤ ድርድሩ በጊዜ እልባት ሊደረግለት ባለመቻሉ፤ ምናልባት ፣ እስከ ነገ ማታ ሳይገፋ እንደማይቀር ተመለከተ።

https://p.dw.com/p/16xzV
ምስል picture-alliance/dpa

በመጨረሻዎቹ ሰዓቶች የጋለ ክርክር ያስነሳውና  በማደራደር ላይ ያለው ጉዳይ፤  አዳጊ አገሮች፣ የአየር ንብረትን መዛባት ለመቋቋም  የጠየቁት የገንዘብ ድጋፍ ነው።በማደግ ላይ  ያሉት  ሃገራት እ ጎ አ  ከ2013 እስከ  2020 ፣  በያመቱ 100 ቢሊዮን ዶላር  እንደሚያስፈልግ ቢያስገነዝቡም ፤ በኢንዱስትሪ የበለጸጉት መንግሥታት  በተለይ ፤ የአውሮፓው ኅብረትና ፣ ዩናይትድ እስቴትስ ፣ አሁን ባለው ሁኔታ ፣ በተጨባጭ  ሁኔታ ቃል እንደማይገቡ ነው ያስታወቁት።

Demo für Klimaschutz in Doha
ምስል DW/A. Rönsberg

 የዶሃው ጉባዔ፣ ታኅሳስ 22 ቀን 2005 የሚያከትመውን የኪዮቶውን የአየር ንብረት ጥበቃ-ነክ ውል ማራዘም ወይም ማደስ የሚቻልበት እንደሚሆን ነው የሚጠበቀው። በአየር ንብረት አጠባበቅ ጉዳይ የሚደራደሩት ወገኖች፤ ከአዳጊ አገሮችና ከበለጸጉት ሃገራት ፤ ከማልዲቨስና ከእስዊትስዘርላንድ፤ ገላጋይ ስምምነት ላይ እንዲደረስ የሚያግባቡ ሁለት ሚንስትሮችን መርጠዋል።   ከኪዮቶው የውል ዘመን  ፍጻሜ በኋላ ፤ የገንዘብ ድጋፍ ለማቅረብ የሚደረግ ስምምነት መንገዱን በማለሳለስ፣ እስከ 2015 ተነድፎ በ 2020  የሚጸድቅ አዲስ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ውል እንዲጸና ማድረግ ያስችላል የሚል ጽኑ ተስፋ አለ። ዶሃ ውስጥ እስካሁን በተደረገው ውይይትና ድርድር፣ ቅር የሚያሰኝ እንጂ የሚያረካ ሁኔታ እንዳልታዬ ነው መገናኛ ብዙኀን የዘገቡት።

በ 30 ያህል አገሮች፤ቅርንጫፍ መ/ቤቶች ያሉት ለተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃ መቆም ዋና መመሪያው የሆነው የጀርመን አረንጓዴ ፓርቲ አጋር የሆነው ፣ ዋና ጽ/ቤቱ በበርሊን የሚገኘው የ ሃይንሪኽ በኧል ድርጅት፤ የብዝሃ-ህይወት ጥበቃ፤ ቀጣይነት ያለው ዕድግት እንዲሁም የአየር ንብረት ፤ የኃይል ምንጭና የተፈጥሮ ሀብት ጉዳዮች ኀላፊ የሆኑትን ወ/ሮ ሊሊ ፉርን አነጋግረናቸዋል።

Symbolbild Klimawandel CO 2 Austoss
ምስል picture-alliance/dpa

«በአሁኑ ጊዜ፤ የሠመረ ሁኔታ አይታይም፤ ያን ያህል የፖለቲካ ፈቃደኝነት የለም። ገንዘብ መስጠት ይገባቸዋል የሚባሉ የአውሮፓውን ኅብረት አባላት የመሳሰሉ አገሮች ያን ለማድረግ ትኩረት አልሰጡም፤ ምነው ቢሉ የራሳቸውን  በጀት ለማስተካከል ሲወጡ ሲወርዱ ነው የሚታዩት። በሌላ በኩል፤ አዎንታዊ ምልክት አልታየም። የኪሣራና ጥፋት ጉዳይ-- ማለት -የአየር ንብረት ለውጥን ተጽእኖ ያዩ ብዙዎች አዳጊ አገሮች ከሁኔታው  ጋር ራሳቸውን ማስታረቅ ይኖርባቸዋል ቢባልም ቀላል አይደለም ስለሆነም ካሳ የምናገኝበት ሁኔታ ይስተካከል ነው የሚሉት። ይህም ነው በዚህ በዶሃ በሰፊው በማነጋገር ላይ ያለው ጉዳይ።»

በአየር ንብረት መዛባት እጅግ ከተጠቁት የዓለም ክፍሎች አንዱ የአፍሪቃው ክፍለ ዓለም መሆኑ እሙን ነው።  ለአፍሪቃ ጥቅም ማነው አሁን በመከራከር ላይ የሚገኘው?

«የአፍሪቃ ቡድን፣ አባላት በተለያዩ ኮሚቴዎች፤ ተመድበው በመደራደር ላይ ይገኛሉ። የአፍሪቃ ተወካዮች፤በልማት እጅግ ወደኋላ የቀሩ አገሮች--ቡድን 77 በሚባሉት ውስጥ የተካተቱ ናቸው እዚህ ዶሃ እንደገና የታዘብነው ምንድን ነው? በብዙዎች አዳጊ አገሮች በአፍሪቃውያኑም ጭምር የአቀራረብም የአቅምም ችሎታ ማነስ ነው የሚንጸባረቀው። ድርድሩ ብዙና ውስብስብም ነው። ቴክኒካዊ ጉዳዮች አሉበት። ሁሉንም በጥሞና መከታተል ያዳግታል። በበኩሌ እዚህ ዶሃ ውስጥ የአፍሪቃ ቡድን ተጠናክሮ ድምፁን ሲያሰማ አላየሁም።»

የኪዮቶውን ውል ያልፈረሙት አየርን በመበከልም በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት ህንድ ቻይናንና   ዩናይትድ እስቴትስን የመሳሰሉ አገሮች፤ የአቋም ለውጥ እስካላሳዩ ደረስ የአየር ንብረት ጥበቃ ለዘለቄታው የሚነገርለትን ያህል ይሣካል? የተጠቀሱት  አገሮች ምናልባት ለውጥ ያደርጉ ይሆን?

የደቡብ አፍሪቃ ተወካይ ሞቶሎሌ ክርቶፈር ሞሴኪ
የደቡብ አፍሪቃ ተወካይ ሞቶሎሌ ክርስቶፈር ሞሴኪምስል DW/A. Rönsberg

«አይመስለኝም! አንዱ ከዚህ መገንዘብ ያለብን፤ እነዚህ መንግሥታት እርስ-በርስ የሚደራደሩ  መሆናቸውንና  የተለያየ የኃይል አሰላለፍ መኖሩን ጭምር ነው። በድርድሩ የነዳጅ ዘይት ኢንዱስትሪውን ጠንካራ ክንድ ለማየት አዳጋች አይደለም። በፖለቲካውም ላይ  ተጽእኖ አለው። በዩናይትድ እስቴትስ፤ የነዳጁ እንዱስትሪ፣ የጠነጠኑ ሃብታም ግለሰቦች፤ («ካርበን ቢሊየኔርስ») የሚባሉት አየር እንዲበከል የሚያደርጉት በሀገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ በፖለቲካው ላይ ተጽእኖ አላቸው። በዚህ በዶሃ ጉባዔ የሚካሄደው በአንዲት የ«ኦፔክ» አባል ሀገር ውስጥ ነው። የኦፔክና የነዳጅ ዘይቱ ኢንዱስትሪ ተጽእኖ በዚህ የአየር ንብረት ጥበቃ ጉዳይ ድርድር ሁላችንንም አሳስቦናል።»

ተክሌ የኋላ

ሸዋዬ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ