1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዓሊ ቦንጎና ዦ ፒንግ ይፎካከራሉ

Negash Mohammedቅዳሜ፣ ነሐሴ 21 2008

ኦመር ቦንጎ እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ2009 ሲሞቱ ሥልጣኑን የወረሱት ልጃቸዉ አሊ ቦንጎ በዚያዉ ዓመት ተደርጎ በነበረዉ ምርጫ ማሸነፋቸዉ ከፍተኛ አመፅ፤ግጭትና ዘረፋ አስከትሎ ነበር።

https://p.dw.com/p/1Jr5q
Gabun Präsidentenwahl Libreville 27.08.2016
ምስል Reuters/E. W. Obangome

የጋቡን ሕዝብ የወደፊት ፕሬዝደንቱን ለመምረጥ ዛሬ ድምፅ ሲሰጥ ነዉ የዋለዉ።በምርጫዉ በነዳጅ ዘይት የበለፀገችዉን ትንሽ ሐገርን የፕሬዝደትነት ሥልጣን ከሰባት ዓመት በፊት ከአባታቸዉ የወረሱት ፕሬዝደት አሊ ቦንጎ ኦንዲምባ እና የቀድሞዉ የአፍሪቃ ሕብረት ኮሚሽን ፕሬዝደንት ዦ ፒንግ በግንባር ቀደምትነት ይፎካከራሉ።1.7 ሚሊዮን ሕዝብ ያላትን ትንሽ ሐገር ለአርባ ዘመናት የገዙት ኦመር ቦንጎ እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ2009 ሲሞቱ ሥልጣኑን የወረሱት ልጃቸዉ አሊ ቦንጎ በዚያዉ ዓመት ተደርጎ በነበረዉ ምርጫ ማሸነፋቸዉ ከፍተኛ አመፅ፤ግጭትና ዘረፋ አስከትሎ ነበር።ዛሬ ድምፅ ከመሰጠቱ በፊት ተቀናቃኝ ፖለቲከኞች አንዳቸዉ ሌላቸዉን ሲያወግዙ ነበር።ተቃዋሚ ፖለቲከኞች አሊ ቦንጎ የተወለዱት ናጄሪያ ዉስጥ በመሆኑ ሐገሪቱን የመምራት ሕገ-መንግሥታዊ መብት የላቸዉም ሲሉ፤ የመንግሥት ወገኖች ደግሞ ከቻይናዊ አባት የሚወለዱት ፒንግን የቻይና ተወካይ በማለት ይወቅሳሉ።ፒንግ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የቦንጎ ቤተሰብ ታማኝ ዲፕሎማት ነበሩ።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፅሕፈት ቤት ተቀናቃኝ ፖለቲከኞች አመፅና ሁከትን ከሚጭሩ እርምጃዎች እንዲታቀቡ አደራ ብሏል።በምርጫዉ ከ6 መቶ ሺሕ በላይ ሕዝብ ድምፅ ለመስጠት ተመዝግቧል።

ነጋሽ መሐመድ

እሸቴ በቀለ