1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን የምርጫ ዉጤትና፤ የጥምር መንግሥት ምስረታ ሂደት  

ሰኞ፣ መስከረም 17 2014

በጀርመን የምክር ቤት ምርጫ ይፋ ጊዜያዊ ውጤት መሠረት የመሀል ግራው የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ በጠባብ ውጤት አሸንፏል። የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ በምርጫ ከተሰጡ ድምጾች 25.7 በመቶ አግኝቷል። ወግ አጥባቂው የክርስቲያን ዴሞክራቶች ኅብረት (CDU) እና የክርቲያን ሶሻል ኅብረት (CSU) ጥምረት 24.1 በመቶ ድምጽ አግኝቷል።

https://p.dw.com/p/40w5H
Infografik BTW21 Sitzverteilung AM 0502

ጥምር መንግሥት የሚመሰርቱት የትኞቹ ፓርቲዎች ይሆኑ?

በጀርመን የምክር ቤት ምርጫ ይፋ ጊዜያዊ ውጤት መሠረት የመሀል ግራው የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ በጠባብ ውጤት አሸንፏል። የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ በምርጫ ከተሰጡ ድምጾች 25.7 በመቶ አግኝቷል። ወግ አጥባቂው የክርስቲያን ዴሞክራቶች ኅብረት (CDU) እና የክርቲያን ሶሻል ኅብረት (CSU) ጥምረት 24.1 በመቶ ድምጽ አግኝቷል። ለአካባቢ ጥበቃ የሚቆረቆረው የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ (Greens) 14.8 በመቶ እንዲሁም ነጻ ዴሞክራቶች ፓርቲ (FDP) 11.5 በመቶ ድምጽ አግኝተዋል።  በጥቂት ድምጽ ብልጫን ያገኘዉ የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ መንግስት ለመመስረት ተጣማሪ ፓርቲን ማግኘት ይኖርበታል። ይህ ደግሞ ገና ወራት ያህል ያወዛግባል ተብሎአል። የጀርመን የምርጫ ዉጤት እና ተጣማሪ መንግሥት ምስረታዉ ማንና መች ይሆን በሚለዉ ላይ አዜብ ታደሰ ፤ የበርሊኑን ወኪላችንን ይልማ ኃይለሚካኤልን ጠይቃዋለች።

የ63 አመቱ ኦላፍ ሾልዝ ተሳክቶላቸው ጥምር መንግሥት ከመሰረቱ በአንጌላ ሜርክል ካቢኔ ውስጥ የፋይናንስ ምኒስትር ሆነው በማገልገል ላይ የሚገኙት እና የቀድሞው የሐምቡርግ ከተማ ከንቲባ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ጀርመንን የሚመሩ አራተኛው የሶሻል ዴሞክራት መራሔ-መንግሥት ይሆናሉ። የመራሒተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል አስተዳደርን የሚተካውን ጥምር መንግሥት ታኅሳስ 16 ከሚከበረው የምዕራባውያኑ የገና በዓል በፊት ለመመስረት ተስፋ እንደሚያደርጉም አስረድተዋል።
በታሪኩ የከፋ ውጤት የገጠመው የክርስቲያን ዴሞክራቶች ኅብረት (CDU) እጩ መራሔ-መንግሥት አርሚን ላሼት ግን አሁንም ተስፋ አልቆረጡም። ላሼት "መራጮች የሚሰራውን ሥራ ሰጥተውናል። ምን አልባት በሶስት የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የጋራ ነገሮች ማግኘት አለብን" በማለት ተናግረዋል። 

ይልማ ኃይለሚካኤል

አዜብ ታደሰ