1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን መከላከያ ሚንስትር በአፍሪቃ

ሰኞ፣ መስከረም 15 1999

ከየአቅጣጫዉ እንደሚያታየዉ የአዉሮጳ ሠራዊት ኮንጎ የሚቆይበት ጊዜ በፊት ከታሰበዉ በላይ መሆኑ አይቀርም።መከላከያ ሚንስትር ፍራንዝ ዮሴፍ ዩንግ ባሁኑ ጉብኝታቸዉ ሥለሠራዊቱ ተልዕኮ ግልፅ መረጃ ይዘዉ ይመለሳሉ ተብሎ ነዉ የሚጠበቀዉ።

https://p.dw.com/p/E0i4
የጀርመን ወታደሮች
የጀርመን ወታደሮችምስል AP



የጀርመኑ መከላከያ ሚንስትር ፍራንዝ ዮሴፍ ዩንግ በሰወስት የአፍሪቃ ሐገራት የሚያደርጉትን ጉብኝት ትናንት ከጅቡቲ ጀምረዋል።ዩንግ በጅቡቲ ቆይታቸዉ ቀይ-ባሕርና አደን ባሕረ-ሠላጤ የሰፈረዉን የጀርመን በሕር-ሐይል ጦርን ይጎበኛሉ።የጀርመኑ መከላከያ ሚንስትር ከጅቡቲ ቀጥሎ ጋቦን፣ አከታትለዉ ኮንጎ ዲሞክራቲሪፐብሊክ የሰፈረዉን የሐገራቸዉን ሠራዊት ይጎበኛሉ።ዩንግ ሰወስት ቀን በሚቆየዉ ጉብኝታቸዉ ከሰወስቱ ሐገራት ባለሥልጣናት ጋርም ለመወያየት ቀጠሮ አላቸዉ።

መከላከያ ሚንስትር ፍራንዝ ዮሴፍ ዩንግ አፍሪቃ የሠፈረ ጦራቸዉን ለመጎብኘት የተነሱት የጀርመን ሠራዊት ወደ ሊባኖስ ይዝመት በሚለዉ ሐሳብ ላይ ይደረግ የነበረዉ ክር-ክርና ሙግት በሐገሪቱ ምክር ቤት ዉሳኔ ደርዝ ከያዘ በሕዋላ መሆኑ ነዉ። ካገባደድነዉ የአዉሮጳዉያኑ ሁለት ሺሕ ስድስት መባቻ ጀምሮ ሲያከራክር የነበረዉ የጀርመን ሠራዊት ወደ ኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ የመዝመቱ ጉዳይ አሁን ለሊባኖሱ እንደሆነ ሁሉ በምክር ቤት ዉሳኔ፣ በዘመቻዉ ከተቆጫ ወራት ተቀጠሩ።

የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ምርጫ እንዳይታጎል ከአደጋ ለመከላከል የዛሬ ሁለት ወር ግድም ከዘመተዉ አንድ ሺሕ ሁለት መቶ የአዉሮጳ ሕብረት ሠራዊት ሰባት መቶ ሰማንያዉ የጀርመን ነዉ።ከዚሕ መሐል ግንባር ቀደምቶቹ ሰወስት መቶ-አስር ወታደሮች ርዕሥ-ከተማ ኪንሻሳ ሰፍረዋል።በደጀንነት የሚጠባበቁት አራት መቶ ሰላሳ ወታደሮች ደግሞ ጋቦን ናቸዉ።

በኮንጎ የአርባ አመት ታሪክ የመጀሪያዉ የተባለዉ ምርጫ ባለፈዉ ሐምሌ ማብቂያ ተደርጓል።ይሁንና በተለይ ለፕሬዝዳትነት ከተወዳደሩት እጩዎች ግልፅ አሽናፊ ሥለሌለ በመጪዉ ጥቅምት ማብቂያ የመለያ ምርጫ ይደረጋል። የምርጫዉ ሒደት መጓተት ለአራት ወር ኮንጎ ይቆያል ተብሎ የዘመተዉ የጀርመን ሠራዊት እዚያ የሚቆይበትን ጊዜ ያራዝመዋል ተብሎ ነዉ የሚታሰበዉ።የመከላከያ ሚንስቴር ቃል አቀባይ ቶማስ ራአበ ግን ቅይጥ ነዉ መልሳቸዉ።

ባሁኑ ወቅት (ሠራዊቱ) እዚያ የሚቆይበት ጊዜ የሚራዘምበትን ሁኔታ የሚጠቁም ምንም አይነት ምልክት የለም።እንደምታዉቁት የመለያዉ ምርጫ ጥቅምት ማብቂያ ላይ ይረጋል ተብሎ ነዉ የተቃደዉ።ያኔ ነዉ ሁሉም ነገር የሚሆነዉ።»

የቀድሞዉ የአዉሮጳ ሕብረት የዉጪ ግንኙነት ሐላፊ ክሪስ ፓተን በቅርቡ እንዳስታወቁት ጀርመንና ፈረንሳይ በጋራ የሚያዙት የአዉሮጳ ሕብረት ሠራዊት EUFOR የኮንጎ ምርጫ ተጠናቅቆ አዲስ መንግሥት እስኪመሰረት ድረስ እዚያዉ መቆየት አለበት።የፓተንን ሥልጣን የተረከቡት ወይዘሮ ቤኒታ ፌሬሮ-ቫልድነር ኒዮርክ ለተሰየመዉ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ እንደነገሩትም ሕብረቱ የሠራዊቱን ተልዕኮ ሳያራዝም አይቀርም።

«EUFOR እዚያ ኮንጎ መስፈሩ በመሠረቱ እጅግ በጣም በጣም አስፈለጊ ነበር።ከምርጫዉ በሕዋላ ችግር ተፈጥሮ እንደነበር ታዉቁታላችሁ።ችግሩ የተወገደዉ በጠንካራዉ በቅጡ በተዘጋጀዉ በአዉሮጳ ሕብረት ሠራዊት ነዉ።እኔ እንደማምነዉ ይሕ ሁኔታ ግጭትና ሁከት ባለበት ወቅት ተገቢዉ ሐይል በተገቢዉ ሥፍራ መገኘት ምን ያሕል ጠቃሚ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነዉ።»


በኑዮርኩ ጉባኤ የሚሳተፉት የጀርመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር ከኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳት ዮሴር ካቢላ ጋር ተገናኝተዉ ሥለ ኮንጎ ምርጫ በተለይም ሥለሠራዊቱ ተልእዕኮ አስንተዉ ተነጋግረዋል።ከየአቅጣጫዉ እንደሚያታየዉ የአዉሮጳ ሠራዊት ኮንጎ የሚቆይበት ጊዜ በፊት ከታሰበዉ በላይ መሆኑ አይቀርም።መከላከያ ሚንስትር ፍራንዝ ዮሴፍ ዩንግ ባሁኑ ጉብኝታቸዉ ሥለሠራዊቱ ተልዕኮ ግልፅ መረጃ ይዘዉ ይመለሳሉ ተብሎ ነዉ የሚጠበቀዉ።

ዩንግ ትልቁ ሥራና ዉይይት ጋቦንና ኮንጎ ቢጠብቃቸዉም ጉብኝታቸዉን የጀመሩት ከጀብቲ ነዉ። ጅብቲ ባሕር ላይ የአሽባሪዎችን እንቅስቃሴ የሚከታተሉ ሁለት መቶ ሠልሳ ሰወስት የጀርመን ባሕር ሐይል መታደሮች ሠፍረዋል።