1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን ርእሰ ብሔር የገና በዓል ንግግር

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 16 2002

የጀርመን ርእሰ ብሔር ሆርስት ከኧለር፣ በዘንድሮው የገና በዓል ባሰሙት ንግግር ላይ የመልእክታቸው መሪ ቃል ፣ «ጥንቃቄ » ወይም «ጥንቃቄ ማድረግ » የሚለው ነው። 200 9 በአዲሲቱ ጀርመን አንድ ልዩ ታሪካዊ ድርጊት የተከናወነበት እንደነበረ ከኧለር በማስታወስ---

https://p.dw.com/p/LDcu
ፕሬዝዳንት ሆርስት ከኧለርምስል AP

«ከ 20 ዓ መት በፊት የግንቡ አጥር የፈረሰበትን ሁኔታ በማስታወስ ሁላችን በጋራ ሐሴት አድርገናል። «ህዝብ እኛ ነን !» በሚል ጥሪ፣ ያኔ ያስተጋባው ድምፅ፣ እስከዛሬ ድረስ ሁላችንንም የሥራ ኀላፊነት ያሸከመ ነው። ዴሞክራሲ ስንል፣ እኛ ሁላችን ነን ። ሁላችንም ለአገራችን የሚቻለንን ሁሉ ማድረግ እንችላለን። »

ርእሰ-ብሔር ሆርስት ከኧለር፣ ጀርመን ውስጥ ፣ ቪነደን በተባለችው ከተማ 15 የትምህርት ቤት ልጆች፣ በአጥፍቶ ጠፊ ተማሪ ህይወታቸው በአጭር የተቀጨችበትን ዘግናኝ ሁኔታ በመጥቀስ፣ ለጸጥታም ሆነ ከጉዳት ራስን ለመጠበቅ አንዳች ዋስትና እንደሌለ ከመጠቆማቸውም፣ ያን የመሰለው ድርጊት እንዴት ሊከሠት ቻለ? ብለን መጠየቃችን አልቀረም፣ ታዲያ፣ በአብሮነት የኑሮ ዘዴአችን፣ የሳትነው፣ ያላስተዋልነው አንድ ጠቃሚ የሆነ ነገር መኖሩን ስሜታችን ሳይነግረን አልቀረም ነው ያሉት።

ርእስ-ብሔር ከኧለር፣ በአፍጋኒስታን ስለተሠማሩት ወታደሮች እንደሚያስቡና ለአገልግሎታቸው ላቅ ያለ ትርጉም እንደሚሰጡት ነው የገለጡት። ከሀገር ርቀው የፖሊስም ሆነ የእርዳታ ተግባር የሚያከናውኑትን ፣ ጸጥታን አስተማማኝ ለማድረግ፣ ሰላምንም ለማስፈን የተሰለፉትን ሁሉ እንኳን ለገና በዓል አደረሳችሁ! ብለዋል።

ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ቀውስ በማጋጠሙ የደረሰውን ጉዳት ፣ የጠቀሱት ከኧለር ፣ የጋራ በሆነችው ምድራችን ስህተቶችን ተገንዝቦ፣ ያን ማረምና ማቃናት ፣ ኀላፊነትንም መሸከም እንደሚገባ ሳያስገነዝቡ አላለፉም። ገንዘብ የሰዎች አገልጋይ እንጂ ገንዘብ ገዥአቸው ሊሆን እንደማይገባ የገለጡት ሆርስት ከኧለር ፣ ንግግራቸውን በመቀጠል---

«በጥንቃቄ መኖር ማለት ለፍትኀዊ ሥርዓት መቆም ነው። እዚህ በእኛ አገርም ሆነ ፣ በዓለም ዙሪያ፣ እናም ገና ብዙ መሠራት አለበት። » ብለዋል።

በቤት ውስጥ ከውሃ ቧንቧ ውሃ እንደልብ የምናገኝ እንደመኖራችን መጠን፣ በሌሎች የዓለም ክፍሎች የሚጠጣ ውሃ ፍለጋ ብዙ ኪሎሜትር ርቀት መጓዝ ግድ የሆነባቸው መኖራቸውን መዘንጋት አይገባም። የኑሮ ደረጃን ከተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃ ጋር በማያያዝ ከፍ ለማድረግ በንቃተ-ኅሊና መኖር ያሻል። የምንከተለው ፖለቲካ፤ ከቀን አልፎ በረጅሙ ለማሰብና ለመሥራት የሚያስችል ሊሆን ይገባል። ጥንቃቄ የማድረግን ዬትም ቦታ እውቅና የመስጠትንም ባህል ማዳበር ይበጃል። ይህ በፊናው አመኔታን ያስገኛል። እያንዳንዳችንም በዚህ ረገድ አስተዋጽዖ ማድረግ እንችላለን» እናም፣ «ለሁላችሁም አስደሳች የገና በዓልና መልካም አዲስ ዘመን ይሁንላችሁ!» ብለዋል።

Tekle Yewhala