1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን ወጣቶች የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውድድር፤

ረቡዕ፣ ግንቦት 27 2006

ከ 2 ሳምንት በፊት በዚህ ክፍለ ጊዜ ባቀረብነው ዝግጅት፣በብሪታንያ ከ 300 ዓመታት በፊት በፓርላማ ተመክሮበት ከጸደቀ በኋላ የተጀመረው፤ ለሕብረተሰብ ጠቀሜታ የሚሰጥ፤ «ሎንግትውድ የሳይንስና ሥነ ቴክኒክ ሽልማት ፣ አሁንም ደንቡ የጸደቀበት 300ኛ

https://p.dw.com/p/1CBmX
ምስል picture-alliance/dpa

ዓመት በመጪው ሐምሌ ወር ሲታሰብ ፣ ለፕላኔታችን ይበጃሉ ከተባሉ 6 የምርምር አርእስተ ጉዳዮች መካከል በቴሌቭዥን ተመልካቾች ለሚመረጠውና ፤ በምርምር አመርቂ ውጤት ለሚገኝበት ጉዳይ፣ ከወዲሁ፣ 10 ሚሊዮን ፓውንድ ሽልማት መመደቡን ማውሳታችን ይታወስ ይሆናል።

የሳይንስና ሥነ ቴክኒክ ዝንባሌም ሆነ ተሰጥዖ ያላቸው ተመራማሪዎች፤ በበለጸጉት አገሮች የሚሰጣቸው የቃላት ማበረታቻና ፣ የቁሳቁስም ሽልማትም የቱን ያህል እንደሚያነቃቃ መገመት የሚያዳግት አይደለም። በተለያዩ ደረጃዎች ፤ በተማሪዎች ፤ በምርምር ተቋማት፣ በግልና በቡድን ለሚደረጉ ውድድሮችም ሆነ አዳዲስ ግኝቶች፤ ከተለያዩ የማሕበረሰቡ ክፍሎች፤ ከማሕበራት ፤ ከኢንዱስትሪዎችና ከመንግሥትም በየጊዜው ሽልማቶች ይሰጣሉ። ለምሳሌ ያህል ፤ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ግሥጋሴ ከታወቁት አገሮች አንዷ በሆነችው በጀርመን ፤ ከተለያዩ የሳይንስና ቴክኖሎጂ የምርምር ተቋማት ሌላ ፤ የሁለተኛ ደረጃ የቀለም ተማሪዎችም ፤ የፈጠራ ውጤቶቻቸውን ለህዝብ እንዲያቀርቡ በያመቱ ውድድር ይዘጋጅላቸዋል።

Johanna Wanka
ምስል Picture-Alliance/Tagesspiegel

STERN =ኮከብ፣ የተሰኘው ታዋቂ መጽሔት ዋና አዘጋጅ በነበሩት ሄንሪ ናነን ፣ እ ጎአ በ 1965 ዓ ም፤

የተቋቋመው፣ ወጣቱ ትውልድ ይመራመራል» Jugend forscht በመባል የታወቀው በህግ የተመዘገበ አገር አቀፍ ማሕበር፣ ከመላው ጀርመን የተውጣጡ ወጣቶችን ሲያወዳድር ዘንድሮ 49 ኛ ዓመቱ ነው።

«ሐሳብህን ( ሐሳብሽን ) ተጨባጭነት ያለው እንዲሆን አብቃ (አብቂ)» በሚል መፈክር ነበረ ለምሳሌ ያህል የዘንድሮው ማለትም እ ጎ አ የ 2014 የውድድር ምዕራፍ የተጀመረው። በሒሳብ፤ የመረጃ ሳይንስ፤ የተፈጥሮ የሳይንስ ዘርፎች እንዲሁም ሥነ ቴክኒክ ተሰጥዖም ሆነ ዝንባሌ ያላቸው፣ በአመዛኙ የሁለተኛ ደረጃ የቀለም ተማሪዎች፤ ዩንቨርስቲ የጀመሩ ጭምር ፤ በአጭሩ በ 15 እና 21 ዓመት የዕድሜ እርከን መካከል የሚገኙ ወጣቶች ፤ የመወዳደር ዕድል አላቸው። መወዳደር የሚቻለው በተናጠል በጥንድ አለበለዚያ 3 ወጣቶች በሕብረት ሊሳተፉ በሚችሉበት ቡድን ነው። በጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ ከሚገኙት 16 ፌደራል ክፍላተ ሀገር መካከል ዘንድሮ ለውድድር የተመዘገቡት 12,298 ወጣቶች (ወንዶች ወጣቶችና ልጃገረዶች) ሲሆኑ፣ ከአንድ ሺ በላይ ተወዳዳሪዎችን ያቀረቡት ክፍላተ ሀገር 5 ነበሩ። እነርሱም፤

ውድድሩን ያስተናገደው ክፍለ ሀገር ባደንቩርተምበርግ፤ 1,413

ባየርን (ባቬሪያ) 2,020

ታኅታይ ሳክሰኒ(ኒደርዛኽሰን) 1,249

ሰሜን ራይን(ኖርድ ራይን)ቬስትፋሊያ 1,998

እንዲሁም

ራይንላንድ ፋልትዝ 1,350

ናቸው።

Jugend Forscht 2013 Bundessieger Mathematik Informatik
ምስል Stiftung Jugend forscht e. V.

ከእነዚህ ሁሉ ተጣርቶ ፤ መጨረሻ ላይ የቀረቡት ተወዳዳሪዎች 409 ነበሩ። በባደንቩርተምበርግ ፌደራል ክፍለ ሀገር ሽቬቢሽ ሃል አቅራቢያ በምትገኘው Künzelsau በተሰኘችው ከተማ ካለፈው ኀሙስ አንስቶ እስከ እሁድ (4 ቀናት) በተካሄደው ውድድር 114 የምርምር ፕሮጀክቶች ነበሩ ለተጋባዥ እንግዶች ቀርበው የታዩት። የዘንድሮውን ውድድርና የሽልማት አሰጣጡን ሥነ ሥርዓት ያዘጋጁት ፤ ራሱ « በህግ የተመዘገበው ማሕበር ፣ ዩገንድ ፎርሽት» እና ፤ ሁለት ኩባንያዎች፤ Adolf Würth GmbH እንዲሁም Co. KG ናቸው። የሁለቱ ኩባንያዎች የሥራ አመራር ቃል አቀባይ፣ ኖርበርት ሄክማን ባሰሙት ንግግር ላይ እንዳሉት ከሆነ «ወጣቱ ይመራመራል ፣ ማሕበር»

በየጊዜው የሚያቀርባቸው ተሰጥዖ ያላቸው ወጣቶች፤ ኤኮኖሚው ያጋጠመው ክፍተት እንዲሞላ ፣ የሰለጠነ የሰው ጉልበት እጥረትም ከሞላ ጎደል እንዲወገድ የሚረዱ ናቸው። 1,100 ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት ሥነ ሥርዓት ላይ የትምህርትና ምርምር ጉዳይ ሚንስትር ፕሮፌሰር ፣ ዶ/ር ዮሐና ቫንካ፤ ከርእሰ ብሔር ጋውክና ባልተቤታቸው የቀረበውን ሽልማት ለኣሸናፊዎቹ አድለዋል።

እጅግ አሥመስጋኝ ተጋባር አከናውነዋል ተብለው ላቅ ያለ ሽልማት ያገኙት የ 17 ዓመቱ ወጣት Lukas Höhne እና የአንድ ዓመት ታናሹ Lukas Gräfner ናቸው። የ Sachsen –Anhalt ፌደራል ክፍለ ሀገር ኑዋሪዎች የሆኑት ሁለቱ ወጣቶች፤ 3 ማዕዘናዊ ምስል የሚያሳይ ማተሚያ በተለይም ያለተዛነፈ ቅርጹን እንደያዘ ለሚሽከረከር ምስል ግኝታቸው ተስማሚ ነው ተብሏል።

የትምህርትና ምርምር ሚንስትር ፕሮፌሰር ዶ/ር ዮሐና ቫንካ ፤ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች የምርምር ተነሳሽነት እንዳረካቸው በመግለጽ፤ ስለ ማህበሩ ዝግጅት ጠቀሜታ እንዲህ ነበረ ያሉት---

«ወጣቱ ይመራመራል» የተሰኘው ዝግጅት ፣ ወጣቶች፣ የቴክኒክና ሳይንስ ጽኑ ፍላጎት እንዲያድርባቸው የሚያስችል እጅግ ጠቃሚ ጉዳይ ነው። ከእንዲህ ዓይነት ፣ በፌደራል ደረጃ ከፍተኛ የውድድር ፍጻሜ ላይ መድረስ ሌላው ማራኪ ሁኔታ ነው። ይህ ለወጣቶች ለኑሮም ሆነ በኑሮ ውስጥ አንድ ትልቅ በር እንዲከፈት በማድረግ አንድ እመርታ ይሆንላቸዋል።»

ከባደን ቩርተምበርግ ፌደራል ክፍለ ሀገር ፣ ሊዮናርድ ባዎርስፌልድ የተባለው የ 16 ዓመት ወጣት፣ መስክ ላይ በጎማም ሆነ ቀጭን የብረት ቧንቧ የሚረጭ ውሃ ፤ መፈናጠሩ ቀርቶ በስበት ኃይል ዙሪያውን እንዲሽከረከር ማድረግ የሚቻልበትን ብልሃት በማሳየቱ የጀርመን መራኂተ-መንግሥት ያሰናዱትን ሽልማት ለማግኘት በቅቷል።ከዚያው ክፍለ ሀገር ሌሎች የ 19 ዓመት ወጣቶች፤ አድሪያን ሁክና ዳንኤል ሃይድ፤ እንዲሁም የ 17 ዓመቱ ራፋኤል ኳድቤክ ባዮጋዝ ከድኝ ቅልቅል ነጻ የሚሆንበትን መንገድ በማሳየታቸው ከትምህርት ሚንስትሯ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተቀብለዋል።

በሥነ ሕይወት (ቫዮሎጂ) ከሃምበርግ ፤ የ 16 ዓመቱ ወጣት Felix Höfer ለምግብ የሚውል ቅጠላ- ቅጠል፤ በአንዳንድ የፕሮቲን ዓይነቶች ርዳታ፤ ብርሃንን ሲቀበሉ ምን ዓይነት ለውጥ እንደሚያሳዩ ያደረገው ምርምር አድናቆትን አትርፎለታል። ታዲያ ለሽልማት የበቃ በውድድር ያሸነፈ ሰው ምንድን ነው የሚሰማው የሚል ጥያቄ ቀርቦለት ይህን ነበረ የተናገረው።

Kugellager aus 3D Drucker Fab Lab in Aachen
ምስል Jutta Wasserrab

«እርግጥ ነው፤ ማመን ነው ያቃተኝ፤ ምክንያቱም ፤ በዛ ያሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ነበሩና! እናም ፣ ከሞላ ጎደል ፣ ማመን ተስኖኛል!»

ፌሊክስ፣ በሥነ ሕይወት (ባይሎጂ) የሚያዘወትርበት ጉዳይ ሳይኖረው ፣ ይህን ምርምር ለማድረግ ሐሳቡ እንዴት እንደመጣለትም ተጠይቆ ነበር---

«በሃምበርግ የተማሪዎች ውድድር አለ። ከጽሑፍ ሌላs፤ በተጨማሪ መታየት ያለበት ፣ ለምሳሌ አትክልቶች የተለያዬ ቀለም ያለው መብራት እየበራባቸው ሲያድጉ ምን ዓይነት ለውጥ ይከሠታል፤ ምን ዓይነት ለውጥ ይታይባቸዋል? ፣ አንዱ የ «ወጣቱ ይመራመራል » ፕሮጄክቴ ይህ ነበር። »

ታዲያ፤ የዚህን ምርምር ውጤት እምን ላይ ማዋል ይቻላል? የቀረበለት ተጨማሪ ጥያቄ ነበር።

«የእኔን የምርምር ውጤት ፣ እዚህ ላይ የሰላጣን አለመጠውለግና መጠውለጉን ማሳየት ይቻላል። ይህም እንዴት ነው፥ የሰላጣ ቅጠል፣ ቀይ መብራት ሲንፀባረቅበትና ሲመለከቱት ፣ ቅጠሉ ምን ይሆናል? ከጥቂት ቀናት በኋላ፤ ምንም ያልሆነውን ከጠወለገው ለመለየት አያዳግትም።»

ከ 10 ቀን በፊት አንድ የ 18 ዓመት ኢትዮጵያዊ ወጣት ፤ በአዲስ አበባ፤ እግረኞች የተደቀነባቸውን የትራፊክ አደጋ በተመለከተ ፣ ለድህነነታቸው የሚበጅ አስጠንቃቂ መሣሪያ ሠርቶ በማቅረቡ ፣ በፕሬዚዳንት ኦባማ አበጀህ ሳይባል አልቀረም። ኢትዮጵያውያን ወጣቶች፤ ለሕብረተሰብ የሚጠቅም ነገር ለማቅረብ በሚያደርጉት ጥረት ሁሉ ፤ የትም ይሁን በሀገር ውስጥም፣ በውጭም አይዟችሁ በርቱ ሊባሉ ይገባል።

የዛሬዎቹ በኢንዱስትሪ የገሠገሱት አገሮች አሁን ከደረሱበት ለመድረስ ፣ ለመደርጀት ፣ በሳይንስና ሥነ ቴክኒክ ባለሙያዎች በእጅጉ መጠቀማቸው የሚካድ አይደለም። ውጤቱ በገሀድ ይታያልና! ውድድሩም ፣ በ የደረጃው በሀገርና በክፍለ ዓለም ደረጃ ነው የሚከናወነው ፤ ለምሳሌ ያህል በዚህ በአውሮፓ በአንድ ዓመት ውስጥ፤ የፈጠራ ውጤት ባለቤትነት መብት መዝጋቢው መ/ቤት 265,690 ማመልከቻዎች ናቸው የደረሱት።

Schüler gemeinsam für Afrika Düsseldorf Solaröfen
ምስል Chantal Kloecker

European Inventor Award የሚሰኝ ዓመታዊ ሽልማትም አለ። ለዘንድሮው አሸናፊ ሽልማት የሚሰጠው ማክሰኞ ሰኔ 10 ቀን 2006 ዓ ም በርሊን ፣ ጀርመን ውስጥ ይሆናል ። ፍጻሜ የደረሱት ተወዳዳሪዎች 3 ናቸው። አደገኛ ጭስን ስለሚመጥ ካብ የተመራመሩ አንድ ኢጣልያዊ ፣ በተንቀሳቃሽ ስልኮች ደረጃ ላይ ሰፊ ምርምር ያደረጉ የተቧደኑ ተመራማሪዎች፤ እንዲሁም ለሳንባ ነቀርሳ የላቀ ፍቱን መድኃኒት ለማግኘት የበቁ በቡድን የቀረቡ ተመራማሪዎች ናቸው ፤ በጠቅላላ አንድ ግለሰብና 2 ቡድኖች!!

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ