1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋምቤላ ጥቃትና የኢትዮጵያ ጸጥታ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 10 2008

ከደቡብ ሱዳን ድንበር የተሻገሩ ታጣቂዎች በኢትዮጵያ የጋምቤላ ክልል በፈጸሙት ጥቃት የተገደሉ እና ታፍነው የተወሰዱ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው። በጥቃቱ እስካሁን ከ200 በላይ ሰዎች መገደላቸውን እና ከ100 በላይ ታፍነው መወሰዳቸውን ለመንግስት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ብዙሃን በመዘገብ ላይ ናቸው።

https://p.dw.com/p/1IXuz
Karte Südsudan mit Sudan Englisch

[No title]

ጋምቤላ በሶስት ወረዳዎቿ ላይ በተፈጸመ ጥቃት እናቶችና ህጻናትን ጨምሮ ከሁለት መቶ በላይ ተገድለው ከመቶ በላይ ታግተው ከተወሰዱ በኋላ ድንጋጤ እና ቁጭት ገብቷታል። ከዘገየም ቢሆን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት በጥቃት ፈጻሚዎቹ ላይ እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀታቸዉ ከመነገሩ ዉጪ ነዋሪዎቿ ሐዘንም-ሥጋትም ላይ ናቸዉ።
ጠቅላይ ሚኒስቴር ሐይለማርያም ደሳለኝ ትናንት የሙርሌ ጎሳ አባላት ከዚህ ቀደምም «የህጻናት ዘረፋ፤የከብቶች ዘረፋ» እና ግድያ ይፈጽሙ እንደነበር ተናግረዋል። ለመንግስት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ብዙሐን ተመሳሳይ ጥቃቶች «ከመጋቢት 15 እስከ ሚያዝያ 6» ተፈጽመው እንደነበር ዘግበዋል። የፀጥታ ጥናት የተሰኘዉ ተቋም የፖለቲካ ተንታኝ አቶ ሐሌሉያ ሉሌ በቅርቡ በጋምቤላ ክልል በአኝዋክ እና ኑዌር ጎሳዎች መካከል በተቀሰቀሰ ግጭት ተሳትፎ ነበራቸው የተባሉ የጸጥታ ኃይል አባላት ትጥቅ መፍታት የአሁኑን ጥቃት ለመመከት ክፍተት መፍጠሩን ይናገራሉ።
የክልሉ መንግስት እንዲህ አይነት ጥቃቶችን አስቀድሞ ለመከላከልም ይሁን ጥቃቶቹ ሲፈጸሙ ለመመከት አቅም የለውም ያሉን አቶ ሙሳ ሰዒድ ከደቡብ ሱዳን ድንበር የተሻገሩት የሙርሌ ጎሳ አባላት ለጥቃቱ ክላሽንኮቭ የጦር መሳሪያ መጠቀማቸውን ተናግረዋል።
ላለፉት ሁለት አስርት አመታት በአፍሪቃ ቀንድ የተሻለ ጸጥታ እና ደህንነት እንዳላት ይነገርላት የነበረችው ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፖለቲካዊ ጥያቄዎች፤የተቃውሞ ሰልፎች እና የጸጥታ መደፍረስ ይስተዋልባታል። ለወራት የዘለቀው የኦሮሞ ተቃውሞ፤የኮንሶ አለመረጋጋት እና ፤የወልቃይት የፖለቲካ ጥያቄ፤ በጋምቤላ በንዌር እና አኙዋክ ጎሳዎች መካከል ተቀስቅሶ የነበረው ግጭት ይጠቀሳሉ። አሁን ድንበር ተሻጋሪ የሆነው ግጭት ከ200 በላይ ሰዎች የተገደሉበት፤ከ100 በላይ የቆሰሉበት እና ከ100 በላይ የታገቱበት በመሆኑ ከአገሪቱ ደህንነት እና ፖለቲካ አኳያ የሚኖረው ትርጓሜ ከፍ ያለ መሆኑን አቶ ሐሌሉያ ሉሌ ተናግረዋል። የጸጥታ ተንታኙ አቶ ሐሌሉያ ጥቃቱ የሚፈጥረው አለመረጋጋት ወደ ደቡብ ሱዳን ሊዛመት ቢችልም በሁለቱ አገሮች ግንኙነት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽዕኖ የከፋ እንደማይሆን ይናገራሉ።
የሙርሌ ጎሳ ወደ 2000 የሚጠጉ አባላት በኢትዮጵያ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ ስታስቲክስ ባለስልጣን የ2007 የዳሰሳ ጥናት ይጠቁማል።


እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሐመድ