1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዶይቼ ቬለ የመናገር ነፃነት ሽልማት

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 13 2008

የዘንድሮውን የዶይቼ ቬለን የመናገር ነፃነት ሽልማት ቱርካዊ ጋዜጠኛ ሴዳት ኤርጊን አሸነፈ ። ሁርየት የተባለው እለታዊ የቱርክ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ኤርጊን የቱርኩን ፕሬዝዳንት ሬሴፕ ታይፕ ኤርዶሃንን ዘልፈሃል የሚል ክስ ተመሥርቶበት እየተሟገተ ነው ።

https://p.dw.com/p/1IaLn
Bobs Award Freedom of Speech Sedat Ergin
ምስል privat

[No title]


ጋዜጠኛ ኤርጊን በሰኔ ወር በሚካሄደው የዶቼቬለ ዓለም ዓቀፍ የመገናኛ ዘዴዎች መድረክ በእንግሊዘኛው GMF ላይ የሚበረከትለትን ሽልማት መጥቶ መቀበሉ ግን ያጠራጥራል ።ዶቼቬለ ለዘንድሮው የንግግር ነፃነት ሽልማት የመረጠው ሴዳት ኤርጊን ፣የዶቼቬለ ዋና ስራ አስኪያጅ ፔተር ሊምቡርግ እንዳሉት ቱርክ ውስጥ ነፃ ዘገባ ለማቅረብና የፕሬስ ነፃነትን ለማስከበር የሚታገሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ጋዜጠኞችን እጣ ፈንታ ይጋራል ። ሁርየት የተባለው ታዋቂው የቱርክ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሴዳት ኤርጊን የቱርኩን ፕሬዝዳንት ሬቼፕ ታይፕ ኤርዶሃንን ዘልፈሃል ተብሎ ክስ ተመስርቶበት ካለፈው መጋቢት አንስቶ ፍርድ ቤት እየተመላለሰ ነው ።አቃቤ ህግ ሴዳት ኤርጊንን የከሰሰው በዚህ ዓመት በመስከረም ወር ፕሬዝዳንቱ የኩርድ ሚሊሽያዎች በቱርክ የፀጥታ ኃይሎች ላይ ጥቃት ካደረሱ በኋላ ስለ ሰጡት መግለጫ በፃፈው ሀተታ ምክንያት ነው ። አቃቤ ህግ ኤርጊን በመግለጫው ቀልዷል ሲል ነው የከሰሰው ። ኤርዶሃን ዘልፋቸዋል ተብለው የተከሰሱ ሌሎች ጋዜጠኞችም አሉ ። ኤርጊን መጋቢት አጋማሽ ላይ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት በሰጠው አስተያየት « በ2016 የቱርክ የፕሬስ ነፃነት በፍርድ ቤት ኮሪደሮች ተገድቧል »ብሎ ነበር ። ነፃ የሚባለው የኤርጊን ጋዜጣ የሁርየት ዋና ቢሮ በጎርጎሮሳውያኑ 2015 ሁለት ጊዜ በመንግሥት ደጋፊዎች ጥቃት ደርሶበታል ። ኤርጊን በተመሰረተበት ክስ እስከ አምስት ዓመት የሚደርስ እሥራት ሊፈረድበት ይችላል ። የዶቼቬለ ዋና ስራ አስኪያጅ ፔተር ሊምቡርግ ፣ ኤርጊ ለዘንድሮው የዶቼቬለ የንግግር ነፃነት ሽልማት የተመረጠበትን ምክንያትም ሲያብራሩም ።
« ሴዳት ኤርጊ ሽልማቱን ማግኘት የሚገባው ትክክለኛው ሰው ነው ።እሱ በቱርክ ሃሳብን በነፃ ለመግለፅ እንዲሁም ለፕሬስ ነፃነት እና ለጋዜጣው የቆመ ሰው ነው ። የቱርክ ባለሥልጣናት ቱርክ ውስጥ ጋዜጠኞችን አርቲስቶችንና ሳይንቲስቶችን ማዋከባቸውን ከአሁን በኋላ ልንቀበል አንችልም ። እኛ እንደ ዶቼቬለ ይህ ባህርይ ተቀባይነት እንደሌለው መልዕክት ማስተላለፍ እንፈልጋለን ። »
ጋዜጠኞች በተለያዩ ዘዴዎች ሲታፈኑ ዝም አንልም ያሉት ሊምቡርግ በጎርጎሮሳዊው 1962 በቱርክ ቋንቋ የራድዮ ሥርጭት የጀመረው ዶቼቬለ ከቱርክ ህዝብ ጋር የተጠናከረ ወዳጅነት እንዳለውም አስታውሰዋል ። ከ1995 ጀምሮ ደግሞ ዶቼቬለ በቱርክ ቋንቋ ድረ ገፁ የተለያየ ይዘት ያላቸውን መልዕክቶች ያስተላልፋል ። የቱርክ ጋዜጠኞች ማህበር እንደሚለው ቱርክ ውስጥ የጋዜጠኞች ነፃነት በመገደቡ ህዝቡ ነፃ የመረጃ ምንጭ የለውም ። በአሁኑ ጊዜ 21 ጋዜጠኖች ታስረዋል ። በጋዜጠኞች ላይ በሚደረገው ጫና ምክንያት በርካታ መገናኛ ብዙሃን በራሳቸው ላይ ቅድመ ምርመራ ለማድረግ መገደዳቸው ይነገራል ።ለጋዜጠኞች መበት የሚከራከረው ድንበር የለሽ ዘጋቢዎች የተባለው ድርጅት ትናንት ባወጣው የዓለማችን የፕሬስ ነፃነት ዘገባ መዘርዝር ውስጥ ከሰፈሩት 180 ሃገራት ቱርክ 151 ኛ ደረጃ ነው የተሰጣት ። የቱርኩ ጋዜጠኛ የሚሸለመው የዶቼቬለ «ሃሳብን በነፃ የመግለፅ ነፃነት ሽልማት» ፣ ለሰብዓዊ መብትንና ለመናገር ነጻነት የሚሟገቱ ለሚያበረታቱ የኢንተርኔት ፀሃፊዎች የሚሰጠው ቦብ የተሰኘው ሽልማት አንዱ አካል ነው ። በጎርጎሮሳዊው 2015 የመጀመሪያው የዶቼቬለ ሃሳብን በነፃ የመግለፅ ነፃነት ሽልማት የተሰጠው ለሳውዲ አረብያዊው የኢንተርኔት አምደኛ ራያፍ በደዊ ነበር ። በፅሁፎቹ እስልምናን ዘልፈሃል ተብሎ የተፈረደበት በደዊ ከዛሬ 4 ዓመት አንስቶ በእስር ላይ ይገኛል ። ሽልማቱን ባለቤቱ ኤንሳፍ በደዊ ተቀብላለች ። ኤርጊን ሽልማቱ የሚሰጠው በመጪው ሰኔ ቦን ውስጥ በሚካሄደው የመገናኛ ብዙሃን መድረክ ላይ ነው። ክሱ በመታየት ላይ ያለው ኤርጊን ሽልማቱን ቦን መጥቶ መቀበሉን ግን ከወዲሁ ለማወቅ ይቸግራል ።

Peter Limbourg
ምስል DW
Freedom of Speech Award
ምስል DW/M.Müller

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ